>
5:13 pm - Thursday April 18, 2424

አጤ ምኒልክ ለምን ለጽንፈኛ ኢሊቶች ቅዠት ሆኑ?!? (ሳሚ ዮሴፍ)

አጤ ምኒልክ ለምን ለጽንፈኛ ኢሊቶች ቅዠት ሆኑ?!?

ሳሚ ዮሴፍ

ሸዋን ወደ ላይም ወደ ታችም አስፍተው የገዙት የአጤ ምኒልክ ስድስት እና ሰባት ትውልዶ ሆነው ሳለ እምዬ ላይ የነገር ፍላጻው. የበረታው ለምን ይህን ካልን:-
 
“ታሪክን አርቀህ ብትቀብረውም በስንጥር ተቆፍሮ ይወጣል”
ዛሬ በአደጉ ሀገሮች ላይ እየኖሮ አእምሯአቸው ያልደገ ለምን እንኳን ሰልፍ እንደሚወጡ የማያውቁ ጽንፈኞች ከ95% ሕዝብ በላይ እንደ እነሱ ስላልጮኸ አሸናፊና ትክክለኛ የሆኑ የሚመስላቸው የአእምሮ ድኩማኖች ዛሬም ድረስ የሚኖርበት ሀገር ሕዝብ ግራ እስከሚገባው ድረስ ዳውን ዳውን ምኒልክ ሲሉ ማየት ያሳፍራል፤ እኛ ለእናንተ ወጥተን መልስ የማንሰጠው በ21ኛው ክፍለ ዘመን እንደ 16ኛው ክፍለ ዘመን ስለምታስቡ ስለማትመጥኑን ነው። በ1906 የሞተ ሰው በመንፈስ የሚገዙ የጤና ስላልሆነ እግዚአብሔር ይማራችሁ።
————–//————
አጤ ምኒልክ ለሸዋ ነገሥታት ስምንተኛ ትውልድ ናቸው። እኔ ግን አሳጥሬ ከቅም አያታቸው ከመርድ አስፋው ወሰን ጀምሮ ወደ ታች አቅርቤዋለህ።
ዛሬ ምኒልክ ከመቅደላ ስለማምለጣቸውን ወደ ሸዋ ስለመመለሳቸው እንመለከታለን….
ምኒልክ እናተቻው ወይዘሮ እጅጋየሁ እና ተከታዮቻቸውን ይዘው ከአባታቸው ወዳጅ ከሆኑት ከወሎ ገዥዋ ወርቂት ዘንድ መስቀላ ደረሱ። ምኒልክ ግን የአባታቸው ወዳጅ ወይዘሮ ወርቂት በሰላም አልተቀበሏቸውም። ምኒልክን እና ተከታዮቻቸውን በሙሉ ወይዘሮ ወርቂት አሰሯቸው። ከዛ በኋላ ወይዘሮ ወርቂት “ምኒልክን እጁን ይዤ ላስረክብዎ ልጄን ልቀቁልኝ” ብለው የሐይቅን መነኮሳት በአማላጅነት ወደ አጤ ቴዎድሮስ ላኩ። መለክሴዎቹ ገና አሊ በር ሲደርሱ ቴዎድሮስ ተበሳጭተው ልጁን አስደብድበው ገደል ሰደዱት፤
የሚል ወሬ ስለሰሙ ተመልሰው መጥተው ለወርቂት ነገሯቸው። ወይዘሮ ወርቂትም ይሄንን በሰሙ ጊዜ
“ይህ ሰው እግዚአብሔር ያልተለየው ነው ገንዘቡንም መልሱ፤ እርሱንም በክብር አምጡልኝ” ብለው ምኒልክ ወደ ታሰሩበት ወደ መስቀላ ላኩ። ምኒልክም ከመስቀላ ቦሩ ሜዳ በደረሱ ጊዜ ወይዘሮ ወርቂት በክብር ተቀብለው “የሸዋ ሰው አውራህ መጥቷልና ደስ ይበልህ ተቀበል”  ብለው አዋጅ አስነግረው በደጃች ገብርዬ የሚመራ አጃቢ አድርገው መለከትና እምቢልታ ጨምረው ወደ ግሼ ድምበር ወደ
አሊ ቡኮ ላኳቸው።
ግሪን ፊልድ እንደፃፈው “…እንደ ሌሎቹ ሸዋዎች ሁሉ ምኒልክ የኦሮሞ ደም ስላለባቸው ወይዘሮ ወርቂት በእርግጥ ይህን ታውቅ ስለነበር ወደ ሸዋ እንዲገቡ አደረገች…” ይላል።
ግሪን ፊልድ ይሄን ያለበት ምክንያት የወሎ ገዥ ወይዘሮ ወርቂት ኦሮሞ ስለነበሩ ነው።
ምኒልክ በሰላም ሸዋ ቢደርሱም ሸዋ ለመግባት ግን አልተመቻቸውም ነበር። የሸዋ ንጉሥ ነኝ ይሉ የነበሩት አቶ በዛብህ የሸዋን ሠራዊት ሰብስበው “ምኒልክ ከአጤ ቴዎድሮስ ጋር ውል አለው፤ ውሉም እኛን አሳልፎ ለመስጠት ነው፤ ቴዎድሮስ ደግሞ ይቀጡናል ይቆራርጡናል” በማለት አዋጅ አስነግሮ ሠራዊቱ ለጦርነት እንዲዘጋጅ አደረገ።
ከዚህ በፊትም አቶ በዛበህ ለወይዘሮ ወርቂት”… ምኒልክን እሰሪልኝ ብሎ 2000 ብር፣ ፈረስና በቅሎ ሰዶላት ነበር…”
ሲሉ አለቃ ገብረስላሴ ጽፈዋል።
ዳር ዳር ያሉት የሸዋ መኳንንት ለምኒልክ በሰላም ገቡላቸው፤ ወይዘሮ ወርቂትም አጃቢ አድርገው የሰጧቸው የእሳቸው ሎሌ ሆነው አብረዋቸው ተጓዙ ኃይላቸውም እየበዛ ሄደ።
የምኒልክን ወደ ሸዋ መግፋት የሰሙት አቶ በዛብህ ግን ከምኒልክ ጋር ጦርነት ለመግጠም ጋዲሎ ከተባለው ቦታ ላይ ተሰለፉ በዚህ ጊዜም አንዲት ሴት…
ማነው ብላችሁ ነው ጋሻው መወልወሉ 
ማነው ብላችሁ ነው ጦራችሁ መሾሉ 
ማነው ብላችሁ ነው ካራቹህ መሳሉ 
የጌታችሁ ልጅ ነው ኧረ በስማም በሉ” ብላ ገጠመች።
ጦርነቱም በ1857 ዓ.ም ነሐሴ 16 ቀን ሰኞ ዕለት ተጀመረ።
በጦርነቱም ድል አድርገው አንድ ሺ ጠበንጃ እና አንድ መድፍ ሲማርኩ አቶ በዛብህ ግን አምልጠው ወደ አፍቅራ ሸሹ። ይህንን የጋዲሎን ከፍተኛ ድል የቀመሱት ምኒልክ ክብረት አምባ ከተባለው ስፍራ የተከማቸ ሌላ አንድ ሺ ጠበንጃና ሦስት መድፍ ስላገኙ የጦር ኃይላቸው እየተጠናከረ ሄደ። በብዙ አጀብም ከአባታቸው ከአንኮበር ከተማ ገቡ። ምኒልክም አንኮበርን ትተው ልቼ ላይ አደረጉ። በጦርነት ተሸንፈው ወደ አፍቅራ ሸሽተው የነበሩት አቶ በዛብህም “አጥፍቼአለሁና ይማሩኝ” ብለው መልእክት ላኩ፤ ምንም እንኳን አጠገባቸው ያሉት መኳንንቶች አውቆ ነው እዚህ ከመጣ በኋላ ሊያሴር ነው አይማሩት ቢሏቸውም ምኒልክ ግን “ከሆነም ወደፊት አያዋለሁ ምሬዋለሁ ይግባ” አሉ። እንደተባለውም አቶ በዛብህ ውስጥ ውስጡን ማሴር ጀመሩ መኳንንቱን በማባባል በምኒልክ ግልበጣ ላይ ያሴሩ ጀመር።
ምኒልክም ይሄን ወሬ ሰምተው ወደ አቶ በዛብህ ሰላይ ልከው እውነት መሆኑን አረጋገጡ። አቶ በዛብህም ታስረው ቤታቸው ሲፈተሽ ከመኳንንቶቹ ጋር የተጻጻፉት ደብዳቤ ተገኘ። ችሎት እንዲደረግም ታዞ አጤ ምኒልክ በደላቸውን ለችሎቱ ነግረው ደብዳቤዎቹንም አቅርበው ፍርድ ጠየቁ።
ችሎቱም በአቶ በዛብህ ላይ የሞት ፍርድ ፈረደባቸው። የሞት ፍርዱን እንዲጸኑ የመጨረሻው ተራ ምኒልክ ጋር ሲደርስ “እንደምታውቁት በድሎኛል፤ እሱ የሌለውን እኔ ባለኝ በአባቴ አልጋ ልቀመጥ ብል መንግሥቴን ማናወጥ ጀመረ፤ አባቴ ሀገር ልግባ ብል አትገባም ብሎ ተዋጋኝ፤ ደጋግሞ ብሎ ቢበድልኝም ንስሐ ገብቶ ተጸጽቶ ለክፉ ቀን የሚሆነኝን በዛብህን የሚያህል ጀግና አልገለውም ምሬዋለሁ፤ ዳግመኛ ግን እንዳያጠፋ ይመከርልኝ፤ ከእሱ ጋር ያሴሩብኝ በሙሉ ምሬአቸዋለሁ” ብለው ያልተጠበቀ ፍርድ ፈረዱ።
መኳንንቶቹ ግን አቶ በዛብህ እንዲህ የሚተማመነው አፍቅራ ባለው ምሽጉ ነው፤ እዚያ ያለውን መሣሪያና ሠራዊት ያስረክብ አሉ፤ አቶ በዛብህም ወደ አፍቅራ ሄደው ሠራዊቱ እምቢ አለኝ በማለት ምሽጉን ለመስበር በተደረገ ጦርነት ብዙ ሰው አለቃ። አቶ በዛብህ ለሦስተኛ ጊዜ ተይዘው ፍርድ ቀረቡና የሞት ፍርድ ተፈረደባቸውና ተገደሉ።
አልቃሽም…
አንተም ጨካኝ ነበር ጨካኝ አዘዘብህ፣
እንደ ገና ዳቦ እሳት ነደደብህ። 
ኦሮሞ አርፈህ ተኛ አውልቀህ ጀባህን፣ 
አማራውም ተንፍስ አራግፍ ኮርቻህን 
በእሳት አቃጠሉት የሚያባንንህን። ብላ ገጥማለች።
ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ እንደፃፉት አቶ በዛብህ የተገደሉበት ጠበንጃ በባሩድና በጨርቅ እየተደቀደቀ በካምሱር የሚተኮስ ነበርና ከባሩዱ ኃይልና ብዛት የተነሳ የለበሰው ልብስ በእሳት ስለተያየዘ ሰውነቱ ተቃጠለ የአቶ በዛብህ ዘመዶችም የተረፈውን ሰብስበው ወስደው ደብረብርሃን ቀበሩት ብለዋል።
አቶ በዛብህ አጤ ቴዎድሮስ ሸዋን ለማስገበር በመጡ ጊዜ በጀግንነት የተዋጉና የጌታዬን ልጅ አላስማርክም ብለው ምኒልክን ይዘው የሸሹ ነበሩ። በጀግንነታቸው አጤ ቴዎድሮስ ሳይቀሩ ያደነቋቸው ጎበዝ ተዋጊ ነበሩ።
የአቶ በዛብህ ጉዳይ በዚህ መልኩ ከተፈጸመ በኋላ ምኒልክ በ1858 ዓ.ም በቴዎድሮስ ዘመነ መንግሥት ምኒልክ ንጉሠ ሸዋ ተብለው ነገሱ።
ምኒልክ የተወለዱት ደብረ ብርሃን አጠገብ ከሚገኘው አንጎለላ ውስጥ ነው፤ ያደጉትም ከሸዋ ኦሮሞ ልጆች ጋር ነው፤ ከመቅደላ አምልጠው ሸዋ ሲገቡም ለመጀመሪያ ጊዜ ያረፉት ከቢሸፍቱ ደቡብ ባለው ከአዳው ኦሮሞ ከቡታ ቤተሰቦች ዘንድ ነው። በሸዋም ላይ ሲነግሱ የረዷቸውና ያስተባበሩላቸው አብሮ አደግ ጓደኛቸው ኦሮሞው
 ጎበና ዳጨው ናቸው። ጎበናም የምኒልክን ግዛት ያመቻቹና ያስተካከሉ ታላቅ ሰው ናቸው።
ምኒልክ ሸዋ ከገቡ በኋላ “የአባቴን ግዛት መያዝ አለብኝ” ይሉ ጀመር። የሸዋው ንጉሥ የምኒልክ አያት ሣህለሥላሴ ሲሞቱ ወዲያው የሸዋ ግዛት በየባላባቱ ተከፋፍሎ ለማንም የማይገብር ራሱን የቻለ መንግሥት ቢጤ ሆኖ ነበር።
ምኒልክ የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑትን ጎበና ዳጨውንና ሌሎችንም ረዳቶቻቸውን አማክረው የሸዋን ግዛት ለማስፋፋት ተስማሙ። የዚያን ጊዜ የሸዋን ግዛት ለማስፋፋት ወይም ወደ ነበረበት ለመመለስ የተስማሙበት አንዱ ምክንያት ኢትዮጵያን ዙሪያዋን የከበቡ ቀኝ ገዢዎች ለእያንዳንዱ ባላባቶች ስጦታ በመስጠትና በማባባል የኢትዮጵያን ግዛት በመቁረስ ወደ ራሳቸው ቅኝ ግዛትነት ይደባልቁ ስለነበር እነኚያን ቅኝ ገዢዎች ለማስቆም ነበር።
ምኒልክ ከመጀመሪያ ጀምሮ ሥራቸው ነገሮችን በሰላም መጨረስ ይወዱ ስለነበር በሸዋ አካባቢ ላሉት ለተከፋፈሉት የኦሮሞ ባላባቶች “ያሳደጋችሁኝ ልጃችሁ አብሬ ያደጉኝ ወንድማችሁ ነኝና በአባቴ አልጋ ከተቀመጥኩ በፍቅር ተገዙልኝ” እያሉ መልክተኛ ይልኩባቸው ጀመር።
አንዳንዶቹ የልጅነት ጓደኞቻቸው በአሁኑ ጊዜ በሞቱት አባቶቻቸው ቦታ የባላባትነቱን ቦታ ይዘዋል። የቅርብ ጓደኞቻቸው ከነበሩት አንዳንዶቹም ለምኒልክ ገብተው እንደ ጎበና የመሳሰሉት የቱሉማ ባላባት ልጆች አብረው ይኖራሉ።
ምኒልክና ጎበና እሺ ያለውን በፍቅር እምቢ ያለውን በጦር ለማስገበር ተስማሙ። በወዳጅነት እንዲገቡ የተላከባቸው የኦሮሞ ባላባቶች የምኒልክ አገዛዝ እንዴት እንደሆነ ጎበናን ይጠይቁ ጀመር። ጎበናም ከምኒልክ ጋር የጨረሱትን “ግዛታችሁና ባላባትነታችሁ አይነካም፤ ግን ለመሀከለኛው ለምኒልክ መንግሥት በዓመትግብር ትከፍላላችሁ፤ የተበታተነው ኦሮሞ አንድ ሆኖ ይኖራል” እያሉ ይነግሩ ጀመር።
*ቼሩሊ እንደፃፈው “…ለመጀመሪያ ጊዜ የሚታው ባላባት
ቢራቱ ጉሌ በምኒልክ ሀሳብ ተስማምቶ ገባ። ምኒልክም ቢራቱ ጉሌን ሸልመው ግዛቱን መረቁለት። የጉለሌው ባላባት ቱፋ ሙና አልገባም አልገብርም ብሎ እምቢ አለ፤ ቀደም ብለው በገቡት በአቢቹና በቢራቱ ቢለመንም እምቢ ስላለ ጦርነት ገጥሞ በጦርነት ተገደለ። ለጉለሌ ባላባትነት የሚገባውን በሕዝብ አስመርጠው ሾሙ። የሸዋ ኦሮሞም እንደ ቴዎድሮስ ይቆርጣሉ ብለን ነው እንጂ ግዛታችን ከኛ የማይወጣ ከሆነ በማለት ብዙዎቹ በሰላም ገቡላቸው…”
የሸዋ ኦሮሞን ከያዙ በኋላ የጎበናን ፈረስ አስቀድመው ይጓዙ ጀመር። በ1866 ዓ.ም መርሐቢቴን፣ ጉመሮንና ቸሃን አስገበሩ። በ1873 ዓ.ም ጥሙጋንና አዳልን (አፋርን) አዘሎ ድረስ ያለውን ሀገር በጦር ኃይል አስገብረው #እንደ #ጥንቱ #የኢትዮጵያ ግዛት እንዲሆን በሸዋ ስር አደረጉት።
ይህም ቢሆን የእንግሊዝ፣ የፈረንሳይ፣ የጣልያን እና የግብጽ መንግሥታት አፋርን ለመያዝ እርስ በእርሳቸው እየተሻኮቱ
ስብከታቸውን አላቆሙም ነበር። ይህንን ጉዳይ የሚያውቁት ምኒልክ ለእነዚህ ሀገሮች መንግሥታት በሙሉ ለእያንዳንዳቸው “አባቶቼ ይገዙት የነበረውን እና በኋላ ጊዜ የከዳውን የአዳልን ግዛት መልሼ በእጄ ስላደረኩት ደስ ብሎኛል እና እርስዎም ወዳጄ ስለሆኑ ደስ ይበልዎት” እያሉ ደብዳቤ ጻፉላቸው። ይህም ግዛት የኢትዮጵያ መሆኑን ገዢውም እሳቸው መሆናቸውን ለማሳወቅ ሲሆን በሌላ በኩል እነኚህ ሀገራት አፋርን እንደተመኙት እንይዛለን ቢሉ ጦርነት የሚገጥሙት ከምኒልክ ጋር መሆኑን ለማሳወቅም ጭምር ነው።
ምንጭ...አጤ ምኒልክ  ጳውሎስ ኞኞ
ምኒልክ ኢትዮጵያን አንድ ሲያደርጉ ቅዠተኞቹ እንደሚያወሩት አይደለም ይህንን ሁሉ ሀገር አንድ አድርገው ለመሀከላዊው መንግሥት እንዲገብር ሲያደርጉ ያደረጉት ጦርነት ከአራት አይበልጥም በሚቀጥለው ጽሑፍ እንመለከታለን።
Filed in: Amharic