>

እኔ ኦሮሞን የማውቀው …  (አሌክስ አብርሃም) 

እኔ ኦሮሞን የማውቀው …

 (አሌክስ አብርሃም) 

‹‹የኦሮሞ ጥላቻ  ›› የሚል ታፔላ በመለጠፍ  ማንንም ማሸማቀቅ አይቻልም፡፡ ላለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ህወሃትና ደጋፊዎቹ እንዲሁም የጥቅም ተጋሪዎቹ ሲነኩ ሲመከሩና ሲዘከሩ ነገሮችን በሰከነ መንገድ ቁመው ከማየት ይልቅ   ዘለው ‹‹የትግሬ ጥላቻ›› እያሉ ህዝብ ውስጥ ለመደበቅና ስህተታቸውን በህዝብ ካባ ሲጠቀልሉ ይሄው የጊዜ ሰፌድ ራሱ እንደ ልቃሚ አንጓሎ ገለል አደረጋቸው ፡፡ ለህዝብ ምን ይዘውለት ሄዱ ተረትና ስጋት ፡፡
አሁንም በኦሮሚያ ህዝብ ራሱን ለመጠቅለል የሚፍገመገመው ዋናው ቄሮ ሳይሆን የድል አጥቢያ አርበኛውና እነጃዋር ጠፍጥፈው የሰሩት ቄሮ ይሄን አለም በሙሉ የሚፀየፈውን የሽብር ድርጊቱን‹‹ተው ›› ሲባል ‹‹የኦሮሞ ጥላቻ ›› እያለ የማያዛልቅ ለቅሶና ስም ልጠፋውን ተያይዞታል ፡፡  ‹‹ለኦርጅናሌዎቹ›› ያልበጀ ዘፈን ምን እንሁን ብላችሁ ነው የምታላዝኑት ? ‹‹ዋናው ያልበጀ ቅራሪው ሰው ፈጀ ›› ሆነኮ ነገሩ !
 ቆይ የምን ጥላቻ ነው የምታወሩት ?
እኔ ኦሮሞን የማውቀው…  በባዶ እግሩ ሮጦ በአለም መድረክ ላይ ሲያስጠራን እንጅ …በባዶ ጭንቅላቱ ገጀራ ይዞ ሰው ሲያርድና ባዶ ሲያስቀር አይደለም ፡፡
እኔ ኦሮሞን የማውቀው …በነፋጡማ ሮባ  በነሃይሌ ገብረስላሴ በነቀነኒሳ በነጡሩነሽ ዲባባና በሌሎቹም ጀግና ልጆቹ  በኦሎምፒክ ትራኮች ላይ አረንኳዴ ጎርፍ ሁኖ በህብረት  ሪከርድ ሲሰብር እንጅ  በመንጋ ግር ብሎ የሰው ንብረትና ተስፋ ሲሰባብር አይደለም !
እኔ ኦሮሞን የማውቀው… በእርሃብና  ድርቅ ስሟ የጠፋ አገሬን  በስፖርት መድረኮች ላይ በፍቅር  ባንዲራዋን ከፍ አድርጎ ከፍ ሲያደርገን እንጅ  <<ዳውን ዳውን>>  እያለ አገሩንም ራሱንም አውርዶ ባንዲራ ሲረጋግጥ አይደለም !
እኔ ኦሮሞን የማውቀው … ገና በ15 ዓመት እድሚያቸው እምቢ ላገሬ ብለው አገራችንን ከወራሪ   ፋሽስት  በታደጉት  ሌፍተናት ጄኔራል ጃገማ ኬሎ እና ቢጤዎቻቸው እንጅ  …በየኩሽናው እየገባ  አያቶቹ የሚሆኑ ባልቴትና ሽማግሌዎችን  በግፍ  ሲገድል አይደለም ፡፡
እኔ ኦሮሞን የማውቀው  ወላጅ  ያጡ ህፃናትን በጉዲፈቻ ወስዶ በፍቅር ሲያሳድግ  እንጅ  ያራሱን ልጆች በሃሳብ ልዩነት ሲበላ አይደልም !
እኔ ኦሮሞን የማውቀው…  በብርቱ ክንድ  ህዝቡን ከወራሪ ሲከላከል እንጅ  ህፃናት ላይ ስለት ሲያነሳና  ወላጆቻቸውን ጨፍጭፎ  ካለወላጅ ሲያስቀር አይደለም ፡፡
እኔ  ኦሮሞን  የማውቀው… በአባ ገዳዎቹ  አገርና  ህዝብ የዱር እንስሳና አዝመራ ሳይቀር በመልካም ቃል  ሲመርቅና ልዩነትን አንተም ተው አንተም ተው ብሎ ሲያስታርቅ   እንጅ  በወጉ  አፍ ያልፈቱ   ህፃናትን የድምፅ ማጉሊያ አስይዞ የዘር ፍጅት ሲያሳውጅ አይደለም !
እኔ ኦሮሞን የማውቀው…  ትርጉሙን እንኳን ሳናውቀው አይኖቻችን በሲቃ እንባ እስኪቋጥሩ በውብ ዘፈኖቹ ባስደመመንና እንኳን ሰውን የኦሮሚያ ጫካና ተራሮችን ‹‹ምነው ሂደን ባየናቸው›› ባስባለን አሊ ቢራ ዘፈኖች እንጅ  ጩኸታቸውና  ስድባቸው  በሚቀፍ  ምድሩ ላይ የሚኖሩ ዜጎች  ላይ በዋለው ግፍ አገሩን በዋይታና ሰቆቃ ድምፅ ባስሞሉት ወመኔዎች አይደለም፡፡
እኔ ኦሮሞን የማውቀው …ወዳጅ ብቻ ሳይሆን አገራችንን የወረረ ጠላት መሪዎች እነ ጂዬቫኒ ቴዶን ለሰራዊታቸው መሸነፍ ቁልፉን ሚና የተጫወቱት የኦሮሞ ፈረሰኞች መሆናቸውን ሲመሰክሩላቸው እንዲሁም  ‹‹የኦሮሞ ተዋጊ ፈረሰኞች  ወደ ሸለቆው ሲወርዱ ድንገት የገነፈለ ጥቁር ባህር ይመስሉ ነበር›› ሲሉላቸውና ጠላት ገና ከሩቅ አይቷቸው ሲርድ እንጅ  …ዱላና ስለት  ይዘው ያውም ራሳቸውን መከላከል የማይችሉ  ሰላማዊ ዜጎች  ላይ ሲዘምቱና     ህፃናትና ሴቶችን ሲያስለቅሱና ሲያስጨንቁ አይደልም!
 እኔ ኦሮሞን የማውቀው እንደዚህ ነው !!  አገር ሲያረጅ ጃርት ያፈራል እንደሚባለው … የጥላቻ ንግግራቸው መርዛማ ላባ የሆነ ፣ በጥላቻ የተሞሉ፣ እንደጃርት የሰው ሰብልና ንብረት የሚያወድሙ …ነብሰ ገዳዮች ስለዚህ ከፍ ባለ ክብር ስለማውቀው ያገሬ ኦሮሞ ሊሰብኩኝም ሆነ ሊያስተምሩኝ ወኔውም እውቀቱም የላቸውም ፡፡
 አገሬው ስለጃርቶቹ ያውራ እንጅ ጃርቶቹ ስለአገሩ ሊያወሩ አፍ የላቸውም !! ባጭሩ አንተን ኦሮሞ ህዝብ መሃል የተደበከውን ነብሰገዳይ ጃርት እንኳን እኔ የሰው ልጅ በሙሉ ይጠለሃል !! ኦሮሞው ራሱ የውሸት እና ጥላቻ ስብከትህ እየገባው አንቅሮ እየተፋህ ነው ፡፡ ከኦሮሞ አብራክ የወጡ ልጆችን አለም በፍቅር ሲመለከታቸው  ሲደመምባቸው እንጅ ማንም  በጥላቻ ስማቸውን ሲያነሳቸው ታይቶም ተሰምቶም አይታወቅም ! የኦሮሞ ስም በክፉ ሲነሳ የሰማነው በአንተ አሰቃቂ ነብሰ ገዳይነትና ክፋት ነው ፡፡
ከህዝብ ማሳ ውስጥ የደረሱ ልጆቹን እያነክ የምትቀጥፈው ጃርት …ጥላቻህ አስጠልቶሃል፡፡ ህዝብ መስተዋት ነው…በዚህ መስተዋት  እያየህ ያለኸው የራስህን የጥላቻ መልክ ነው ! ደግሞ መልኩ የራስህ አይደለም  የሚነዱህ አጥፊዎች እንደሜካፕ  ፊትህ ላይ በጥላቻ ቀለም  የሳሉልህ  እንጅ  ፡፡ በአባቶችህ ፍቅር ፊትህን ታጠበው… ያኔ ኩሩ ኦሮሞ መልክህ ይወጣል… መስተዋት ፊት ስትቆምም የምታየው ያንኑ ፍቅር ነው !! ከዚህ ውጭ ጠሉኝ እያልክ ስትጮህ ብትውል …የሚቀየር ነገር …..አበደን !!
Filed in: Amharic