>

እነሆ ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ እ.ኤ.አ.  በ1902 ዓ.ም. ከእንግሊዝ  መንግሥት ጋር የተፈራረሙት ስምምነት ትክክለኛ ቅጂ!   (አቻምየለህ ታምሩ)

እነሆ ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ እ.ኤ.አ.  በ1902 ዓ.ም. ከእንግሊዝ  መንግሥት ጋር የተፈራረሙት ስምምነት ትክክለኛ ቅጂ!  

አቻምየለህ ታምሩ

ሱሌማን ደደፎ ሲባል የሰማውን ሳያጣራ በመድገም በዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ላይ የሰነዘረውን የሐጢዓት ክስና ያስተጋባውን የፈጠራ ትርክት ለመተቸት ያቀረብሁት እ.ኤ.አ. በ1902 ዓ.ም. ከእንግሊዝ  መንግሥት ጋር የተፈረመው ስምምነት በታይፕ የተመታ ጽሑፍ በመሆኑ  ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ የተፈራረሙት  የዓባይን ወንዝ ላለመገደብ  ሳይሆን ውኃውን ከዳር እስከ ዳር በመድፈን ለማስቆም ሲያስቡ ብቻ ከእንግሊዝ መንግሥት ጋር አስቀድመው መስማማት እንዳለባቸው የሚጠቅስ እንደሆነ የሚያትተውን የስምምነቱን 3ኛ አንቀጽ የተጠራጠሩ አልጠፉም።
ምንም እንኳን  መዋሸት በማይቻልበት ዘመን ያተምሁትን ዶሴ የሚጠራጠር ሰው ቢኖር አሳማኝ ማስረጃ ማቅረብና ተፈረመ ብሎ የሚያምነውን ስምምነት ትክክለኛ ቅጅ  በማሳየት መሞገት እንዳለበት ባምንም የስምምነቱ ትክክለኛ ቅጂ ለአንባቢ መቅረቡ ጠቃሚ መሆኑን ስለምገነዘብ ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ እ.ኤ.አ. በ1902 ዓ.ም. ከእንግሊዝ መንግሥት ጋር የአባይን ወንዝና የጣናን ሐይቅ እንዲሁም የኢትዮጵያና ሱዳንን ድንበር አስመልክተው የተፈራረሙትን በብራና የተጻፈውን ስምምነት ዋናውን ቅጂ እነሆ ከታች አትሜዋለሁ።
በቀይ ያሰመርሁበት  የብራናው ቅጂ አንደኛው አንቀጽ የኢትዮጵያና ሱዳንን ድንበር የሚያሳይ ሲሆን [ከስምምነቱ ጋር የተያያዘውን ካርታም ማየት ይቻላል]  የተሰመረበቱ ሶስተኛው አንቀጽ ደግሞ ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ እ.ኤ.አ. በ1902 ዓ.ም. ከእንግሊዝ  መንግሥት ጋር የተስማሙት ዓባይን ከዳር እስከ ዳር ለመገደብና ለመድፈን ሲያስቡ አስቀድመው ከእንግሊዝ መንግሥት ጋር እንዲስማሙ እንጂ እነ ሱሌማን ሲባል የሰሙትን ሳያጣሩ በመድገም እንደሚያስተጋቡት በወንዙ ላይ ምንም አይነት ግድብ ላለመስራት አይደለም።
እንዴውም በስምምነቱ ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ የማንንም ፍቃድና ስምምነት ሳይጠይቁ፤  ከግብጽ ጋር አስማሙን እያሉ  ከደቡብ አፍሪካ እስከ አሜሪካ መንግሥታት ደጅ ሳይጠኑ እስከ 99% የሚሆነውን የዓባይን ወንዝ  መጠን መገደብ  የሚያስችል መብት ለኢትዮጵያ አስገኝተዋል። ይህን አይነት ስምምነት ያደረጉትን የኢትዮጵያ መሪ ነው እንግዲህ  የዛሬዎቹ  የሰፈር ኮልኮሌዎች ዳግማዊ ምኒልክ የተስማሙትን ይህንን አይነት መብት ለኢትዮጵያ የሚሰጥ ስምምነት ለመድገም  ቆርቶ የኢትዮጵያ አጀንዳ እንኳን አድርገው የማቅረብ ሞራሉ ሳይኖራቸው የራሳቸውን አለመቻላቻውን በሚጠሏቸው ስም ምኒልክ እያሳበቡ ያልፈረሙትን ስምምነት እንደፈረሙ አድርገው በማቅረብ ሲወቅሷቸውና  የኢትዮጵያን ወንዝ ለመጠቀም የግብጽን ይሁንታ ለማግኘት ሲለማመጡ  እየዋሉ የአለም መሳለቂያ ሲያደርጉን ይውላሉ።
Filed in: Amharic