>

የታጋቹ ማስታወሻ  (በእውቀቱ ስዩም)

የታጋቹ ማስታወሻ 

በእውቀቱ ስዩም

ይሄ ቀሳ  ግን ስንቱን አሳበደ?   ቲክቶክ ምስክሬ ነው፤ የድሮ እብድ ሙዚቃ ቤት በር ላይ ይደንስ ነበር ፤ የዘንድሮ ዲጅታል  እብድ ደሞ ሞባይሉ ካሜራ ፊት ይደንሳል ፤  እኔ ራሴን እየታዘብኩት ነው፤   አሁን “ ዘፈን ሃጢአት ነው አይደለም?”  በሚል ክርክር ላይ  በስካይፒ መሳተፌ የጤና ነው?  
ኬፋ ሚዴቅሳ ;- በእውቄ ዘፈን ላንተ ሃጢአት ነው ወይስ አይደለም?
 እኔ  – well  ችሎታ ሳይኖርህ ከዘፈንህ ሀጢአት ነው፤   ቀሺም ዘፈን ራሱን የቻለ ሀጢአት እንኳን ባይሆን ወደ ሌሎች ሀጢአቶች ይመራል :: በምሳሌ ላስረዳህ፤ የሆነ ጊዜ ላይ   በጉዋደኛችን ሰርግ ላይ አንዱ  የሃይልየ ታደሰን የሰርግ ዘፈን ለመዝፈን ሞከረ   ፤ ድምፁ ግን  ከሃይልየ ይልቅ  ለሃይሌ ይቀርባል፤   ሙሽራው ተናደደና ካንዱ አጃቢ ጠመንጃ ቀምቶ  ተኩሶ  ገደለው ፤   ወዳጄ  ፍርድቤት ሲቀርብ ለምስክርነት ቀርቤ “ ባርቆበት ነው” ብየ ዋሸሁ፤   እስርቤት ሲገባ ሚስቱ ከጠበቃው ጋር ተኛች፤  ባንድ ብሽቅ ዘፈን ምክንያት   “ አትግደል፤ በሀሰት አትመስክር፤  እና “አታመንዝር “ የሚባሉ ህግጋቶች ተጣሱ!
አቤት እኔኮ እተነትነዋለሁ !
 በነገራችን ላይ  ጌትሽ ማሞ የኮሮናን መስፋፋት አስመልክቶ አዲስ  ዘፈን ሊለቅ ነው፤  ርእሱን “ ተቀባበል” ብሎታል አሉ፤
  ባልተያያዘ ዜና ፤ ባለፈው ከአመፁ ከተመለስሁ በሁዋላ ገላየን ስታጠብ የሆነ ሚጢጢ ቁስለት አንገቴ ስር  አየሁ፤ ለካ  በትንቅንቁ መሀል በፕላስቲክ ጥይት rubber bullet  ተመትቻለሁ፤  ጥይቲቱን ካንገቴ ውስጥ ነቅሼ  አውጥቼ   ስመለከታት    Durex የሚል ምልክት እንደተፃፈባት ልብ አልሁ፤
 በነገራችን ላይ የጊዮርጊስ ፍሎይድ ግድያን   ተከትሎ ብዙ ፈረንጆች በ ሃይለኛ የጠጠት ስሜት እየተሰቃዩ ነው፤  ድሮ ከመ-ገብስ የማይቆጥሩን   ሰዎች፤ አሁን በክብርና እንክብካቤ እያጨናነቁን ነው ፤እኔማ አጋጣሚውን ተጠቅሜ ከሶስት ሴቶች ስልክ ተቀበልኩ፤
አንደኛዋ በዩንበርሲቲያችን ውስጥ ሚስስ ዩንበርስቲ ተብላ መሸለሙዋን ብነግራችሁ አታምኑኝም ’፤  በማግስቱ ጀምሮ በጉጉል ቪድዮ ማውራት ጀመርን ፤ ደና አውርተን አውርተን እሚገራርም ጥያቄ መጠየቅ ጀመረች፤
“ ኩዋራንታይኑ  ካለቀ በሁዋላ ቅልጥ ያለ ኦርጂ ለማሰናዳት አስበናል፤ ትቀላቀለናለህ?”
“ ምንድነው ደግሞ ኦርጂ ”
“ በቡድን ግብረስጋ ማድረግ አታውቅም?”
  “  አላውቅም! ባገራችን በቡድን የምንሳተፈው በአጨዳና በማስ ስፖርት ላይ ነው’
’ ኩዋረንቲን ምርር ብሎኛል!   ዲልዶም እየሰለቸኝ ነው   ” አለቺኝ ደሞ ሌላ ቀን፤
“ ዲልዶ ምንድነው? “  አልኩኝ፤
“  ዲልዶ ማለት  ጥዝዝዝዝዝ የሚል ድምፅ ያለው  የደስታ እቃ  ነው”
“ ኦ! እኛ ጊልዶ ነው እምንለው” አልኩዋት!
በዚህ አይነት ለሶስት ቀናት ካወራን በሁዋላ አንድ ምሽት ላይ  አልጋዋ ላይ እንደተቀመጠች፤
“እስቲ ዛሬ እንኩዋ አውልቀህ አሳየኝ” ስትለኝ ጆሮየን ተጠራጠርኩ፤
 “ አውልቅና አሳየኝ ነው ያልሽኝ? “
“ አዎ”
ባንድ ጊዜ  ንዴትም አፍረትም ፍልጎትም ሰቅዞ ያዘኝ ፤“ስሚ! ቀን ጥሎኝ ነው እንጂ ባገሬ የተከበርኩ ሰው ነኝ፤ “
 እሱዋ;-” ታድያ ይሄ  ፌስ ማስክ ከማውለቅ ጋር ምን ያገናኘዋል?”
Filed in: Amharic