>

የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውን ውለታ ለአፍሪካ አንድነት/ኅብረት (በተረፈ ወርቁ)

የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውን ውለታ ለአፍሪካ አንድነት/ኅብረት

እንኳን ለአፍሪካ ቀን አደረሰን!

 

በተረፈ ወርቁ


‘‘ኢትዮጵያ ለእኛ ለአፍሪካውያንና ለመላው ጥቁር ሕዝቦች የነጻነታችን ትእምርት/Symbol የሆነች አገር ናት፡፡ ስለሆነም አዲስ አበባ ‹‹የፓን አፍሪካን መዲና›› (የአፍሪካ አንድነት ከተማ) መባሏ ከዚህ ታሪካዊ ሐቅ ጋር የተያያዘ ነው…፡፡’’ (የናይጄሪያው ሳንዴይ ኦብዘርቨር/ጁላይ 23፣ 1972)

 

ይህ አጭር መጣጥፍ የትናንትናው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) የዛሬው የአፍሪካ ኅብረት (AU) የተመሠረተበትን 57 ዓመት ምክንያት በማድረግ- ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ለአፍሪካ ሕዝብ የፀረ-ቅኝ ግዛትና የነፃነት ተጋድሎ እንዲሁም ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት/አፍሪካ ኅብረት መመሥረት ያደረጉትን ታሪካዊ አስተዋጽኦ በተመለከተ በጥቂቱ ለመዘከር ታስቦ የተዘጋጀ ነው፡፡ መልካም ንባብ፡፡ 

‘‘የአፍሪካ መዲና’’ ተብላ በምትጠራ አዲስ አበባችን፣ ለአፍሪካና ለአፍሪካዊነት ወንድማማችነትና ኅብረት ታላቁን መሠረት በጣለች በሀገራችን ኢትዮጵያ- የአፍሪካ ምሥረታ ቀን፣ የአፍሪካ ቀን እንደሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ብሔራዊ ቀን ሆኖ መከበሩ ቢቀር እንኳን ቀኑን በቅጡ የማናስበው መሆኑ እንዴት ያሳፍራል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ የትናንትናዎቹ ኢትዮጵያውያን ትውልዶች- ለተባበረች አፍሪካ፣ ለአፍሪካ ሕዝቦች አንድነት፣ ኅብረትና ወንድማማችነት የከፈሉትን ክቡር መሥዋዕትነት መዘከር የሚገባ ነው ብዬ አምናለኹ፡፡

በሺሕ ዘመን ታሪክ፣ ነፃነትና ገናና ሥልጣኔ ባለቤት የሆነችው ሀገራችን ኢትዮጵያ- ለአፍሪካ፣ ለአፍሪካ አሜሪካዉያን እና በአጠቃላይም ለመላው ጥቁር ሕዝቦች የፀረ-ቅኝ ግዛት እና የነፃነት ትግል ያደረገችው አስተዋጽኦ እጅግ ከፍ ያለ ነው፡፡ ይህ ሀገራችን ኢትዮጵያ ለጥቁር ሕዝቦች የነፃነት መራር ትግል ያደረገችው ታሪካዊ አስተዋጽኦ በተለይ አውሮፓውያንን የሃፍረት ሸማ ካከናነበው የዐድዋው አንጸባራቂ ድል በኋላ የተለየ ገጽታን ተላብሷል፡፡

የትናንትናው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ የዛሬው የአፍሪካ ኅብረት በሁለት እግሩ እንዲቆም በማስቻል የኢትዮጵያ የሺህ ዘመናት ታሪክ፣ ሥልጣኔና ቅርስ፣ የቀደሙ አባቶቻችን ጽኑና አይበገሬ የሆነው የኢትዮጵያዊነት ብሔራዊ ኩራትና መንፈስ እንዲሁም ጥቁር ሕዝቦችን ሁሉ ያኮራውና አንገቱን ቀና አድርጎ እንዲራመድ ያስቻለው፣ የዐድዋው ድል- የኢትዮጵያውያኑ የነፃነት ተጋድሎ፣ በባርነትና በቅኝ ግዛት ስር ይማቅቁ ለነበሩ ለአፍሪካ አገሮች ነፃነትና አንድነት እውን መሆን ትልቁን መሠረት ጥሏል፡፡

ይህን የኢትዮጵያንና የኢትጵያውያንን ታሪክ፣ ሥልጣኔ፣ ብሔራዊ ኩራትና የአባቶቻችንን አኩሪ የነፃነት ተጋድሎ- ለአፍሪካ፣ ለአፍሪካ አሜሪካውያንና ለመላው ጥቁር ሕዝብ የነፃነት ዓርማ፣ ከፈጣሪ ለተቸረ ሰው የመሆን ከፍ ያለ ክብር እና የመንፈስ ልእልና መገለጫ እስከመሆን ደርሶ ነበር፡፡ ይህ የኢትዮጵያውያን የዐድዋው የነፃነት መንፈስ ለመላው ትቁር ሕዝቦች በተለይ በደቡብ አፍሪካውያን የፀረ-ቅኝ ግዛትና የፀረ-አፓርታይድ ትግል ውስጥ ደግሞ የራሱ የሆነ ልዩ ታሪክ አለው፡፡

ሰላም፣ ወንድማማችነት፣ አንድነትና ኅብረት ለአፍሪካና ለአፍሪካውያን ወሳኝና ተቀዳሚ ነገር መሆኑ የተረዱት ግርማዊ ቀዳማዊ ዐፄ ኃ/ሥላሴ፣ ጸሐፌ ትእዛዝ  አክሊሉ ሀብተ ወልድ፣ አቶ ከተማ ይፍሩና አቶ ክፍሌ ወዳጆ– የመሳሰሉ ብርቅዬ ኢትዮጵያውያን አፍሪካውያን መሪዎችንና ፖለቲከኞችን በማስተባበር የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲቋቋም የላቀ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡ ታሪክና አፍሪካ ሁሌም ስማቸውን በክብር ትዘክራዋለች!!

ለአብነትም ያህል፤ የናይጄሪያው ሳንዴይ ኦብዘርቨር (ጁላይ 23፣ 1972) ባወጣው ዕትሙ፣ አዲስ አበባ ‹‹የፓን አፍሪካን መዲና›› (የአፍሪካ አንድነት ከተማ) ለመባል የበቃችበትን ምክንያት በተመለከተ ሰፊ ሐተታን አስነብቦ ነበር፡፡ በተመሳሳይም የብሪቲሹ፣ ለንደን ታይምስ (The Times London) በጁላይ 22፣ 1972 (ሐምሌ 15 ቀን 1965 ዓ.ም.) ዕትሙ፣ ‹‹የንጉሠ ነገሥት ዐፄ ኃ/ሥላሴ ጽኑ ሥልጣን በአፍሪካ መሪዎች ዘንድ ትልቅ ተቀባይነትንና ታፋሪነትን አትርፎላቸዋል፡፡›› (Emperor’s firm authority earns respect among the Leaders of Africa) በሚል ርዕስ ሐተታ አስፍሮ ነበር፡፡  

በሐሳቤ መደምደሚያም ሁላችንንም ኢትዮጵያውያንን ‘እንኳን ለአፍሪካ ቀን አደረስን!’ ለማለት እወዳለኹ፤ በአፍሪካ አንድነት ምሥረታ መክፈቻ ጉባኤ ላይ፣ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች ካደረጉት ንግግሮች መካከል አንድ ሁለቱን በአጭሩ በማካፈል ልሰናበት፡

የጊኒ ፕሬዝዳንት የነበሩት ሴኮ ቱሬ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ የመሪዎች ጉባኤ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር- ለአፍሪካ አንድነት ምስረታ ኢትዮጵያና ንጉሡ አፄ ኃ/ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽኦና ሥራ በተመለከተ ሲናገሩ እንዲህ ነበር ያሉት፡-

… ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው፡፡ ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው፡፡ ይህ በንጉሠ በአፄ ኃ/ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖችም ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል፡፡

የኢትዮጵያ ንጉሥ የነበሩትና በአፍሪካውያን ዘንድ ‘‘የአፍሪካ አባት’’ ተብለው የሚመጠሩት፣ ግርማዊ፣ ቀዳማዊ ዐፄ ኃ/ሥላሴ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ ጉባኤ ስብሰባ ላይ ባደረጉት የ’እንኳን ደህና መጣችሁ!’ ንግግራቸው እንዲህ ነበር ያሉት፡-

በዚህ በዛሬው ቀን በዚህች በዋና ከተማችን በአዲስ አበባ የዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ተካፋይ ለመሆን የመጣችሁትን የነፃ አፍሪካ አገር መሪዎች፣ ወንድሞቻችን በራሳችንና በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ስንቀበል በጣም ደስ ይለናል፡፡ ይህ ዛሬ እኛ የአፍሪካ ነፃ መንግሥታት መሪዎች የምናደርገው ጉባኤ በዓለም ላይ እስካሁን ድረስ ተወዳዳሪ የለውም፡፡ የዚህን ታላቅ ጉባኤ መደረግና የመላው አፍሪካ አገሮች መሪዎች ተካፋይ በመሆን ለዚህች ክፍለ ዓለማችን በውስጧም ለሚገኙት ሕዝቦቻችን ላለን ጥልቅ አሳቢነት ዓይነተኛ ምስክር ነው፡፡ ባጭሩ ይህ ቀን ለአፍሪካና ለአፍሪካውያን በመላ ታሪካዊና ታላቅ ቀን ነው … ፡፡

ይህን የታሪክ ማስታወሻ- የጋና የነጻት አባት፣ ዕውቁ ፓን-አፍሪካኒስት ዶ/ር ክዋሜ ንኩርማ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ ወቅት ባደረገው ንግግሩ ላጠቃልል፤

Ethiopia is a great people, an African people that have fought bravely for the independence of Africa, for their preservation of freedom and the normal exercise of the right of our peoples to guide their destiny with no foreign control or interference and to manage their own affairs in full sovereignty…. because of this African conference is being held in the Ethiopian capital, Addis Ababa and Ethiopia have become still more closely linked with African history; they are henceforth in the midst of this the unbroken course of events and facts that are consciously induced and guided by the people of a whole continent in a manner consonant with the understanding of affairs and their desire for progress. Ethiopia shall soon stretch out her hands unto God. Africa must unite!

Filed in: Amharic