>

የነዳንኤል ክብረትና የኔ - ሁለት አቢይ አህመዶች! (ዳግማዊ ጉዱ ካሣ)

የነዳንኤል ክብረትና የኔ – ሁለት አቢይ አህመዶች!

 

ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

 

የጠ/ሚ ዶ/ር አቢይ ምስል በኔ አእምሮ ውስጥና በፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እንዲሁም በሙሃዘ ጥበባት ዳንኤል ክብረት አእምሮ ውስጥ የሰማይና ምድርን ያህል ልዩነት ማሳየቱ ትልቅ ምሥጢር ሆኖብኛል፡፡

ዶ/ር አቢይ በመጀመሪያ አካባቢ የኢትዮጵያ ሙሤ ሆኖ ይታየኝ ነበር – ይህን አልክድም፡፡ እየቆዬ ግን ተገለበጠና ለኢትዮጵያ ጥፋት ከአጋንንቱ ዓለም የተላከ ያህል ይሰማኝ ጀመር –  ይህም እውነት ነው፡፡ አሁን ዓለምን እያተረማመሷት የሚገኙት የኮረና ቫይረስ አምራች የኢሉሚናቲ ኩባንያዎች ኢትዮጵያን በቁጥጥራቸው ሥር ለማስገባት በቅድሚያ መለስ ዜናዊን ተጠቀሙ፡፡ ሲበቃቸው እርሱን አስወገዱትና ይህን ብላቴና አራት ኪሎ አስገብተው በአዲስ ጉልበት ሀገራችንን ማውደም ተያያዙ፡፡ “አውቆ የተደበቀ ቢጠሩት አይሰማም” እንዲሉ ሆኖ ለነዳንኤልና ብርሃኑ ቢሠወርባቸውም ለብዙዎቻችን ግን ይህ ገሃድ እውነት በጣም ግልጽ ነው፡፡ 

ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በወዲያኛው ሰሞን “የአቢይን ያህል ኢትዮጵያን አልወድም” ዓላማው ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ ሲያሞካሸውና በዚህኛው ሰሞን ደግሞ ሙ.ጥ ዳንኤል ትናንትና ማታ በደረጀ ኃይሌ ፕሮግራም እንግዳ ሆኖ ዕንባ እስኪያቀር ድረስ ያንኑ የፕሮፌሰር ብርሃኑን ቃል – ከሞላ ጎደል ቃል በቃል መድገሙን ስታዘብ እነሱ የተረዱትን አቢይ እኔ በነሱ የአረዳድ አቅጣጫና መጠን ባለመረዳቴ ራሴን ታዘብኩት፡፡ ችግሩ የኔ እንደሆነ እስክጠራጠር ድረስ ተጨነቅሁ፡፡ “ይህ ናርሲሲስት ፀረ-አማራ ጠ/ሚኒስትር እኔ ያላየሁለትና እነሱ ተረድተውለት ከነሱም በላይ በኢትዮጵያዊነቱ እንዲገዝፍ ያስደረጋቸው ተዓምር ምን ይሆን?” ብዬም ብዙ አሰብኩ፡፡ ደጋግሜ በሃሳብ ብወጣ ብወርድም አልከሰትልህ አለኝ፤ የገባችሁ እንድታስረዱኝ እለምናችኋለሁ፡፡

ብዙ ነገሮች አንጻራዊ መሆናቸው ይገባኛል፡፡ ሺህ ጊዜ አንጻራዊ ይሁኑ እንጂ ግና ትግራይ ከነወንጀለኞቿ ልክ እንደ አንድ ነፃ ሀገር እንደልቧ እንድትፈነጭ ያደረገ፣ አማራ ግን ሁለት ሽህ ሚሊሺያ እንኳን ሲያሰለጥን ዐይኑ ደም የሚለብስና በሌላ በኩል ደግሞ ኦሮሞ በያንዳንዱ ዙር በአሥር ሽዎች የሚቆጠር ዘመናዊ ጦር ለ30 እና 40 ጊዜ እያሰለጠነ ማስመረቁን ለማስፈራሪያነት ጭምር በሚዲያ ሲያስታውቅ በደስታ ተውጦ ዝም ያለ፣ ንጹሓን የአማራ ተማሪዎች ከአራት ወራት ለበለጠ ጊዜ በአክራሪ ኦሮሞ ሽፍቶች ታግተው ሳለ “ራሳቸውን በራሳቸው ያገቱ ሰዎችን ፈልጎ ማግኘት አይቻልም” ብሎ በዜጎች ያላገጠ፣ የአማራን ምርጥ ምርጥ አመራሮች በልዩ ሥልት ገድሎ ወይም አስገድሎ የአንድን ትልቅ ክልል አመራር በራሱ ሰዎች የተካና አማራን ለማጥፋት ቆርጦ የተነሣ፣ ጃዋራዊ ቄሮን አጠገቡ አስቀምጦ ሀገርን በቋንቋና በጎጥ እየበለተ ሳለ ጎንደር ውስጥ አደብ ገዝቶ የተቀመጠን ፋኖ ሊያውም ኮሮና ቫይረስ ዓለምን የስንግ ይዞ በሚያስጨንቅበት በአሁኑ ሰዓት ካላጠፋሁ ብሎ የፌዴራል ጦር ያዘመተ፣ የፌዴሬል መንግሥት ተብዬውን መሥሪያ ቤቶች ከሞላ ጎደል ሁሉንም የኃላፊነትና ጥቅማ-ጥቅም ቦታዎች በኦሮሞ ነገድ አባላት ካለ(በቂ) ችሎታና ካለውድድር ያቃረጠና እያቃረጠ ያለ እስስትና ይሉኝታቢስ ጠ/ሚኒስትር በዚህ መልክ አጋንኖ መግለጽ መልስ የሌለው ክፍለ-ዘመናዊ ዕንቆቅልሽ ነው፡፡ ሀገር ላይ የደረሰውና እየደረሰ ያለው የዚህ ሰው በደል ተዘርዝሮ እንደማያልቅ አስምሬበት ማለፍ እወዳለሁ – አንዳንድ ትያትራዊ ተግባራቱ ከሚፈጽማቸው መሠረታዊ እንከኖቹ ጋር ሲወዳደሩ ቅቡልነትን ለማግኘትና ሤራውን አጠናክሮ ለመቀጠል ከመርዳት ባለፈ ሚዛን የሚደፉ አይደሉም፡፡ ለምሣሌ እስረኛን ማስፈታትም ሆነ መፍታት ዓላማው ለታይታና ለፕሮፓጋንዳ አለፍ ሲልም ለሌላ እስረኛ ቦታ ማስለቀቅ እስከሆነ ድረስ በደስታ እምቢልታን የሚያስነፋ አይደለም፡፡ ለማንኛውም…. ይህን ሁሉ ወንጀል የሚሠራ ግለሰብ ማፍቀርና በዕንባ እየተራጩ “ዘላለማዊ ክብርና ሞገስ ለጠ/ሚኒስትራችን!” ማለት አልገባህ ብሎኛልና የገባችሁ አስረዱኝ፡፡ ይህ ሁሉና ከዚህም የከፋ ወንጀል በፌዴራል መንግሥት ተብዬው እየተፈጸመ ሳለ የፕሮፌሰር ብርሃኑ ሚዲያዎች በስማም እንደተባለበት ሰይጣን ጭጭ ብለዋል፡፡ ምሣሌ ካስፈለገ ኢካድፎረም የተባለው ድረገጽ የቆመበትን ቀንና ሰዓት ማየት በቂ ነው፡፡ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን የማይገቡን ወቅት ላይ ደርሰናል፡፡ ይህን ዕንቆቅልሽ የሆድ ነገር እንዳልለው እነዚህን ሰዎች በሆድ ማማት ይቸግረኛል፡፡ የሥልጣን ነገር እንዳልለውም በተለይ ዳንኤል ከንግግሩ እንደተረዳሁት ለሥልጣንና ለገንዘብ ጥዩፍ መሆኑን ከራሱ አንደበት ሰምቻለሁ፡፡ ምናልባት አንዴ ስለወደዱት የዚህን ሰውዬ ዕድፍና ጉድፍ ላለማየት በካፈርኩ አይመልሰኝ ተጠርንፈው እንደሆነ ሰጋሁ፡፡ ይህም በሽታ ነው፡፡ እንጂ ብርሃኑ አቢይን ስለወደደና ዳንኤልም ስላመለከው ችግራችን እንደጪስ በንኖ ይጠፋል ማለት እንዳልሆነ እነሱና እኛ ብቻም ሳንሆን ታዛቢም ሳይቀር በተግባር እያየን ነው፡፡ የእውነት አምላክ ግን ፍርዱን ይስጥ፡፡ በውነቱ ይህ ዘመን ብዙ ጉድ እያሳየን ነው፡፡

Infatuation እና/ወይም calf love (calf’s love) የሚባሉ የእንግሊዝኛ ፈሊጦች አሉ – እነዚህን አባባሎች ሳልጠቅስ ጅምሬን መቋጨት አልፈልግም፡፡ በኛም በአንድ ፈሊጣዊ አገላለጽ “የወረት ፍቅር” ልንላቸው እንችላለን፡፡ ልክፍት እንጂ ምክንያታዊነት የላቸውም፡፡ አንድ ሰው በቂ ምክንያት ሳይኖረው ወይም እንዲኖረውም ሳይፈልግ እንዲሁ አንድን ሰው የሚያፈቅርበት ወይም የሚወድበት ሁኔታ ከተፈጠረ በዚህ ፈሊጥ ይገልጻል፡፡ በዚህ መልክ ያፈቀርከውን ሰው ወደኅሊናህ ስትመለስና ፍቅርህን ስታጤነው ልክ እንዳልነበርክ ይከሰትልህና ልታፍር ትችላለህ፡፡ … ለማንኛውም የአቢይን ጠንካራ ጎን እኔም እንደነሱው ባወቅሁና ተፀፅቼ ንስሃ በገባሁ፡፡ እነዚህ ሰዎች በዚህ ሰው የተመሰጡበትንና አደባባይ የተሰጣውን የሰውዬውን ገመና አስረስቶ ከኢትዮጵያዊነት አንጻር እንደዚህ ከራሳቸው አሳልፈው ሰማየ ሰማያት የሰቀሉበትን አመክንዮ ባውቅ ደስ ባለኝ፡፡ አሁንም ልድገመው – የገባው ካለ ቢነግረኝ ምሥጋናየ ወደር አይገኝለትም፡፡ 

የኢትዮጵያ አምላክ ከሰው ሠራሹ የኮሮና ቫይረስ ይጠብቀን፤ከምሥኪኑ የዓለማችን ሕዝብ ራስ ወርዶ በሠሪዎቹ በራሳቸው ላይ ንግሥናውን ያሳይ፡፡ ጦርነቱ በራሳቸው ሜዳ ይለቅ፤ አሜን ነው! አሜን፡፡   

Filed in: Amharic