>

አድዋና የህዳር በሽታ....!!! (በእውቀቱ ስዩም)

አድዋና የህዳር በሽታ….!!!

(በእውቀቱ ስዩም)
* ጀግንነት ማለት የእሳት ራት መሆን አይደለም፤ ጀግንነት  ከጠላትህ ጋር መጋፈጥ በሚገባህ ሰአት መጋፈጥ፤ መሸሽ በሚያዋጣህ  ሰአት መሸሽ ነው!
—-
በአድዋ ጦርነት ዘመቻ  ታውጆ  ፤ ሰራዊቱ  ወደ ሰሜን ሲዘምት፤   በትውልድ ግብጣዊ፤ በሙያ የኢትዮጵያ  ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት አቡነ ማቴዎስ  ቀሳውስትን መርተው፤ የማርያምን ታቦት አስይዘው ወደ ጦርሜዳ   ዘምተዋል፤ ለወታደሮች ወኔና መንፈሳዊ ብርታት ለግሰዋል!  እየሸለሉም ባይሆን እየቀደሱ ተመልሰዋል ::
ቆይቶ ቆይቶ…
ዘመን አልፎ ዘመን መጥቶ…
  በንግስተ ነገስታት  ዘውዲቱ ዘመነ መንግስት የኮሮና ታላቅ ወንድም የሆነው የህዳር በሽታ፤  ወደ አገራችን ገብቶ ብዙ ህዝብ ፈጀ፤ የእልቂቱ ዝርዝር ውስጥ አልገባም፤   “ በዘውዲቱ  ሬሳ ጎትቱ “ የሚለው ያማርኛ ፈሊጥ ነገሩን ጠቅለል አድርጎ ይገልፀዋል፤
   በጊዜው  አቡነ ማቴዎስ   ሁኔታውን በቅርብ ርቀት  ሰለሉት፤   ወረርሽኙ በትንፋሽ  እንደሚተላለፍ ባነኑ ፤  አጅሬው ቫይረስ እንጂ ብኤልዘቡብ ወይም ጄኔራል አልበርቶኒ አይደለም:: እና  ሊሳፈጡት አልሞከሩም ፤ በቅሎቸውን ኮልኩለው ፤ ወደ መናገሻ ተራራ ስልታዊ ማፈግፈግ አደረጉ ::
 በርግጥ በጊዜው መንፈሳዊ ልጆቻቸውን በትነው መሸሻቸው ትክክል ነበር  አይደለም የሚለው ሊያከራክር ይችላል ፤ ግን ራስን አድኖ ሌላውን ከማዳን  ጥበብ  አንፃር  ከመዘንነው አቡኑ ያደረጉት ትክክል ይመስለኛል ፤ ቢያንስ ለተጨማሪ አመታት በህይወት እንዲኖሩ አድርጉዋቸዋል፤ ለሌላውም ጠንቅ ከመሆንም ታቅበዋል፤
  ጀግንነት ማለት የእሳት ራት መሆን አይደለም፤ ጀግንነት  ከጠላትህ ጋር መጋፈጥ በሚገባህ ሰአት መጋፈጥ፤ መሸሽ በሚያዋጣህ  ሰአት መሸሽ ነው፤
Filed in: Amharic