>

ዳግማዊ ዐጤ ምኒልክ — ጥቁሩ የነጭ ጌታ (አቻምየለህ ታምሩ)

ዳግማዊ ዐጤ ምኒልክ — ጥቁሩ የነጭ ጌታ

አቻምየለህ ታምሩ
የአምባላጌውን ምሽግ ሰባሪው የጎጃሙ አርበኛ  ራስ ቢትወደድ መግገሻ አቲከም
 
የማንነት ቀውስ ዋግ እንደመታው አገዳ ያኮሰሳቸው ናዚ ኦነጋውያንና ፋሽስት ወያኔዎች፣ የበታችነት ሥነ ልቦናቸው ታሪክን በማርከስና የዓለም ጀግኖችን በመዝለፍ የሚሽርላቸው እየመሰላቸው፣ ሕዝባችን የሚሉትን የኅብረተሰብ ክፍል  በዘመናቸው በድቅድቅ የባርነት ጨለማ ውስጥ ከተውት  እንዳይተነፍስ ነጻነቱን አፍነው አሳሩን እያሳዩት፤ ይህንን ለመለወጥ ጣምራ ትግል  እንዳያደርግ ደግሞ  ያለዘመናቸው ወደኋላ ተጉዘው ስላልኖሩበት ዘመን ፖለቲካ የወለደውን የኃጢአት ክስ እየነዙ የዳግማዊ ምኒልክን ስም በማክፋት በእየለቱ ሲያላዝኑ ይውላሉ። ወይን ጠጁ ምኒልክ ግን እያደረ ጣማቸው እየጨመረ በመሄድ ላይ ይገኛል። ጎሰኞቹ ግን በዘመናቸው ዐይናቸው እያየ ከሚፈጸመው በደል ይልቅ ከ140 ዓመታት በፊት ተደረገ ተብሎ በተረት አባቶቹ በነ ተስፋዬ ገብረአብ የተደረሰውን ወሬ ሳያጣሩ እያመኑ፣ የሚያዩትን ግን ማስተዋል ተስኗቸው ያለዘመናቸው ለድንጋይ ዘመን ሰውነት እንኳ አንሰው ይገኛሉ።
ተረት የወለደው አርቲቡርቲ ተጭኗቸው ነገን ሳይኾን ዘወትር በትናንትና ለመኖር የሚያተጋቸው የተወናከረ ፖለቲካቸው እና የተኮላሸው የዛሬ ተግባራቸው ትናንትና ‹ተበድለናል› ከሚሉት በላይ ሕዝባችን ለሚሉት የዛሬው ሞቱን እያቀላጠፉለት መኾኑን ግን ገና የተገነዘቡት አይመስልም። እነዚህ የጥላቻ ብሔርተኞች፣ የነጻነትን ብርሃን፣ የዘመናዊነትን ጎዳና፣ የአንድነትን መሠረት ከወራሪና ከተስፋፊ ቅኝ ገዢ አውሮፓውያን ጋር በብርቱ ታግለው የክብርን አክሊል፣ የኩራትን መንፈስ ያወረሱንን ደጋጎቹን አያቶቻችንንና ታላቁ መሪያቸውን ዳግማዊ ምኒልክን በማንጓጠጥ ስለደከሙና ሀገራችንንም ገዝግዘው ስለጣሏት ዛሬ በዓለም ላይ በስደት፣ በርሃብና በውርደት እንድንታወቅ ባደረጉን ፋሽስት ወያኔና ናዚ ኦ.ነ.ግ ከፈጸሙብን ጭካኔ በላይ ክፉት ሀገራችን ያስተናገደች ይመስል በተለይ ከዐማራ ወገን እውነት በተነገረ ቁጥር የድሮ ወደሚሉት ሥርዓት ለመመለስ የተደረገ አስመስለው በማቅረብ ሊያሸማቅቁበት ይሞክራሉ።
በዚህ የሰለጠነ ዘመን በተጫናቸው ባሪያ አሳዳሪ ፋሽስታዊ አገዛዝ ላይ ድል መቀዳጀት ያልቻሉ ደካማና ልፍስፍስ የጥላቻ ግብረ ኃይሎች ሁሉ ጀግኖች አያቶቻችንን ለመዝለፍ ሲንጠራሩ ይበልጥ እየተዋረዱ መኾናቸውን እንኳ አለመረዳታቸው የሚያስገርም ነው። ያለፈውን ታሪክ ስኬት እንደመነሻ አድርጎ ከዚያ በላይ ለመሥራት መነሣት የማይፈልግ ትውልድ፣ ባለፈው ትውልድ ብቻ ሳይኾን በራሱ ትውልድ ታሪክም ሲያፍር የሚኖር ነው። የዳግማዊ ምኒልክ ጥላቻ ርእዮተ ዓለማቸው የኾነ የርስ በርስ መተላለቅ ነጋሪት ጎሳሚዎችና የጥላቻ ዶክተሮች ፖለቲካ የሚፈጥረው ትውልድ ግን የሚያፍረው ባለፈው ትውልድና በራሱ ትውልድ ታሪክ ብቻ ሳይኾን የወደፊቱንም ትውልድ እጀ ሰባራ አድርጎ በታሪኩና በሀገሩ ሲያፍር እንዲኖር የሚያደርግ ነው።
ተወደደም ተጠላ ዳግማዊ ምኒልክ ወደፊትም ለማግኘት የሚያዳግቱ፣ በታሪክም ያልታዩ የመላው ጥቁር ዓለም ክስተት ናቸው። በካድሬዎቹ ‹ታላቁ መሪ› እየተባለ ሲሞካሽ የኖረው መለስ ዜናዊ በቢሊዮን ዶላር የውጭ ርዳታና ብድር እየጎረፈለት፣ ከሌላው ዓለም ሊያገኘው የሚችለውን ‹ሥልጣኔ› ሁሉ እያገኘ ማድረግ ያልቻለውን ነገር ዐጤ ምኒልክ ግን በጠላት ተከበው፣ ከግራ ከቀኝ የሚመጣባቸውን ጠላት በትከሻ፣ ባህያና በበቅሎ የተያዘ በሶ፣ ቆሎና ጥሬ እየበሉ፤ በወጣ ገባና አስቸጋሪው የሀገራችን መልክአ ምድር እየተንገላቱ፤ ተበታትኖ ይኖር የነበረውን ሕዝብ ከነበረበት የአስተሳሰብ አድማስ (Paradigm) አውጥተው ወደ አዲስ የአስተሳሰብ አድማስ (New Paradigm) በማስገባት ለኑሮ አስፈላጊ የኾነውን ነገር ሁሉ በሀገራቸው ውስጥ ሰርተውና አሰርተው ራሳቸውን ችለው በመኖር በሰላምና በአንድነት የቆመች ታላቅ ሀገር መመሥረት ችለዋል።
ድሮ፣ ያኔ ድሮ፣ ይህ የታያቸው አለቃ ገበረሃና ራሳቸው ‹ገብረሃና ሞቷል› ብለው ቤተ መንግሥት ወሬው እንዲወራና ለተዝካራቸው ማውጫ የሚኾን ጠገራ ብር ዐጤ ምኒልክ ወደ ትውልድ መንደራቸው ናበጋ ጊዮርጊስ እንዲልኩ ካስደረጉ በኋላ፣ ጠገራ ብራቸውን ጨርሰው ወደ ምኒልክ ቤተ መንግሥት በመምጣት እጅ ነስተው ሲቆሙ «ምነው አለቃ ሞተሀል አልተባለም?» ብለው ዳግማዊ ምኒልክ ቢጠይቋቸው «ጃንሆይ በሞትሁበት ሰማይም ኾነ በኖርሁባት ምድር እንደ ምኒልክ የሚሆነኝ ሰው ባጣ ተመልሼ መጣሁ» ሲሉ መለሱላቸው አሉ። ዳግማዊ ምኒልክም ስቀው «የአንተ መላ ወትሮስ መቼ ጠፋን» ብለው መሽቶ ኖሮ ወደ ግብር ቤታቸው አመሩ። አለቃም እዚያው ታድመው አመሹና አዝማሪዋን «ተቀበይ» በማለት የሚከተለውን ውስጠ ወይራ ሁለት ዘለላ ግጥም በማፍሰስ ‹ሞቷል› ካስባሉ በኋላ ‹ሄደው ባዩት› ዓለምም ኾነ ከዚያ በፊት ምድር ላይ እንደ ምኒልክ የሚኾናቸው ሰው እንዳጡ እንዲህ መሰከሩ፡-
ምንሊክ መጓዙን የምትጠይቁኝ
ፊትም አላለፈ ኋላም አይገኝ!
አለቃ እውነት አላቸው። ጥቁሩ ሰው ዳግማዊ ምኒልክ ነጭን ድል በመንሳት የነጭ ጌታ የኾኑ የምድሪቱ ብቸኛው ጥቁር ንጉሠ ነገሥት ናቸው። ከዚህ በተጨማሪ ዳግማዊ ምኒልክ አሸንፈው ብቻ ሳይኾን ተሸንፈውም ማሸነፍ የሚችሉ ብልህ መሪ ነበሩ። ይህ የዐጤ ምኒልክ የአእምሮ የበላይነት ነው እንግዲህ የዝቅተኝነት ስሜትና ጥላቻን ቀስቅሶ ለኦ.ነ.ግና ለወያኔ ፖለቲካ የኾነው። ዐጤ ምኒልክ ማንንም ሳያስገድዱ በብልህነታቸውና በሩኅሩኅነታቸው ብቻ በሕዝባቸው ዘንድ እምዬ ተብለዋል። የምኒልክን ሩኅሩኅነት ወዳጆቻቸው ብቻ ሳይኾኑ ተቃኞቻቸውና ጠላቶቻቸው ፈረንጆችም አይተውታል።
ተቀናቃኞቻቸው ዐጤ ቴዎድሮስ ሸዋን እንዲገዙ የሾሟቸው በዛብህ አባ ድክር፣ የወላይታው ገዢ ካዎ ጦናና የጎጃሙ ንጉሥ ተክለሃይማኖት የምኒልክ ሩኅሩኅነት ደርሷቸዋል። ይህ የዳግማዊ ምኒልክ የአእምሮ ኃይል የበላይነት፣ የዝቅተኝነትና የጥላቻ ስሜት የቀሰቀሰባቸው ወያኔና ኦ.ነ.ግ ግን የኒህን ታላቅ ሰው አሻራ ሊያጠፉ አብረውት ያልተሰለፉት የኢትዮጵያ ጠላትና ዳግማዊ ምኒልክ በሕይዎት ሳሉ ድባቅ ያልመቱት የውጭ ጠላት የለም። ታሪካቸው ይሰረዝ ዘንድም ብራና ፍቀው ቀለም በጥብጠው በጥላቻ ሞተር እየተነዱ ዘመቱባቸው፤ የጥላቻ ሐውልት አቆሙባቸው፤ ስማቸው እንዳይነሳም የሚያስቀስፍ እግድ ጣሉ።
የአያቶቹን እውነት አላስቀብር ያለው ከያኒው ቴዎድሮስ ካሣሁን ግን አስታዋሽ ነውና ከኦ.ነ.ግ ‹ምኒልክ ሂትለር ነው› እስከ ወያኔ ‹ምኒልክ ቅኝ ገዢ ነው› ድረስ ለተጎሰመው የጥላቻ ነጋሪት ዘመን በማይሽረው «የጥቁር ሰው»ዘፈኑ. . .
ኢትዮጵያ ሀገሬ የአፍሪካ መገኛ ናት፣
የነጻነት አርማ የሉዓላዊነት፤
ያናብስቶች ምድር የአርበኞች ተራራ፣
በዓለም አደባባይ ግርማሽ የተፈራ፤
የጥበብ ምልክት የፍቅር ማደሪያ፣
ኑሪ ለዘላለም ቅድስት ኢትዮጵያ፤
ዳግማይ ምኒልክ፣ ዳግማይ ምኒልክ፣
ምኒልክ፣ ምኒልክ፣ ዳግማይ ምኒልክ…
ሲል በይፋ የዳግማዊ ምኒሊክን የሀገር ባለውለታነት ታሪክ ጠቅሶ ተከራከረ።
ቴዎድሮስ ካሣሁን ይህንን የዳግማዊ ምኒልክን ዘመን የማይሽረው ታሪክ በመመስከሩ ብዙ እንግልትና ስቃይ ደርሶበታል። ስለ ዳግማዊ ምኒልክ በመዝፈኑ በችሎታው ያገኝው የስፖንሰርሺፕ ስምምነት በአክራሪ የኦ.ነ.ግ ፕሮግራም አቀንቃኞች ጫጫታ ምክንያት ስምምነቱ ፈርሷል፤ ካገር እንዳይወጣ ታግዶ የውጭ ሀገር ትርዒቶቹ ተሰርዘውበታል፤ በሀገር ውስጥም ሊያቀርባቸው ያዘጋጃቸው አውደ ሙዚቃዎች ፍቃድ ተነፍጓቸዋል። ይህንን ሁሉ መስዕዋትነት የከፈለው እንደ ፋሽስት ወያኔ ድሀ እየመተረ፣ እርጉዝ እየገደለ ሀገር ስለዘረፈ አይደለም። ቴዎድሮስ ካሣሁን ይህንን ሁሉ መስዕዋትነት የከፈለው የአያቶቹን እውነት አላስቀብርም ብሎ የዳግማዊ ምኒሊክን የሀገር ባለውለታነት የሻረውን የወያኔንና የኦ.ነ.ግን የተባበረ ፕሮፓጋንዳ ብቻውን ደምንሶ ከመቶ ሀያ ዓመታት በፊት የኾነውን ያንን የመላው ጥቁር ሕዝብ ታላቅ ገድል ዛሬ የኾነ ያህል እንዲሰማን የሚያደርግ መንፈስ የመጫን ኃይል ያለው ድንቅ የዘፈን ክሊፕ በታሪክ ምንጣፍ ላይ በመቅረጹ ነው።
የጎሳ ፖለቲከኞችና የአፓርታይድ አራማጆች ምኒልክን ማውገዝ ከተዉ ፖለቲካ ማቆማቸው ስለኾነ፣ እውነቱን ቢያውቁም ስለማይጠቅማቸው፣ ምንም ነገር ማገናዝብ ባይፈልጉ ባያስፈርድባቸውም በነሱ የሚዘወረው ወጣትና የፈጠራ ትርክታቸው ሰለባ የኾነው ወገን ግን ዳግማዊ ዐጤ ምኒልክን የሚያወግዙ የዘር ፖለቲከኛ ነጂዎቹ እንዲያገናዝብ የማይፈቅዱለትን የሚከተሉት ዐሥር ነጥቦች ማወቅ ይኖርበታል፡-
አንደኛ፡-
ከመቶ በላይ የነበረውን የተበጣጠሰ ነገድ ቀድመው በዘመኑ ይሠራበት በነበረው በኃይልም ኾነ በዘመኑ ሥራ ላይ ባልዋለው በዲፕሎማሲ ባንድ ጥላ ሥር ባያሰባስቡት ኖሮ ቅኝ ገዥዎች እየነጠሉ ሁላችንንም ቅኝ ይገዙን እንደነበረ አለማሰብ የዓለምንና የአፍሪካን የታሪክ ሀ ሁ አለማወቅ ነው፡፡
ሁለት፡-
በዋናነት በሸዋ አማሮች፣ በሸዋ ኦሮሞዎችና በሸዋ ጉራጌዎች የሚመራው የዐፄ ምኒልክ ጦር እንደ ነጭ ወራሪ በቀለም ልዩነት የዘር ግንብ የሚገነባ ሳይኾን አንድ ካደረገው ወገኑ ጋር እንደ አንድ ሕዝብ መንደር መስርቶ፣ በየአካባቢው የሚነገሩ ቋንቋዎችን ተላምዶ፣ ለጠባቡ ክፍለ ሀገር ሕዝብ ሰፊ ሀገር ፈጥሮ፣ ሁሉንም የሀገሪቱን አካባቢዎች ሀገሬ ብሎ ኗሪ መኾኑንና በዚህም የተነሣ ዛሬ ሁሉም የኢትዮጵያ ነገዶች ተወላጆች በነጮች ፊት ቀና ብለው እንዲሄዱ ማስቻሉን ለመረዳት አለመፈለግ የእውቀት ጾመኛ ኾኖ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ መኖር ነው፡፡
ሦስት፡
ዳግማዊ ምኒልክ ያስገበሯቸው ግዛቶች እንደ ሀገር ኅልውና ያልነበራቸው፣ ከጥንት ጀምሮ የኢትዮጵያ ግዛት ኾነው ሲገብሩ የኖሩና እሳቸውም በዘመናቸው መልስው ወደ ግዛታቸው ጠቀለሏቸው እንጂ በቅኝ ግዛት ያዟቸው የሚለው ትረካ የፈጠራ ወሬ እንደኾነና አንዳችም የቅኝ ግዛት ማሳያ በኢትዮጵያ ውስጥ አለመከሰቱን አለማገናዘብ ታሪክ አለመማር ብቻ ሳይኾን የታሪክ ደጅ አለመድረስ መኾኑን፤
አራት፡-
የስኬት ጉዳይ እንጅ መጠቅለል የሁሉም ነገድ የጎበዝ አለቆች ፍላጎት እንደነበረ ለመረዳት አለመፈለግ፤ መስፋፋት እንደ ኦሮሞ፣ ሲዳማ፣ ወላይታ ዓይነት ነገዶች ምኒልክ ኢትዮጵያን እንደገና አንድ ካደረጉ በኋላ እስከ 1966ቱ ዐቢዮት የቀጠለ የማኅበረሰብ ጠባይ እንደነበር አለመገንዘብ፤
አምስት ፡-
በተለይ የኦ.ነ.ግ ፕሮግራም አቀንቃኞች፣ ኦሮሞ ከሰላሳ በላይ ነገዶችን ማንነት፣ ባህልና ቋንቋ የዋጠበትን ሥርዓት በደግ እያነሱ እንደ ዋርካ ተስፋፍተው እየኖሩ ‹ምኒልክ ማንነታችንን አጥፍተዋል› ሲሉ የሚያቀርቡት የፈጠራ ክስ መንታ ሚዛን (double standard) እና ፈጠራ መኾኑን ለማጤን አለመቻል፤
እንደውም እዚህ ላይ ዐጤ ምኒልክ መወቀስ ካለባቸው ወደ ደቡብ በዘመቱበት ወቅት ከጥንት ጀምሮ የኢትዮጵያ መሬትና ሌሎች ሕዝቦች ይኖሩበት የነበረውን የደቡቡን የአያቶቻቸውን ሀገር መልሰው አንድ ለማድረግ ሲዘምቱ ከዘመቻቸው ሁለትና ሦስት መቶ ዓመታት በፊት ኦሮሞ ሌሎችን ገድሎና አጥፍቶ በመስፋፋት የያዛቸውን የሌላ ነገዶች አካባቢዎች የኦሮሞ ይዞታ አድርገው ማጽናታቸውና በሌሎች ነገዶች ላይ ኦሮሞን ገዢ አድርገው መሾማቸው ብቻ ነው።
ስድስት፡-
የንጉሥ ምኒልክ ዘመን የመጠቅለል፣ የመገበርና የማስገበር እንጅ የሪፈረንደም ዘመን አለመኾኑን ከሰለጠኑት ከጀርመኑ ቢስማርክና ከጣልያኑ ጋሪባልዲ ታሪክ ለመማር አለመቻል ሌላው የመሀይምነታቸውን ጥግ ማሳያ ነው፤
ሰባት ፡-
በነጮች የተገዙትን እነ ሶማሊያና ሩዋንዳን እያዩ ምኒልክ ከሚገዛን በነጭ በተገዛን ብሎ መመኘት ዓለምን ያለማወቅ ያህል ድንቁርና መኾኑን አለመገንዘብ፤
ስምንት፡-
በምኒልክ አስተዳደር ውስጥ የነበሩ የሌላ ነገድ አባላትን ተሳትፎ በማሳነስ ሀገር አንድ የማድረጉን ዘመቻ እና አስተዳደሩ የአንድ ነገድ ብቻ እንደነበረ ማስመሰል፣ ሌላው ቢቀር እምባቦ ላይ ዳግማዊ ምኒልክና ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት በተጋጩ ጊዜ የጅማ፣ የወለጋ፣ የሸዋ ኦሮሞና ጉራጌ የተባበረ ጦር ጎጃምን ወግቶ እንደነበር እንኳ ለማስታወስ አለመፈለግ ኅሊና ያላቸውን ታዳጊዎች ግንዛቤ መናቅ መኾኑን አለመገንዘብ፤
ዘጠኝ፡-
የንጉሥና የባላባት አስተዳደር በሁሉም ነገዶች ዘንድ ይሰራበት የነበረ መኾኑ ተዘንግቶ ምኒልክ ከአዳም በኋላ እንዳመጡት አድርጎ ማስቀመጥ እንደማይገባ፣ ለዚህ ምሳሌ የሚኾን የከፋው ንጉሥ ጋኪ ሼሮቾ ከምንሊክ ጦር ጋር ለመዋጋት በተቃረቡበት ወቅት በምሥራቅ አፍሪካ ኡጋንዳ ተቀማጭነት የነበረው የእንግሊዝ ወታደሮች አዛዥ ለከፋው ንጉሥ ድጋፍ ሊያደርግላቸው ሲጠይቃቸው የሰጧቸው መልስ ነው። ጋኪ ሼሮቾ ለእንግሊዙ ወታደራዊ አዛዥ ሲመልሱ፣ እርዳታውን እንደማይፈልጉ በመግለጽ «እሱ ካሸነፈኝ ሀገሩን ጠቅልሎ ይገዛል፤ እኔ ካሸነፍኩት ደግሞ የሱን ሀገር እጠቀልላለሁ» ካሉ በኋላ «ይህ የርስ በርስ ውጊያ ነው፤ ባይኾን ከባህር ማዶ ለሚመጡት መዋጊያ ትረዳናለህ» በማለት ለወቅቱ የምሥራቅ አፍሪካ የእንግሊዝ ወታደራዊ አዛዥ መልሰውታል። የዛሬዎቹ የጥላቻ ዶክተሮችና ፕሮፌሰሮች ግን በዚያ ዘመን ጋኪ ሼሮቾ የነበራቸውን ዓይነት ቅንነትና እውነት የላቸውም።
ዐሥር፡-
ምኒልክ በአሁኑ ደቡብ እና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ያደረጉት የግዛት ማስመለስ ዘመቻ ከሰሜን ሕዝቦች ጋር እንዳደረጉት ሁሉ ግዛት ከማስፋት በቀር ሌላ ዓላማ እንደሌለው እየታወቀ ጦርነቱ ዘር ለማጥፋት እንደተደረገ ማስመሰል፤ ለዚህም ደግሞ የጥንቱን ትተን የቅርቡን እንኳ ብንወስድ የኢትዮጵያ ክልል ከምድር ወገብ 3° እስከ 18°፣ ከግሪንዊች ሜሪዲያን ከ33° እስከ 48° በመለስ ሲኾን ይህም ክልል የኢትዮጵያ መሬት ኾኖ የተከለለው ኢትዮጵያን ከ1314-1344 ዓ.ም. በገዙት በአጼ አምደ ጽዮን ዘመን መኾኑን አለማወቅ ናቸው።
ከዚህ በተጨማሪ በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከ20 በላይ ባንክ የዘረፉና አርሲ ላይ በአደባባይ ንጹሐንን ዘቅዝቀው የሚሰቅሉ ጎሰኞች ዳግማዊ ምኒልክን ሊያስወቅ የሚያስችል የሞራል ልዕልና እንደሌላቸው፣ ከሚከተላቸው መንጋ እውነት የሚናገር ደፋር የኅሊና ሰው መጥፋቱ የዘር ማጥፋት ወንጀል ባገራቸው ተፈጽሞ እንዲታይ የራሱን አስተዋጽዖ አድርጓል።
በግፍ ዙፋኑ ላይ ተንፏሎ ለ27 ዓመታት የኖረው ወያኔም በቢሊዮን ዶላር የውጭ ርዳታና ብድር እየጎረፈለት፡ ከሌላው ዓለም ሊያገኘው የሚችለውን ሥልጣኔ ሁሉ እያገኘ፣ ሀገር ማስተዳደር ሲያቅተው፤ የርእዮተ ዓለም ወንድሙን ኦ.ሕ.ዴ.ድን በአንቀልባ አዝሎ የዐጤ ምኒልክን ውርስና ቅርስ ለማጥፋት ያልፈነቀለው ድንጋይ ያልጻፈው የታሪክ ቡትቶ፣ ያላቆመው ሐውልትና ያላቀበለው ወፍራል ሽልጦ የለም። ኦነጋውያንና ኦሕዴዶችንም ይህንንም እንደ ትልቅ የፖለቲካ ስኬት ይቆጥሩታል።
ምንም እንኳ ወያኔም ኾነ ኦነግ የፖለቲካ ቁማር መጫዎቻቸውንና የሥልጣን ዘመናቸውን ርዝማኔ የዳግማዊ ምኒልክን ውርስና ቅርስ በፈጠራ ታሪክ ላይ ተመስርተው ከማጥፋት ጋር ቢያቆራኙትም ሀቅ አትሸፈንምና ዳግማዊ ዐጤ ምኒልክ ለእኛና ለጥቁር ሕዝብ ሁሉ የዋሉትን ወደር የለሽ ውለታቸውን አውርተው ያልጠገቡ ጥቁር ሕዝቦች ሁሉ በየዓመቱ ሲዘክሩት ከመቶ ሀያ ዓመታት በላይ ኾኖታል። አድዋ ላይ ከፍ ብሎ የተውለበለበው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማም ደመናና ፀሐይ እስካልተፋለሱ ድረስ ሰማይ ላይ ቀስተ ደመና ኾኖ ሲውለበለብ ይኖራል!
እምዬ ምኒልክ እንኳን ተወለዱልን! ዘለዓለማዊ ክብር በብልህነትዎ ታይቶ ተሰምቶ የማይታወቅ ታሪክ ለጻፉልን ይኹን!
ክብር ከእምዬ ጋር አብረው ተሰልፈው የማይጠፋ ሥራ ሰርተው ላለፉ የአድዋ ጀግኖች ሁሉ ይኹን!
             *      *        *
እንደምርቃት…
 
የአምባላጌውን ምሽግ ሰባሪው የጎጃሙ አርበኛ  ራስ ቢትወደድ መግገሻ አቲከም
እንኳን በፈረስና በበቅሎ በእግር ለመውጣት  አስቸጋሪ ገደል የሆነውን የአምባላጌውን የጣሊያን ምሽግ ሰብረው ማጆር ቶዞሊን እዚያው ገድለው  የቀበሩት  የአድዋ ጀግና  ከደጋ ዳሞት 6000 ጦር ይዘው የዘመቱት የጎጃሙ አርበኛ  ራስ ቢትወደድ መግገሻ አቲከም ናቸው።
በመተማና በሳር ውኃ ጦርነት ለተገደሉት ካሳ፤ የተማረኩት ኢትዮጵያውን ደግሞ እንዲፈቱ በዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ተልከው  በመደራደር ከኦምዱርማኑ ከሊፋ  ዛሬ ከጎጃም ተቆርሶ  ቤንሻንጉል ጉሙዝ  የሆነውን መሬት  በጦር ካሳነት እንዲሰጥ  የተደረገው በራስ ቢትወደድ መንገሻ አቲከም ጥረት  መሆኑን  ነፍሳቸውን  ይማረውና የከንቲባ ገብሩ  ድስታ ልጅ ኮሎኔል ዳዊት ገብሩ ስለ አባታቸው ታሪክ በጻፉት የሕይወት ታሪክ  ውስጥ ነግረውናል።
ዘላለማዊ ክብር የማይጠፋ ሥራ ሰርተው ላለፉ የአድዋ ጀግኖች ሁሉ ይኹን!
________
የግርጌ ማስታወሻ
1. ይህ የጎጃም ጦር ጥሊያኖቹን ጀኔራል አልቤርቶኒንና ጀኔራል አሪሞንዲን ከፊታውራሪ ገበዬሁ ጋር በመሆን ጥለው በወደቁ በጎጃሙ ጀግና የጦር መሪ በፊታውራሪ ተገኜ ወርቄ የተመራውን ጦር አይጨምርም።
2. ራስ ቢትወደስ መንገሻ አቲከም የጠቅላይ ሚኒስቴር  እንዳልካቸው መኮንን አያት ሲሆኑ የእንዳልካቸው እናት ወይዘሮ ዘውዲቱ መንገሻ ይባላሉ። ራስ ቢትወደድ  መንገሻ ልጃቸውን ዘውዲቱ የሚል መጠሪያ ያወጡላቸው የሚወዷቸው ንጉሥ ዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ ጥቅምት 23 ቀን 1882 ዓ.ም. ዘውድ ሲጭኑ ስለተወለደች ነው።
Filed in: Amharic