>

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቻይና የሚያደርጋቸውን በረራዎች ማቋረጥ ተቀባይነት የለውም ( አቶ ተወልደ ገ/ማሪያም)

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቻይና የሚያደርጋቸውን በረራዎች ማቋረጥ ተቀባይነት የለውም

 

አቶ ተወልደ ገ/ማሪያም

 

 

 ቢቢሲ አማርኛ

 

 

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቻይና የሚያደርጋቸውን በረራዎች ቻይና ጊዜያዊ ችግር ባጋጠማት በዚህ ወቅት ማቋረጥ ተቀባይነት የለውም ሲሉ የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ተናገሩ።

ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ ተወልደ ገብረ ማሪያም እንዳሉት “አየር መንገዱ ከ1973 ጀምሮ ወደቻይና በረራ ሲያደርግ ቆይቷል። አሁን ጊዜያዊ ችግር ስላጋጠማቸው ማቋረጥ በሞራልም በሥነ ምግባርም ተቀባይነት የለውም” በማለት ከቻይናዊያን ጎን መቆም እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።

አክለውም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቻይና የሚያደርጋቸውን በረራዎች ቢያቆም የቻይናና የአፍሪካ የአየር ትራንስፖርት ሙሉ ለሙሉ ይቋረጣል፤ በኢትዮጵያ አየር መንገድ በኩል ያለ ማንም ሰው ይህ እንዲሆን እንደማይፈልግ ተናግረዋል።

በዚህም ቻይና ከአፍሪካ ጋር ካላት ግኙነት አንጻር “ከአፍሪካዊያን እህቶቻችንና ወንድሞቻችን ጎን መቆም አለብን” ብለዋል ዋና ሥራ አስፈጻሚው።

የተከሰተውን የበሽታ ወረርሽኝ በመፍራት በርካታ አየር መንገዶች ወደ ቻይና የሚያደርጓቸውን በረራዎች በማቋረጣቸው የኢትዮጵያ አየር መንገድም ተመሳሳይ እርምጃ እንዲወስድ ግፊት እየተደረገበት ባለበት ጊዜ ነው ዋና ሥራ አስፈጻሚው ይህንን ያሉት።

በአሁኑ ወቅት የተከሰተውን ችግር ለመከላከልም “ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለብን፤ በረራዎችን ማቋረጥ ግን ካሉ አማራጮች ውስጥ አይደለም” ሲሉም ተናግረዋል።

አቶ ተወልደ እንዳሉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቻይና የሚያደርጋቸውን በረራዎች ቢያቆም መንገደኞች በሲንጋፖር፣ በማሌዢያና በአውሮፓ በኩል ወደ ኢትዮጵያ መምጣታቸውን እንደማያቆሙ አመልክተዋል።

የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ ወደ ቻይና የሚያደርጉትን በረራዎች ከበሽታው መከሰት ጋር በተያያዘ ያቋረጡ አየር መንገዶች የእራሳቸው ምክንያት እንዳላቸው ጠቅሰው፤ እንደ ምሳሌም “የብሪቲሽ አየር መንገድ በረራውን እንዲቆም ያደረገው በእራሱ ኢኮኖሚያዊ ምክንያት ነው” በማለት ጠቅሰውታል።

ነገር ግን የቻይና አየር መንገዶች ወደ ዩናይትድ ኪንግደም በረራዎቻቸውን እያከናወኑ መሆናቸውን አቶ ተወልደ ተናግረዋል።

ምዕራብ አፍሪካ ውስጥ ኢቦላ ከ8 ሺህ በላይ ሰዎችን መግደሉ አይዘነጋም። ነገር ግን በሽታው ዴሞክራቲክ ኮንጎ ውስጥ እያለ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደዚያው እየበረረ መሆኑን ጠቅሰዋል።

ዋና ሥራ አስፈጻሚው ይህንን የተናገሩት አየር መንገዱን ለረጅም ጊዜ ላገለገሉ ሠራተኞች በተዘጋጀ የእውቅና ዝግጅት መዝጊያ ላይ ባደረጉት ንግግር ነው።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ አምስት የቻይና ከተሞች በሳምንት 35 በረራዎችን በማድረግ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው መንገደኞችን ወደ አፍሪካ ያጓጉዛል።

በዚህም ከአፍሪካ ወደ ቻይና በሚደረጉ በረራዎች የኢትዮጵያ አየር መንገድን የሚፎካከር አህጉራዊም ሆነ ዓለም አቀፋዊ የአየር ትራንስፖርት ሰጪ ተቋማት የለም።

BBC Amharic

Filed in: Amharic