>

እውነት አብርሃ ደስታ አሸባሪ ወይስ ህወሓት እህአዴግ ነው ለሰላማዊ ትግል ፈሪ? [ክብሮም ብርሃነ-መቐለ]

Abrha Desta (photo by Kuru Hagere FB)ነሐሴ 1 ቀን 2006 ዓ.ም የአረና ትግራይ ፓርቲ ስራ አስፈፃሚና የመቀሌ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር አብርሃ ደስታ በሽብር ተጠርጥሮ በተከሰሰበት ልክ በወሩ ፍ/ቤት እንደሚቀርብ በፌስ ቡክ አይቼ እኔም እንደ ዜጋና እንደ አድናቂው የሚቀርቡለትን የድራማ ክስ ለመስማት ጓጉቼ ፍ/ቤቱ ስደርስ እንደ እኔ አብርሃ ደስታን በአይናቸው ለማየትና የክሱን ድራማ ለማወቅ እንዲሁም ለቆራጡ ወጣት ፖለቲከኛ አብርሃ ደስታ የሞራል ድጋፍ ለመስጠት የተሰባሰቡ የተለያዩ የክልላዊና ሀገራዊ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች፣ አባላት፣ ጋዜጠኞችና ብሎገሮች እንዲሁም የወጣቱ ፖለቲከኛ አድናቂዎች ሽማግሌዎችና ወጣቶች ተደማምረው ያልገመትኩት የሕዝብ ብዛት በቡድን በቡድን ሰብሰብ ብለው የአብርሃ ቆራጥነትና የሀገራችን የፖለቲካ ሁኔታ ሲወያዩ አገኘኋቸው፡፡

የክሱን ሁኔታ ለመመልከት የመጡ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች
1. የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ(አንድነት) ተቀዳሚ ም/ፕሬዚዳንት አቶ ተክሌ በቀለ
2. የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ(አንድነት) ም/ፕሩዚዳንት አቶ በላይ ፍቃዱ
3. የሰማያዊ ፓርቲ ም/ፕሬዚዳንት አቶ ስለሺ ፈይሳ
4. የመድረክ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጥላሁን እንደሻው
5. የጌድኦ ሕዝብ ዴሞክራስያዊ ፓርቲ ፕሬዝዳንት ኣቶ ኣለሳ መንገሻ እንዲሁም ጋዜጤኞች፣ ብዙ የታወቁ ሰዎችና ወጣት አድናቂዎቹ ተገኝተዋል፡፡

አብርሃ ደስታ ወደ ፍ/ቤት ሲገባ
አብርሃ ወደ ፍ/ቤቱ ግቢ ከመድረሱ በፊት ቁመቱ ትንሽ ረዘም ያለ የፊቱ ቀለም አብርሃን የሚመስል አንድ የትግራይ ተወላጅ ደህንነት (ለራሱ ያልዳነ) ከኋላው ሶስት ጠመንጃ ያነገቡ የፌዴራል ፖሊስ አስከትሎ ሲገባ አብርሃ ደስታን ለማየት ጓጉቶ የነበረ የአዲስ አበባ አድናቂዎቹ ‹‹ መጣ ……. መጣ…….. ›› ማለት ጀመሩ፡፡ ደህንነቱና የፌዴራል ፖሊሶቹ ልክ እንደገቡ ፊታቸውን ከሰል አስመስለው “ገለል በሉ …. ዞር በሉ ……!” እያሉ ትዕዛዝ ስለሰጡ ራቅ ብለን ተሰለፉ ሳንባል ፊታችን ወደ ዋናው መንገድ አድርገን ራሳችን ተሰለፍን
አንድ የፌዴራል ፖሊስ ከፊቱ ሆኖ እየመራው አብርሃ በኢትዮጵያ ሕዝብ፣ በሙስሊሙና በክርስቲያኑ ያለውን የመልካም አስተዳደር እጦት እንዲሁም የፖለቲካ ጣልቃ ገብነትና አፈና ለመግለጽ ቀለም የሚያንጠባጥብ ብዕር መያዝ ብቻ የለመዱ እጆቹ በብረት ሰራሽ ካቴና ክርችም ብሎ እልህ የሚነበብበት ፊቱ ጠቆር ብሎ፣ ሰውነቱ ከሳ ብሎ ሁለት የፌዴራል ፖሊስ አስከትሎ ገባ፡፡ ልክ ሙሽራ ሲመጣ እንደምናደርገው አቀባበል ወደ ፍ/ቤቱ ግቢ እንደገባ ያ ሁሉ ሕዝብ ግቢውን በጭብጨባ ቅውጥ አደረገው ያኔ አብርሃ ደስታ ግራ ገባው፡፡ ያ ሁሉ ሰው በሰልፍ ቆሞ ሙሽራ እንደመጣ ሲያጨበጭብ ይሆናል ብሎ ስላልጠበቀ መሰለኝ ጭብጨባው ለራሱ አልመሰለውም፡፡ አንድ ሁለት እርምጃ እንደሄደ ቀና ብሎ ሲያይ ብዙ የሚያውቃቸው ሰዎች ሲያይና ‹‹ አይዞህ!……. አይዞህ!……. አብርሃ የኛ ጀግና! ከጎንህ ነን! ›› እያሉ እጃቸውን እያወዛወዙ ሰላምታና ሞራል ሲሰጡት ለሱ መሆኑን ሲያውቅ ፊቱን ፈገግ በማድረግ የታሰሩ እጆቹን ከፍ በማድረግና ከወቡ ጎንበስ በማለት በተደረገለት አክብሮትና ሞራል የጨዋ ምላሽ እየሰጠ ወደ ችሎቱ ገባ፡፡
የግቢውን በር ከረገጠበት ጀምሮ ችሎት እስከሚገባ ድረስ ባለማቋረጥ በኃይለኛ ጭብጨባ ታጀበ፡፡ ያኔ ይዞት የመጣው ደህንነት በጣም ስለበሸቀ ‹‹ ስነስርዓት አድርጉ!…. ስነስርዓት አድርጉ!…. ›› ቢልም ሀሳቡ ስነስርዓት የሚያሲዝ ስላልነበረ መሰለኝ ጆሮ የሚሰጠው አልነበረም፡፡ አስከትሎም ምንም እንኳ በግልጽ ለማን መሆኑ ባይታወቅም “ቆይ አሳይሃለሁ!…. ኋላ ይቆጭሃል!…. ” እያለ ማስፈራራት ጀመረ፡፡ ይህን የሚገልጽ አንድ የትግርኛ አባባል አለ፡፡ ምን ይላል መሰላችሁ “ሰበይቱያ ዝለአኸቶስ ደገአፍ ቤተመንግስቲ አይፈርሕን ” በአማርኛም እንደዚህ “ሚስቱ የላከችው ሞት አይፈራም ” ይባላል፡፡ ያ ያልዳነ ድህንነትም ያመነው ነገር ባይኖር ህግ ባለበት ሀገር ደህንነት በመሆኑ ብቻ እንዲህ ብሎ ሰው ማስፈራራት አይችልም ነበር፡፡
“ቆይ አሳይሃለሁ!… ኋላ ይቆጭሃል!….” ማለቱ አንተም በሽብር ከስሼህ አሰቃይሃለሁ ማለቱ ይሆን?
በነገራችን ላይ አብርሃ ወደ ፍርድ ቤት ይቀርባል ተብሎ የተቀጠረው በ8፡00 ሰዓት ነበር፡፡ አብርሃን ለማየት የተሰበሰበ የሕዝብ ቁጥር አላምር ስላላቸው መሰለኝ ምናልባት ተሰላችተው ይሄዱ ይሆናል በሚል ታሳቢ እስከ 10 ሰዓት ከ25 አላቀረቡትም ነበር፡፡ ሕዝቡም ይሄን ተረድቶ እስከ 12 ሰዓትም ቢሆን እንቆያለን ብሎ በመረጋጋቱ እንደማይሆንላቸው አውቆ 10 ሰዓት ከ25 ሲል ነው ያመጡት፡፡ ይህ ግን በአብርሃ ብቻ ሳይሆን በእነ ሀብታሙ አያሌውም እንዲህ ተደርጓል፡፡ የሆነው ሆኖ ከግማሽ ሰዓት የችሎት ቆይታ አብርሃ እንደገና ታጅቦ ከችሎት ወጣ፡፡ ሲወጣም እንደገና ቅልጥ ያለ ጭብጨባና ሞራል ሲሰጠው ፈገግ እያለ አፉ ባይናገርም በታሰሩ እጆቹ አይዟችሁ እያለ እጅ እየነሳ ወጣ፡፡

የአብርሃ ደስታ ክስ በፖሊስ ሲነበብ
አብርሃ ችሎት ከገባ በኋላ አጠገቡ የነበረው በሙያውና በስነምግባሩ የታወቀ እንዲሁም ከብር ይልቅ ለፍትህ ቅድሚያ የሚሰጥ ጠበቃው ተማም አባቡልጉ ብቻ ነበር፡፡ ኋላ ግን ሁለት የአረና አመራርና አንድ የአክስቱ ልጅ ገብተው የክሱን ሁኔታ እንዲከታተሉ ስለተፈቀደላቸው ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ተከታትለዋል፡፡
አጠቃላይ የክሱ ጭብጥ
1. አረና ትግራይ ሽፋን በማድረግ ከግንቦት 7 አመራሮች እየተገናኘና ገንዘብ እየተቀበለ ሽብርን ለመፍጠር ተንቀሳቅሷል፡፡
2. ሽብር ለመፈጸም 60 ሰዎች መልምሏል፡፡
3. በቤቱ ሽብር ለመፈጸም የሚያስችል ዶክመንት በፍተሻ ተገኝቷል የሚሉ ነበሩ፡፡
መቼም ቢሆን አብርሃ ደስታ ይህን የፈጠራ ክስ ፈጽሞት ይሆን? ብሎ የሚጠራጠር ካለ የዘመኑ በጣም የዋህ ወይም የህወሓት/ኢህአዴግ መሰሪ ሴራና ተንኮል የማያውቅ ብቻ ነው፡፡ አብርሃ ህወሓት የሚፈጽማቸውን አፈናዎችና የህግ ጥሰቶች በየቀኑ ለኢትዮጵያ ሕዝብ እያሳወቀ በመሄዱና ሕዝብ በጽናት ታግሎ በሚቀጥለው ምርጫ ከትከሻው አሽቀንጥሮ መጣል እንዳለበት በድህረ ገጾችና በመጽሔቶች እየጻፈ ለብዙ ወጣቶች አርአያ እየሆነ በመሄዱና የትግራይ ሕዝብ የህወሓት ክህደትን አውቆ ለዳግም ሰላማዊ ትግል በሁሉ አቅጣጫ እንዲነሳሳ ማድረጉ ለህወሓት ትልቅ የራስ ምታት ስለሆነበት ነው እንጂ አብርሃ ደስታ የተከሰሰበትን የፈጠራ ክስ እንደማይፈጽምና እንዲህ አይነት ተልካሻ ስራ በሚወዳት ሀገሩና በሚወደው ሕዝብ ላይ ለመስራት የሚያዘው ጭንቅላት እንደሌለው አብርሃን በቅርበት የሚያውቁት ሁሉ ይመሰክሩለታል፡፡
አብርሃ ደስታ ለፍ/ቤቱ ካቀረባቸው አቤቱታዎች
1. በጣም ቀዝቃዛና ጨለማ በሆነ ቤት ብቻውን እየታሰረ እንዳለ
2. ፍ/ቤት እስከቀረበበት ጊዜ 8 የተለያዩ ግለሰቦች ከለሊቱ ከ7 እስከ 8 ሰዓት በየተራ እየመጡ እንደሚደበድቡት
(እንደሚያሰቃዩት)
3. በጭለማ ቤት ሆኖ የማያውቀውንና ያላነበበውን ጽሑፍ (ዶክመንት) እየተደበደበ እንዲፈርም እንደተደረገ
4. የቆየ የጨጓራ ህመም ስላለው እንጀራ ብዙም እንደማይማይበላና ሆኖም ግን አሁን ያለ ፍላጎቱ እያመመው እንዲበላ ስለተገደደ በከፍተኛ የጨጓራ ህመም እየተሰቃየ እንዳለ፣ በማዕከላዊ (ታስሮ ባለበት ቦታ) በሚደረግለትን የህክምና ዕርዳታ ሊያገግም እንዳልቻለ እነዚህና ሌሎች እየደረሱበት ያሉ ስቃዮች ምንም እንኳን ሰሚ ባያገኝም በአቤቱታ መልክ አቅርቧል፡፡
የተከበራችሁ አንባቢዎች እውነት አብርሃና መሰሎቹ ሽብርን ለመፈጸም በተጨባጭ መረጃና ማስረጃ ተይዞ ከሆነ እመኑ እየተባሉ ያ ሁሉ መደብደብ፣ መሰቃየትና ሳያነቡ ጽሑፍ እንዲፈርሙ መደረጉ ለምን አስፈለገ? የተገኘ እውነተኛ መረጃ ለሕዝብ ግልጽ አይደረግም? ፍርዱን ሕሊና ላለው ሰው ይሁን፡፡

በጠበቃው ተማም አባቡልጉ የቀረበ ክርክር
አንድ ሰው በወንጀል ተጠርጥሮ ሲየዝ በቂ የሆነ መረጃና ማስረጃ መኖር አለበት (ሕገ መንግስት እያጣቀሰ) አለበለዚያ ሰውን አስረህ ፖሊስ መረጃና ማስረጃ ላሰባስብ ጊዜ ይሰጠኝ ስላለ ብቻ ከበቂ በላይ ጊዜ እየተሰጠ ሰው ማሰቃየት ከህግ በላይ መሆን ነው፡፡ ወይም ሰው በእምነቱ እንዳይጓዝ ለመገደብ የሚደረግ ህገ መንግስቱን የጣሰ አካሄድ ነው፡፡ ስለዚህ አሁንም ፖሊስ ከዚህ ቀደም በቂ ጊዜ ተሰጥቶት እያለ ትርጉም ያለው መረጃና ማስረጃ ሊያቀርብ ስላልቻለ አሁንም እንደገና ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ መጠየቁ ደንበኛዬ ከስራው ለማስተጓጎልና ለማሰቃየት ካልሆነ ሌላ ዓላማ ስለሌለው ደንበኛዬ የዋስ መብቱ እንዲከበርለትና በዋስ ተፈትቶ ክሱን በውጭ ሆኖ እንዲከታተል ይወሰንልኝ ብሎ ህገ መንግስቱን ተንተርሶ ተከራክሮዋል፡፡ ግን ምን ዋጋ አለው ከሳሹና ፈራጁ አንድ በሆነበት ሀገር ፍትህ እንዴት ይገኛል? ድሮም እኮ ፍትህ ቢኖር በፈጠራ ክስ ሰው አይከሰስም ነበር፡፡ እንዲህ ስለሆነ እንደገና ከ28 ቀናት በኋላ ነሐሴ 29 ፍርድ ቤት ይቀርባል ተባለ፡፡

በዛን ቀን የታዘብኩት ነገር
ህወሓት/ኢህአዴግ በቋንቋ፣ በብሔርና በጎጥ ከፋፍሎ ሲገዛን የራሱና ለራሱ ብቻ የሚሆን ምክንያት አለው፡፡ ነገር ግን ያን ቀን የታዘብኩት ነገር ካለ በህወሓት/ኢህአዴግ ሴራ ኢትዮጵያዊነታችን አሁንም ጨርሶ እንደማይናድ ነው፡፡ ምክንያቱም ህወሓት/ኢህአዴግ አብርሃን መቐለ ይዘው አዲስ አበባ ፍ/ቤት ሲያቀርቡት የፍርድ ሂደቱን የሚከታተል ብዙ ሰው ስለማይኖር የአብርሃ ሞራል ይጎዳል ብለው ይሆንናል፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችን እኩል አይቶ በእኩል የሚቆረቆር፣ ከግላዊ ጥቅምና ክብር የሕዝብ ጥቅምና ክብር የሚያስቀድም እንዲሁም የሀገርና የሕዝብ መብትና አንድነት ይከበር ብሎ በፅናት በአደባባይ የሚከራከር ኢትዮጵየዊ ከየትኛውም ብሔር ወይም ክልል ይምጣ፣ የፈለገውን ቋንቋ ይናገር በኢትዮጵያውያን ዘንድ የተለየ ክብርና ሞገስ እንዳለውና ሁሌም ኢትዮጵያውያን ከጎኑ እንደሆኑ በደንብ ተረድቻለሁ፡፡ አሳሪዎቹም ጭንቅላት ካላቸው ሳይረዱት አይቀርም፡፡ እንዴት ብትሉኝ አብርሃ የትግራይ ተወላጅ ኢትዮጵያዊ ቢሆንም ህወሓት/ኢህአዴግ እርስ በእርሳችን በጥላቻ አይን ከመተያየት አልፈን እንዳንተባበር የሚያደርጋቸውን የተለያዩ ሴራዎችን ሰብሮ የአብርሃ ጉዳይ የሁላችን ጉዳይ ስለሆነ ያሳስበናል ብሎ ብሔር፣ ቋንቋ እንዲሁም የህወሓት/ኢህአዴግ የመከፋፈል ሴራ ሳይገድባቸው የትግራይ፣ የአማራ፣ የኦሮሞና የደቡብ ተወላጆች ኢትዮጵያውያን በአንድነት የግል ስራቸውን ትተው የወጣት ፖለቲከኛና መምህር አብርሃ ደስታ የፍርድ ሂደት ሲከታተሉ መዋላቸውና ከፍተኛ ሞራል መስጠታቸውን ሳይ ኢትዮጵያዊነታችን በህወሓት/ኢህአዴግ ሴራ ጨርሶ እንደማይሸረሸር አረጋግጫለሁ፡፡ በኢትዮጵያዊነቴም ኩራት ይሰማኛል፡፡ አሁንም ገዢዎች በሚያደርጉት ሴራ እኛ ኢትዮጵያዊያን መለያየትና መቀያየም የለብንም፡፡ ለጋራ ዓላማና ጥቅም በጋራ መንቀሳቀስ አለብን፡፡ ስንተባበር ክንዳችን ይጠነክራል ሞራላችን ከፍ ይላል፡፡
ቸር እንሰንብት!

አንድ ቀን የፍትህና የነፃነት ባለቤቶች እንደምንሆን አልጠራጠርም!

ምንጭ – ፍኖተ ነጻነት

ፎቶ ቅንብር በኩሪ ሃገሬ

Filed in: Amharic