>

አባቶቻችን ሙስሊም የአማራ ነፍጠኞች !!! (አቻምየለህ ታምሩ)

አባቶቻችን ሙስሊም የአማራ ነፍጠኞች !!!

 

አቻምየለህ ታምሩ
እስልምና እንደ ሃይማኖት አረብ የሆነውን ያህል ኢትዮጵያዊም ነው። በኢትዮጵያ  ውስጥ ደግሞ  እስልምናን ቀድመው የተቀበሉ፣ በኢትዮጵያ  ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የእስልምና አካባቢያዊ መንግሥት በመመስረት  የሙስሊም ሱልጣኔት ያቋቋሙ አማሮች ናቸው። የሸዋ የሙስሊም ሱልጣኔት  የአማራ የሙስሊም መንግሥት ነበር። ይህ ብቻ አይደለም! በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከሸዋ ወደ ምስራቁ የኢትዮጵያ ክፍል በመሄድ የአዳልን የሙስሉም ሱልጣኔት ያቋቋሙት የኡመር ወላስማ ዘሮችም  የአማራ ተወላጅነት ያላቸው ናቸው። በዚህ ጉዳይ ወደፊት በሰፊው እመለስበታለሁ።
የኦነግ የሃይማኖት ክንፍ  ፕሮፓጋንዲስቶች  ግን ጸረ አማራነታቸውን በእስልምና ስም ሸፍነው ከአማራ በላይ ሙስሊም ሆነው ለአማራ እስልምናን ሊያስተምሩት ይቃጣቸዋል። አማራ በኢትዮጵያ ምድር የእስልምና አስተማሪ እንጂ ከቶ የእስልምና ተማሪ ሊሆን አይችልም። በኢትዮጵያ ውስጥ ወንበር ዘርግተው፣ ጉባኤ አስፋፍተው፣ ቀለም በጥብጠውና ብራና ፍቀው እስልምናን ያስፋፉት አማሮች ናቸው።  የሩቁ ብቻ ሳይሆን በቅርቡም  የአገራችን ታሪክ ውስጥ አማሮች የእስልምና አስተማሪዎች እንጂ የእስልምና ተማሪዎች ሊሆኑ  አይደሉም። የነ አሕመዲ ጀበልን «አባት» የጅማውን ንጉሥ ቀዳማዊ አባ ጅፋርን እስልምና እንዲቀበሉ ያደረጉት  የጎጃምና የጎንደር አማራ ሙስሊሞች ናቸው። ይህንን ታሪክ  የነገረን  ደግሞ ማንም ሳይሆን  የጅማን ዘውዳዊ መንግሥት ታሪክ የጻፉት የአባጅፋር ልጅ  የሆኑት አባ ጆቢር ናቸው።
ሐምቡርግ ዩኒቨርሲቲ እ.ኤ.እ. በ2003 ዓ.ም.   በእንግሊዝኛ አስተርጉሙ ያሳተመው አባ ጆቢር በአረብኛ የጻፉት  የጅማ ንጉሣዊ ቤተሰብ ታሪክ «The History of Jimma and the DiGGO Dynasty» ገጽ 12 ላይ እንደሚነግረን የጅማን ዘውዳዊ ቤተሰብ ወደ እስልምና ሃይማኖት እንዲገቡ ያደረጉት የጎንደር ሊቦ ተወላጁ ሸሕ አብዱል ሐኪምና የጎጃም ተወላጁ አባ አረቡ የተባሉ አማሮች ናቸው። እነዚህ ሁለት የአማራ ሼሆች ቀዳማዊ አባ ጅፋርን ወደ እስልምና የቀየሯቸው በ1822 ዓ.ም. መሆኑን  አባ ጆቢር የጻፉት የጅማው ታሪከ ነገሥት ያወሳል።
በኦሮሞ የገዢ መደብ ወረራ የፈለሰውን ርስታቸውንና የፈረሰውን አገራቸውን  እንደገና አንድ በማድረግ ረገድም  እንደ ክርስቲያን አማሮች ሁሉ ሙስሉም አማሮችም ግንባር ቀደም  ነፍጠኞች ነበሩ። ነፍጠኛ ማለት የተነጠቀውን ርስቱን ለማስመለስ፣ በወራሪ የተቀማውን ባድማውን ለማስከበርና አገሩን መልሶ አንድ ለማድረግ  የተሰማራ አርበኛ ማለት ነው። አማራውን የሰደቡ እየመሰላቸው ነፍጠኛ ሲሉ የሚውሉት ኦነጋውያን አማራው በሃይማኖት ሳይለያይ ነፍጠኛ የሆነው የተነጠቀውን ርስቱን ለማስመለስ፣ የተቀማውን ባድማ ለማስከበርና የኦሮሞ የገዢ መደብ ወረራ የፈረሰውን አገሩን ከሌሎች ጋር ሆኖ ወልሶ አንድ ለማድረግ እንደዘመተ እየመሰከሩለት ነው።
የአማራው አንድነትና ጣምራ እንቅስቃሴ ያሰጋቸው፣  ሴት ሙስሊም  ወጣት አማሮች የአርበኛ  አባቶቻቸውን ምልክት የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ መልበሳቸው አስደንግጧቸው  ከሰሞኑ  በእስልምና ስም ጸረ አማራና ጸረ ኢትዮጵያ  ፕሮፓጋንዳቸውን ሲያስፋፉ የሰነበቱት ጀበሎች አማራው የእስልምና አስተማሪ እንጂ ተማሪ አለመሆኑን፤ እነሱንም እስልምና ያስተማረው አማራው መሆኑን ማወቅ አለባቸው!
ከታች በፎቶው ላይ የሚታዩ የአማራ ሙስሊም አርበኞች የ19ኛውና የ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩ ነፍጠኞች ናቸው። ጋቢ የለበሱቱ የመጀመሪያው አርበኛ የአድዋ ዘማቹ የወሎ አምባሰሉ ደጃዝማች አሊ ሲሆኑ  ካባ የለበሱቱ ሁለተኛው  አርበኛ ደግሞ የጎጃሙ ፊታውራሪ አሊ ናቸው። ሁለቱ አሊዎች ዳግማዊ ምኒልክን ተከትለው ርስት በማስመለስና አገር አንድ በማድረግ ዘመቻው ውስጥ ግንባር ቀደል ተሰላፊ የነበሩ ዐሊም የአማራ  ነፍጠኛ ነበሩ።
Filed in: Amharic