>
5:13 pm - Thursday April 20, 7876

አቶ ሙስጠፌ ለካቢኔያቸው የሰጡት ትእዛዝ! (ሙክታሮቪች ኡስማኖቭ)

አቶ ሙስጠፌ ለካቢኔያቸው የሰጡት ትእዛዝ!

ሙክታሮቪች ኡስማኖቭ
   የሱማልያ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ ሚስጠፌ በዛሬው እለት ካቢኔያቸውን  አስቸኳይ ስብሰባ ጠርተው በክልሉ የተፈጠረውን ሰላም ና መረጋጋት ለማደፍረስ እየሰሩ ስላሉ አክራሪ ውኃ ብዮች በተመለከተ ከረር ያለ መመርያ ሰጥተዋል።
   ” እኔ ከአላህ የተላከውን የቅዱስ ቁርአን አስተምህሮ በመስጂድ ውስጥ የተማርሁት #እስላም ማለት ሰላም መሆኑን ነው። አላህ ወንጀልን ይፀየፋል፣ በቀል ና ጥፋት ደግሞ ወንጀል ነው። ኢትዮጵያ የክርስትያኖች ብቻ መኖርያ በነበረችበት ክርስትና ከቤተመንግስት እስከ መንደሮች በጥብቅ ተፅእኖ ሥር ሀገሪቷን በሚያስተዳድርበት፣ ስልጣኔ ባልነበረበት በድሮ ጊዜ እስልምናን በሰላም ና በክብር  እንግድነት የተቀበሉት የኢትዮጵያ ክርስትያኖች ናቸው።
ዛሬ የእኛ ትውልድ “ወርቅ ላበደረ ጠጠር” እንደሚባለው አባቶቻችንን በክብር የተቀበለውን ህዝብ በሰይፍ መግደል፣ የእምነት ቤቱን ማቃጠል በመንግስታችን በኩል በህግ የሚያስጠይቅ ሲሆን በአላህ ፊት ደግሞ እጅግ አፀያፊ ተግባር ነው።
     ቀድሞ በእኛ ክልል ብዙ አብያተ ክርስትያናት በአክራሪ ሀይሎች ሲቃጠሉ በመላው ኢትዮጵያ የሚገኙ ክርስትያናት በመስጅዶችና በእስልምና ተከታዮች ላይ ምን አደረጉ? በአሁኑ ሰአት በአማራ ክልል የተቃጠሉ መስጂዶችን ያቃጠሉ ክርስትያኖች ሳይሆኑ የአክራሪ እስልምና ክንፎች ናቸው።
አላማውም በሀገራችን የተፈጠረውን ሰላም ለማደፍረስ ና የኃይማኖት ፀብ በመፍጠር ሀገርን በማተራመስ የክፉዎችን ተልእኮ ለመፈፀም ሆን ተብሎ የታቀደ ነው።
     ከዚህ በፊት በአማራ ክልል እኛ የምናውቀው በክልሉ ቤተክርስትያን ሲገነባ እስላሞች በገንዘብና በጉልበት ሲያግዙ፣ መስጂዶች ሲሰሩ ደግሞ ክርስትያኖች በገንዘብና በጉልበት ሲያግዙ ነው። ክረስትያኖች ይህን ተግባር የሚፈፅሙበት ምንም አይነት ምክንያት የለም።
    ስለሆነም ከዛሬ ጀምሮ በክልላችን ውስጥ በክርስትያኖችና በቤተ እምነታቸው ላይ የሚፈፀም ማንኛውም ጥቃት ቢኖር የመጀመርያ ተጠያቂ የሚሆነው ይህ የክልላችን ከፍተኛ አመራር ነው። ምክንያቱም ክልላችንን የሚያስተዳድረው መንግስት ሁሉም ነገር መዳፉ ውስጥ እንደሆነ ሁላችንም እናውቃለን። ስለሆነም በክልላችን ውስጥ ማንኛውም አይነት ጸረ ሰላም እንቅስቃሴ ከተፈጠረ ተመጣጣኝ ና ቆራጥ እርምጃ በመውሰድ ወንጀለኞችን ማስተማር ተቀዳሚ ተግባራችን ይሆናል”   በማለት ከረር ያለ ትእዛዝ አስተላልፈዋል
Filed in: Amharic