>

በመቋለ የተሰባሰቡ ፌደራሊስቶች ያወጡት የአቋም መግለጫ!!!

በመቋለ የተሰባሰቡ ፌደራሊስቶች ያወጡት የአቋም መግለጫ!!!
መቐለ በተካሄደው ሕገ መንግስትን እና ሕብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ስርዓት የማዳን ሁለተኛ አገር አቀፍ መድረክ መጠናቀቁን ተከትሎ ከተሳታፊዎች የተላለፈ የአቋም መግለጫ
አገራችን ኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች በመፈቃቀድ በጋራ የመሰረቷት ቤት እንደመሆንዋ በብዝሃነት ላይ የተመሰረተ አንድነትን ለመገንባት የሚያስችል ሕገ መንግስት እና ህብረ ብሔራዊ ፌደራሊዝምን በብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ይሁንታ ፀድቆ ወደ ሥራ ከገባ ወዲህ ከሃያ ዓመታት በላይ አስቆጥሯል።
በነዚህ ዓመታት ውስጥ ሕገመንግስታዊነትንና ህብረ ብሄራዊ የፌደራልዝም ስርዓትን ቀስ በቀስ እግር እየተከሉ በሰላም፣ በልማት እና በዴሞክራሲ ረገድ ብዙ ለውጦች የተመዘገቡ ቢሆንም ቅሉ በመንግስት ውስጥ እየገነገነ በመጣው ኪራይ ሰብሳቢነት፣ የፀረ ዴሞክራሲ አሰራር እና የመልካም አስተዳደር ችግር የተጀመረውን መልካም ሥራ በተለይም ሕገ መንግስቱንና ህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ስርዓቱን ለከፍተኛ አደጋ ተጋልጠዋል። ኢህአዴግ በህብረ በሔራዊ የፌደራሊዝም ስርዓት እንዲመራት በአደራ የተቀበላት አገርና የተሰጠው የፖሊተካ ስልጣን መንገድ ስቶ አገሪቷን ወደ መበታተን አያመራች ነው።
አገራዊ ተጨባጭ ሁኔታችን የብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች ሕገ መንግስታዊ መብቶች እና ራስን በራስ የማስተዳደር መብታቸውን አደጋ ላይ የወደቀበት፤ የሕግ የበላይነት፣ ሰላምና የዜጎች ደህንነት የማይከበርበት፤ የዜጎች መሰረታዊ ጥያቄዎች በማዳፈን ስልጣን ላይ ያሉ ሀይሎች ያለ ገደብ ያሻቸውን ለማድረግ ሕግ የማይገዛቸው በሚመስል መልኩ የሚጓዙበት፤ የተጀመሩ መልከም ውጤቶች ወደ ኋላ የተመለሱበት በጣም አስጊ በሆነ መንገድ እየተጓዝን ባለንበት ሁኔታ ኢህአዴግ እነዚህ ተጨባጭ እና አንገብጋቢ አገራዊ ችግሮች ከመፍታት ይልቅ በለውጥና ሌሎች አማላይ ቃላት እየተንቆለጳጰሰ በውህደት ሥም ወደ ቀድሙት ስርዓቶች ለመመለስ ጫፍ ላይ ደርሷል። የመንግስትም የግልም ሚድያዎች አገርን የማዳን ሀላፊነታቸውን ከመወጣት ይልቅ ሀቆችን በማዳፈንና ችግሮችን በማባባስ ተጠምደዋል።
እኛ የመድረኩ ተሳታፊዎች ባካሄድነው ሰፊ ወይይት በሕገ መንግስታችንና በህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ስርዓታችን የተደቀነው አደጋ በብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች የጋራ ትግል ካልተገታ አገርን ወደ መበታተን ህዝቦችን ወደ የእርስ በርስ ዕልቂት ሊያስገባን እንደሚችል መደምደምያ ላይ ደርሰናል።
በአገራችንና ህዝቦቿ ላይ የተደቀነው ግልጽ አደጋ በመቀልበስ በኩል ከፍተኛ ሚና መጫወት ያለበት መንግስትና መሪ ድርጅቱ ቢሆኑም፤ ሕገ መንግስት፣ ህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ስርዓት እነዲሁም አገራችን የመንግስት እና የፖለቲከኞች ብቻ አይደሉም። አገራችን የብሄሮቿ፣ የብሔረሰቦቿና ህዝብቿ ናት። የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች ከባድ መስዋዕትነትን ከፍለው በሕገ መንግስቱ የተጎናጸፏቸው መብቶችና ነጻነቶች ወደ ቀድሞ ጨፍላቂና አሀዳዊ ስርዓት ለመመለስ የሚደረገውን ጥረት ከሁሉም በላይ ይጎዳቸዋል ብቻ ሳይሆን ገና ከወዲሁ ከፍተኛ መፈናቀል፣ ግድያ፣ ንብረታቸውን መዘርፍንና መቃጠል፣ በእምነታቸውን መሸማቀቅ ወዘተ በግልጽ እየታዩ ናቸው። ስለዚህም የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች የተደቀነባቸውን የመበታተንና የመተላለቅ አደጋ ከወዲሁ በነቃ ተሳትፎና አደረጃጀት ፊትለፊት ወጥተው መታገል አለባቸው።
ስለዚህ ሕዳር 23-24/2012 ዓ.ም ሕገ መንግስትን እና ህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ስርዓት የማዳን ሁለተኛ አገር አቀፍ መድረክ በመቐለ ከተማ የተሳተፍን የብሔራዊ እና አገርአቀፍ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች፣ ከብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች የመጣን የሀይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ አባገዳዎች፣ እናቶች፣ ሙሁራን፣ ወጣቶች፣ የሲቪክ ማህበራት ተወካዮች፣ በአጠቃላይ የፌደራሊዝም ኃይሎች በተጨባጭ አገራዊ ወቅታዊ ሁኔታዎች ላይ የቀረቡት ጥናታዊ መነሻ ፅሑፎች አድምጠን ባደረግነው ሰፊ ውይይትና ተሳትፎ የጋራ መግባት ላይ ደርሰናል።
በዚሁም መሰረት ወደ ተግባር እንዲቀየሩ የሚኪተለውን የአቋም መግለጫ በጋራ አውጥተናል፦
1. ፀረ ህብረ ብሔራዊ ፌደራሊዝም እና አሀዳዊ ሀይሎች ባለ በሌለ አቅማቸው በሕገ መንግስታችን እና ህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ስርዓታችን የከፈቱት ጥቃት ለመመከት የሚያስችለን ህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ሀይሎች ፎረም በመፍጠር፤ ፎረሙም ወደፊት በሚያስቀምጠው አቅጣጫ እና ውሳኔ መሰረት ጠንካራ አደረጃጀት በመፍጠር መላ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች በማንቀሳቀስ ሕገ መንግስቱን እና ህብረ ብሔራዊ ፌደራሊዝሙን ለመታደግ በጋራ ለመታገል ወስነናል።
2. በዚህ አገርን የማዳን መድረክ በተላለፈው ውሳኔ መሰረት ወደ ተግባር ለመግባት ህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ሀይሎች በምናደርገው እንቅስቃሴ እና ትግል ሁሉም ባለድርሻ አካላትና የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች ያልተቆጠበ ድጋፍና ሰላማዊ ትግል እንዲያደርጉ ጥሪ እናስተላልፋለን።
3. እኛ ህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ሀይሎች የፖለቲካ ስልጣን ሉዓላዊ ባለቤቶች ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች ናቸው ብለን እናምናለን። በመሆኑም የኢፌዲሪ ሕገ መንግስት በደነገገው መሰረት ስድትኛው የ2012 አገራዊ እና ክልላዊ ምርጫ ወቅቱን ጠብቆ እንዲካሄድ የሚገባው ሆኖ፤ ይህ ሳይሆን ቀርቶ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች ሉዓላዊ የስልጣን ባለቤትነታቸውን ተጥሶ የሚያዝ ፖለቲካዊ ስልጣን በምንም መስፈርት ተቀባይነት የሌለው መሆኑን በጥብቅ እናሳስባለን።
4. የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ህዝቦች ነጻነታቸውንና ደህንነታቸውን ተጠብቆላቸው በአገራቸው ተንቀሳቅሰው የመኖር፣ የመስራት፣ ሀብት የማፍራት ሕገ መንግስታዊ መብት አላቸው። ይሁን እንጂ በአሁኑ ጊዜ የኢትዮጵያ ዜጎች ሕገ መንግስታዊ መብቶቻቸው ተጥሶ በጅምላ እስከ መግደል የሚደርሱ ወንጀሎች እየተፈጸሙ መሆናቸውን እንገነዘባለን። ስለዚህም መንግስት በአፋጣኝ የዜጎችን መሰረታዊ መብቶች እና ነጻነቶች እንዲከበሩ ሕገ መንግስታዊ ግዴታውን እንዲወጣ እናሳስባለን።
5. ህብረብሔራዊ ፌደራሊዝም ስርዓቱን ከአደጋ መታደግ ኢትዮጵያን እንደ አገር ማስቀጠል በመሆኑ ሁሉም መንግስታዊ እና የግል መገናኛ ብዙሀን፣ የፍትሕ እና የፀጥታ ተቋማት፣ ሲቪክ ማሕበራት፣ የሀይማኖት ተቋማት፣ የወጣቶችና የሴቶች አደረጃጀቶች፣ እንዲሁም መላ ኢትዮጰያውያን ሕገ መንግስታዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ እንጠይቃለን።
ድል ለህብረ ብሔራዊ ፌደራሊስት ሀይሎች!
ሕዳር 24/2012 ዓ.ም
መቐለ
Filed in: Amharic