>

ዘመኑን በማይመጥኑ የእምሮ ድኩማኖች የኦሮሞ ወጣት ተስፋውን የሚያጨልመው ለምን ይሆን??? (መሳይ መኮንን)

ዘመኑን በማይመጥኑ የእምሮ ድኩማኖች የኦሮሞ ወጣት ተስፋውን የሚያጨልመው ለምን ይሆን???
ጋዜጠኛ መሳይ መኮንን
በወለጋ ሰዎች የተሞላው የኦነግ አመራር ቡድን አርሲዎችንንና ሸዋዎችን መቀበል አልቻለም። ግብግቡ የተጀመረው እነ ከማል ገልቹ የኤርትራን ምድር ከመርገጣቸው አስቀድሞ ነው። በኋላ ላይም ሁኔታው ያላማራቸው እነዳውድ ኢብሳ የሞት ፍርድ በይነው ሊገድሏቸው አቅደው ኤርትራውያኑ ጣልቃ ገብተው እንዳስጣሏቸው ሰምተናል!!!
#Ethiopia : አስመራ በገባን በሳምንቱ ነው። ልናገኛቸው እንደምንፈልግ ለኤርትራ ሰዎች ነገርናቸውና መልዕክት ላኩባቸው። ፍቃደኛ ሆነው ሊያገኙን እንደሚመጡ ገለጹልን። በኢሳት ሬዲዮ ላይ ለበርካታ ጊዜያት ቃለመጠይቅ ስላደረኩላቸው በቅርበት የማውቃቸው ያህል ይሰማኛል። ቀድሞ በአካል እንደተያየን ነገር ነበር የጠበኳቸው። እኔና ባልደረባዬ ፋሲል የኔዓለም በቀጠሮው ሰዓት ካረፍንበት ሆቴል የአስመራ ቢራ እየጠጣን ሰውዬውን መጠበቃችንን ቀጠልን። 500 ወታደሮችን አስከትለው፡ የህወሀትን ጥብቅ ሰንሰለት በጣጥሰው፡ የኤርትራን ድንበር አቋርጠው የገቡበት ገድል ሁሌም አድናቆት እንድሰጣቸው አድርጎኛል። የህወሀት ዙፋን ጠባቂ ሆኖ መቆየት አልፈለጉም። የወገኖቻቸው ህመም እረፍት ይነሳቸው ነበርና አጋጣሚው ሲመቻችላቸው ወታደሮቻቸውን ይዘው እብስ አሉ።
ሁለተኛ ቢራችንን እየተጎነጨን እያለ አንድ ጥብቅ ያለ ጂንስ ሱሪ የለበሰ፡ የቴክሳስ ጎረምሳ የመሰለ ቄንጠኛ ወጣት መሳይ ሰው ከሆቴላችን ሲገባ አየነው። በፍጹም የምንጠብቀው ሰው ይሆናል የሚል ግምት አልነበረንም። በፎቶግራፍ በወታደራዊ ዩኒፎርም የማውቀው ሰው እንዳልሆነ ለራሴ እርግጠኛ ሆንኩ። ሰውዬው አለባበሱ የማይክል ጃክሰንን ቄንጠኛነት የሚያስታውስ ነው። በአይኑ እያማተረ ሲፈልግ እኛን እንደሆነ አልገባንም። እንዴት ይሆናል? ያ ቆፍጥና ወታደር፡ ከየት መጥቶ እንዲህ የ20 ዓመት ጎረምሳ ገጽታ ሊኖረው ይችላል?! ግምታችን ልክ አልነበረም። ሁለት እጆቹን በጥብቆው ጂንስ ሱሪ ኪስ ውስጥ አድርጎ እየተንጎማለለ የገባው ሰው የሚፈልገው እኛን ነበር። ቢራችንን እየኮመኮምን የምንጠብቀው ሰው ፍጹም ባልገመትነው ቁመናና አለባበስ በቀጥሮው ቦታ ተገኝቷል። እሳቸው ናቸው። ሰውዬው። ብ/ጄነራል ከማል ገልቹ።
በሹክሹክታ እንደሰማነውና በአስመራ የቀናት ቆይታችን በሰፊው እንደተነገረን የኦነግ መሪዎች ትግሉን ትተውታል። አንድ ቁራሽ መሬት መቆጣጠር ሳይችል የጎልማሳ ሰው እድሜ የበላው የኦነግ ትግል አስመራ ላይ መልኩን ቀይሮ መሪዎቹ የኤርትራ መንግስት ባቀረበላቸው ቪላ ቤትና አውቶሞቢል እየተመነሸነሹ ሲዝናኑ ውለው ሲዝናኑ ያመሻሉ። ከብ/ጄ ከማል ገልቹ ጋር እያወራን የተረዳነው ይሄንኑ ነው። ኤርትራ ከገቡ ከመግለጫ ያለፈ በመሬት ላይ የሚያካሂዱት ትግል አንድ ስንዝር ወደፊት መራመድ ያልቻለበት ምክንያት ይገርመኝ ነበር። ብ/ጄ ከማል ወታደር ናቸው። የፖለቲካ ሰው አይደሉም። አለመሆናቸውን አሁን ላይ በሚገባ እያስመሰከሩ ነው። የአስመራው ትግላቸው እንደግመል ሽንት ወደኋላ የሆነበት ሚስጢርን ከእሳቸው ብሰማ ብዬ ጓጉቼአለሁ። ‘’ይሄው አስመራ ላይ ቢራ እየጠጣን ቁጭ ብለን ስምንት አመት አለፈን” ሲሉን እኔና ፋሲል ድንገት አይን ለአይን ተገጣጠምን።
ነገሩ እንዲህ ነው። 
ብ/ጄ ከማልና ብ/ጄ ሃይሉ ጎንፋ በሁለት አቅጣጫ አምስት መቶ ወታደሮችን ይዘው ኤርትራ ይገባሉ። የዛሬ 14 ዓመት። እቅዳቸው በስድስት ወራት በኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ውስጥ ያለውን የኦሮሞ ወታደር በማስኮብለልና ህዝቡም እንዲቀላቀላቸው በማድረግ አቶ መለስ ዜናዊን ማስወገድ ነበር። ሰውዬውን ኋላ ላይ ስረዳቸው በጣም ችኩልና መረጋጋት የራቃቸው ናቸው። እንደአቅማቸው ማሰብና መራመድ የሚችሉ አይደሉም። እናም አስመራ እንደደረሱ ለኤርትራ ባለስልጣናት ‘’በአስቸኳይ መሬት ስጡን፡ እኛ ወታደር እያሰለጠንን ኤክስፖርት በማድረግ ወያኔን በአጭር ጊዜ እናስወግዳለን። የእናንተ ድጋፍ መሬት በመስጠት ላይ የተወሰነ ብቻ መሆን አለበት። ሌላውን እኛ እንወጣዋለን’’ የሚል ሱሪ ባንገት ካላወጣሁ አይነት ጥያቄ ያቀርባሉ። ሰውዬው ፖለቲካ እንዳልገባቸው የሚያሳይ አንድ ማስረጃ የሚሆን ጥያቄ ነው። ወታደር ሸቀጥ አይደል ኤክፖርት ተደርጎ የሚዋጋው? ከኤርትራ ጋር ድንበርተኛ ባልሆነው በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ወታደራዊ እንቅስቃሴ ለማድረግ እንዲህ ዓይነት ስትራቴጂ ምን የሚሉት እብደት ነው? ኤርትራን መሬትሽን ብቻ የሚለው አካሄድ ለአቅመ ፖለቲካ ከደረሰ ሰው የሚጠበቅ አይደለም። ጄነራሉ ግን ደፋር ናቸው። ቀና ብለው ደረታቸውን ነፍተው የያዙት አቋም ለሌላው ያስደነግጣል። ኤርትራውያኑ ‘’ ጄነራል እባክዎትን ይረጋጉ። አብረን እንሰራለን። የአከባቢው ጉዳይ በተናጠል የሚሰራ አይደለም። እንነጋገርና በጋራ እንስራ’’ ብለው ይመልሱላቸዋል። ይሄን እንግዲህ የሚነግሩን ራሳቸው ብ/ጄ ከማል ገልቹ ናቸው።
አሻፈረኝ አሉ። ‘’ከእናንተ የምንፈልገው ወታደሮችን የምናሰለጥንበት መሬት ብቻ ነው። ሎጀስቲክም ሆነ ትጥቅ አናስቸግራችሁም። ራሳችንን እንችላለን።’’ ብ/ጄ ከማል ገልቹ በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ ስራ ሰርተናል ብለው በአደባባይ መናገር የጀመሩት እግራቸው አስመራ በረገጠ ማግስት ነበር። 30ሺህ የኦሮሞ ወታደሮችን መከላከያ ውስጥ አደራጅተናል ብሎ መደስኮር የሰውዬውን ክሽፈት ከማሳየት ያለፈ ትርጉም አልነበረውም። ፖለቲካ ራሱን የቻለ ሳይንስ መሆኑ ለጄነራሉ ቀልድ ሆኖ የሚታያቸው ይመስላል። ህወሀትን የመሰለ ሴረኛና ተንኮለኛ መንግስት አዲስ አበባ ላይ ተቀምጦ መከላከያ ውስጥ ስራ ሰርተናል ብሎ በአደባባይ ማወጅ በእርግጥም የፖለቲካ ድንቁርና እንጂ ሌላ የሚያሰኝ አይደለም። ብ/ጄ ከማል ይህን በተናገሩ ዕለት ህወሀት በሰራዊቱ ውስጥ ከመስመራዊ መኮንን ጀምሮ ያሉትን የኦሮሞ ተወላጆችን ሰብስቦ እስር ቤት አስገባቸው። የጄነራሉ ፉከራና ሽለለ ከጆሮአችን ጓዳ ሳይጠፋ ህወሀት በወታደራዊ ደህንነቱ አማካኝነት የጄነራሉን ሰንሰለት በመበጣጠስ ስውር እቅዱን ብትንትኑን አወጣው። ሂሳብ ብትሳሳት እርማት ትላለህ። እንግሊዘኛ ብትሳሳት እርማት ትላለህ። ፖለቲካ ብትሳሳት ግን ገደል ትገባለህ እንዲሉ ብ/ጄ ከማል ከእውቀትና ልምድ ማጣት ገና በጠዋቱ ፖለቲካው ካዳቸውና ትግሉን በብዙ እርምጃ ወደኋላ መለሱት። ችግሩ ሰውዬው ከዚህም የሚማሩ አለመሆናቸው ነው። አስመራ ከገቡም በኋላ በግትርነትና በብስለት ማጣት ሌላ ስህተት መስራት ጀመሩ።
ኤርትራውያኑ ባለስልጣናት አስመከሯቸው። አብረው ካልሰሩ በቀር ለብቻ የሚደረግ ትግል ውጤት አያመጣም በሚል በፊት ለፊትና በእጅ አዙር መልዕክት ሰደዱባቸው። ሰውዬው ወይ ፍንክች! ጥርሳቸውን በፖለቲካ የነቀሉትና ሴራውን መሬት ላይ በቅጡ ማንበብ የሚችሉት የሻዕቢያ መሪዎች ከሰውዬው ጋር ከዚህ በላይ መጓተት አልፈለጉም። እንዴት ማስተንፈስ እንደሚችሉ ያውቁበታል። ይዘውት የመጡትን ሰራዊት ወስደው በአሰብ አቅራቢያ አንድ ወታደራዊ ካምፕ ውስጥ አስቀመጧቸው። ከአዛዣቸው የተነጠሉት ወታደሮች ምንም ዓይነት ግንኙነት በማያደርጉበት ስፍራ እንዲቀመጡ ሲደረጉ ብ/ጄ ከማል የሚያዙትም የሚመሩትም ሃይል አጡ። ባዶ እጃቸውን ቀሩ። ቪላ ቤትና ቆንጆ አውቶሞቢል ተሰጣቸውና የአስመራ ቢራ እየጠጡ ከመቆየት ውጪ ምርጫ እንዳይኖራቸው ተደረጉ። በጎቹና እረኛው ሲነጣጠሉ የሚፈጥረው ክፉ ስሜት ብ/ጄ ከማል ገልቹን ያስቃያቸው ጀመር። ግትርነታቸው ዋጋ አስከፈላቸው። በፖለቲካ ጥልቀት የሌለው እውቀታቸው ከገደል አፋፍ አስጠጋቸው።
አሁንም ሰውዬው በፖለቲካው የሰሩትን ፋወል እየነገሩን ነው። እሳቸው ሲያወሩት በብሽቀት አይደለም። ስህተት ሰርቼአለሁ የሚል ጸጸት ሲያልፍም አይነካካቸውም። ደረታቸውን ነፍተው በጀብደኝነት የነገሩንን ሳይሆን ገልብጠን የተረዳነውን ነው እያከፈልኳችሁ ያለሁት። ከስህተት አለመማራቸው ሌላ ስህተት እንዲፈጽሙ እያደረጋቸው ነው። ዘንድሮም ከዚያ አዙሪት አልወጡም። በኋላም እሳቸውን ተከትሎ አብሮአቸው ኤርትራ የገባው ሰራዊት መበታተን ጀመረ። በእሳቸው እዝ ስር የነበሩና ከወራት ቆይታ በኋላ በተስፋ መቁረጥ ከአሰብ ካምፕ ወጥቶ አርበኞች ግንቦት ሰባትን የተቀላቀሉ የኦነግ ሻምበል አዛዥ እንዳጫወቱኝ ከሆነ ብ/ጄ ከማል የሰሩት ስህተት የሰራዊቱን ሞራል ሰብሮታል። እሳቸው አስመራ ቪላ ቤት ውስጥ ሲኖሩ ተከትሎአቸው የመጣው የኦነግ ሰራዊት ግን በረሃ በልቶት ገሚሱ ወደ ሀገር ቤት ሲገባ የተቀረው እዚያው አሰብ ውስጥ ይንከራተታል። ሰውዬው ግፍ ተፈጸመብኝ እንጂ በፖለቲካው ጨዋታ ተበለጥኩ ብለው እጅ የሚሰጡ አይደሉም። ንግግራቸው ሁሌም ፉከራ ይበዛዋል። ግትር መሆናቸውን አንድ አረፍተ ነገር ከአፋቸው እንደወጣ ማንም ሰው የሚረዳው ነው።
ብ/ጄ ከማል ባዶ እጃቸውን ከቀሩና ዩኒፎርማቸውን አውልቀው እንደቴክሳስ አራዳ ጂንስ ሱሪ ካጠለቁ በኋላ ብዙም ድምጻቸው አይሰማም ነበር። ከእነዳውድ ኢብሳ ጋር መቦጫጨቅ የጀመሩት በጊዜ ነው። ኦነግን የተቀላቀሉት ጄነራሉ ሁሌም መሪና አዛዥ የመሆን ስር የሰደደ ፍላጎታቸውን እነዳውድ ሊቀበሉት አልቻሉም። የመንደርና የጎጥ ጣጣም ሰዎቹ እንዲስማሙ አላደረጋቸውም። በወለጋ ሰዎች የተሞላው የኦነግ አመራር ቡድን አርሲዎችንንና ሸዋዎችን መቀበል አልቻለም። ግብግቡ የተጀመረው እነ ከማል ገልቹ የኤርትራን ምድር ከመርገጣቸው አስቀድሞ ነው። በኋላ ላይም ሁኔታው ያላማራቸው እነዳውድ ኢብሳ የሞት ፍርድ በይነው ሊገድሏቸው አቅደው ኤርትራውያኑ ጣልቃ ገብተው እንዳስጣሏቸው ሰምተናል። የኦሮሞን ህዝብ ነጻ እናወጣለን ያሉት ሰዎች አስመራ ላይ አንገት ለአንገት ሊቀነጣጠሱ መፋጠጣቸው ከምጸትም በላይ አሳፋሪ ክስተት ነው።
ብ/ጄ ከማል አብረዋቸው በረሃ ከወጡት ከብ/ጄ ሃይሉ ጎንፋ ጋርም መስማማት አልቻሉም። እሳቸው በአንደበታቸው እንደነገሩን ‘’ሃይሉ ትግሉን ትቶ የውጭ ኑሮን መረጠ። ስዊዲን ለመውጣት ፕሮሰስ ጀምሮ ሲስተጓጎልበት አንተ ነህ እንቅፋት የሆንክብኝ ብሎ ጠመደኝ።’’ እያሉ ብ/ጄ ሃይሉን ይወቅሳሉ። እንደሰማነው ደግሞ ሁለቱ ሰዎች ጠባቸው የብ/ጄ ከማል ግትርነት ነው። በስብሰባ ላይ ቡጢ መማዘዛቸውም ይነገራል። ብ/ጄ ሃይሉንም በሌላ ቀን እዚያው ሆቴል አግኝተናቸዋል። እንደከማል ችኩልና ግትር ባይሆኑም እሳቸውም በፖለቲካው ላይ ጠንከር ያለ ቁመና እንደሌላቸው ተረድተናል። አስመራ እንደሚወራው ኦነጎቹ በሞት ይፈላለጋሉ። ከማልና ሃይሉ አንድ ቦታ ላይ ከተያዩ ከዓይን ግልምጫ ባለፈ ለድብድብ እንደሚቃጣቸው ይነገራል። አንድ ጠረጴዛ ላይ ገበታ መቅረብ ይቅርና አንዱ ባለበት አንደኛው መታየትን አይፈልግም። አይንና ናጫ፡ እሳትና ጭድ ሆነው ነው ስምንቱን ዓመት በአስመራ የቆዩት። እነዚህ ሰዎች ናቸው እንግዲህ ለታላቁ የኦሮሞ ህዝብ ነጻ እናወጣሃለን የሚል መሃላ እያዥጎደጎዱ በገቢር ራሳቸውን ከአስተሳሰብ ድህነት ነጻ ማውጣት ተስኗቸው በሀገር ኤርትራ የኦሮሞን ህዝብ እያዋረዱት የዘለቁት።
ብ/ጄ ከማል የኋላ ኋላ በኤርትራ ቢራ እየጠጡ መቆየት መረራቸውና በስምምነት ወደሌላ ሀገር ለመሄድ ጥያቄ አቀረቡ። የኤርትራ ባለስልጣናት ሁኔታዎችን አመቻቹላቸውና ወደ ኡጋንዳ ሄዱ። አንድ ጥይት ሳይተኩሱ፡ አንድ ጋት መሬት ነጻ ሳያወጡ፡ የኤርትራን ምድር የለቀቁት ብ/ጄ ከማል ኡጋንዳ ገብተው አዲስ ያቋቋሙትን የነጻ አውጪ ድርጅት እየመሩት መሆኑን ገለጹ። ከህወሀት ወታደራዊ አዛዥነት ወደ ኦነግ አማጺ ሰራዊት መሪ፡ በኋላም የኢትዮጵያ ነጻ አውጪ ሃይል ከመሆን በብርሃን ፍጥነት ተመልሰው የኦሮሞ ነጻ አውጪ ግንባርን በሌላ ስም ይዘውት ኡጋንዳ ገቡ። የሰውዬው ድንግርር ያለ፡ እውቀትና ብስለት የራቀው እንቅስቃሴ ኡጋንዳ ሆኖ አማጺ ቡድን አደራጀሁ ብሎ መደስኮር ነው። በብዙ ሺህ ኪሎሜትሮች ርቀው፡ ከካምፓላ የተቀመጡት ብ/ጄ ከማል በኤርትራ ያላሳኩትን የነጻ አውጪ ተልዕኮአቸውን በኡጋንዳ ሊሞክሩት ጥሪ አደረጉ። እንደምኞታቸው አልተሳካላቸውም። እዚያው እንደተቀመጡ፡ ከሽለላና ቀረርቶ ሳይላቀቁ፡ በእነ አብይና ለማ ጥሪ ወደ ሀገር ቤት ተመለሱ። በእግር በርሃ አቋርጠው ከሀገር የወጡትን ሰው እነ አብይ በክብር በአውሮፕላን በቦሌ በኩል እንዲገቡ አደረጓቸው።
ሰውዬው ወደሀገር ቤት ሲገቡ የወቅቱ የፉክክርና የእኔ እበልጥ ፖለቲካ ያስከተለው ሙቀት የጀግና አቀባበል እንዲደርግላቸው እድል ፈጥሮላቸዋል። መሬት ከጠላት እያስለቀቁ፡ ከተማ እየተቆጣጠሩ፡ ጦራቸውን ይዘው ከአስመራ ውደ አዲስ አበባ በድል አድራጊነት እየገሰገሱ የገቡ ይመስል በጠዋቱ ትዕቢትና እብሪት ያጠላበት ንግግር ማድረግ ሲጀምሩ ነበር ትዝብት ላይ የወደቁት። እነለማም ቢያንስ አስተዋጽኦ አድርገዋል በሚል አክብረዋቸው የኦሮሚያ ክልል የጸጥታ ቢሮ ሃላፊ እንዲሆኑ ሹመት ሰጧቸው። ለቦታው የሚመጥን የፖለቲካም ሆነ የእውቀት ዝግጅት ያልነበራቸው ብ/ጄ ከማል መንግታዊ መዋቅሩን ተጠቅመው ማህተም እንኳን የሌለውን አዲሱን የነጻ አውጪ ድርጅታቸውን ፖለቲካዊ ስራ በሽፋን መስራቱ ላይ ተጠመዱ። አስመራ ላይ የሞት ፍርድ የፈረዱባቸውን እነዳውድ ኢብሳን የሚበቀሉበትን አጋጣሚ የተፈጠረላቸው መሰላቸውና እግር በእግር እያሳደዱ ማዋከብ ጀመሩ። የመንግስትን ስራ ወደ ጎን ትተው በሾሟቸው የኦዲፒ መሪዎችና የኦነግ አመራሮች ላይ ሴራ መጎንጎኑ ላይ በግልጽ መስራታቸውን ቀጠሉ። ኦነግ ወደ ሀገር ቤት የገባበትን ስምምነት ያፈረሰ ሲል የብ/ጄ ከማልን ሹመት ተቃወመው። መጠላለፉ አስመራ ላይ ሳይቋጭ በአዲስ አበባም ቀጠለ። በኋላ ነገሩ ያላማራቸው አቶ ለማ መገርሳ በአንዲት ብጣሽ ወረቀት ከሃላፊነት አሰናበቷቸው።
ብ/ጄ ከማል ገልቹ በይፋ የለውጡን ሃይል መገዝገዝ የጀመሩት ብጣሿ የስንብት ደብዳቤ እጃቸው ከገባች ዕለት ጀምሮ ነው። አንድ የሚያዙት ወታደር ሳይኖራቸው፡ የኦሮሞ ወጣትን ተማምነው የጦርነትና የዕልቂት ጥሪ መጎሰምን ስራዬ ብለው ተያያዙት። በ48ሰዓታት የአብይን መንግስት ማፈራረስ እንችላለን ብለው ሲፎክሩም ሰማናቸው። ሰሞኑንም ኦሮሚያን በኮንፌደሬሽን ከእናት ሀገሯ ለመገንጠል ህልም እንዳላቸውና ይህንን ህልማቸውን የሚያስቆም ምድራዊ ሃይል እንደማይኖር ማይክ ጨብጠው ሲፎክሩ የሚታዩበት ቪዲዮ በማህበራዊ መድረኮች ላይ በስፋት ተሰራጭቷል። በካምፓላ እንቅልፋቸው ሲለጥጡ የነበሩትን ሰው በክብር ወደ ሀገራቸው እንዲገቡ ያደረጓቸውን የለውጥ መሪዎች በኦሮሞ ጠላትነት በመፈረጅ ህዝብ እንዲነሳባቸው ግልጽ የሆነ የጦርነት ነጋሪት መጎሰማቸው ስሰማ የሰውዬው መጨረሻ ምን ይሆን ብዬ ራሴን ጠየኩ።
ብ/ጄ ከማል የጎረሱበትን እጅ መንከሳቸው ለህሊናቸው ሰላም እንጂ ጸጸት እንደማይሰጣቸው ያስታውቃሉ። ሲፎክሩ እስከአፍንጫው የታጠቀ አንድ ባታሊዮን ጦር የሚያዙ ነው የሚመስሉት። የኦሮሞ ፖለቲካ የዚህ ዓይነቱ ጨለምተኛ፡ እውቀት አጠር፡ ገታራና ቆሞ ቀር ሰዎች የሚፈነጩበት መሆኑ የሚያሳዝን ነው። በእነዚህ የድንጋይ ዳቦ ዘመን አስተሳሰብ ባጠቃቸው የፖለቲካ ደሀ በሆኑ ፖለቲከኞች የኦሮሞ ወጣት የነገውን ተስፋ የሚያጨልመው ለምን ይሆን የሚል ጥያቄ እንድናነሳ ተገደድን። በእርግጥም ለእነዚህ የስልጣን ጥመኞች እርካታ ሲባል የስንት ሰው ህይወት መቀጠፍ አለበት? የራሳቸውን ዘመን በከንቱ አበላሽተው በነገው ትውልድ ህይወት ላይ ቁማር የሚጫወቱ መሰል ግለሰቦች ከእንግዲህ እድሉ እንዳይሰጣቸው የማድረግ ሃላፊነት የዘመኑ ትውልድ አይደለምን?
Filed in: Amharic