>

አማራነትን ሣይሆን አማራዊነትን ያዙና ኢትዮጵያን አድኑ! (ሰሎሞን ንጉሡ)

አማራነትን ሣይሆን አማራዊነትን ያዙና ኢትዮጵያን አድኑ!

ሰሎሞን ንጉሡ

መንፈሴ በል ያለኝን እናገራለሁ፡፡ ኢትዮጵያችን ክፉኛ ታማለችና የሚመለከታችሁ ሁሉ ፈጥናችሁ እንድታድኗት በልጆቻችን ስም እማጸናችኋለሁ፡፡ እኔን መሰል የዕድሜ ባለጠጋ ከመናገርና ከመጻፍ ውጪ ሌላ ይህ ነው የሚባል አስተዋፅዖ እምብዝም የለውም፡፡ ኢትዮጵያን ከተደቀነባት አደጋ ለመታደግ ግን በተለይ ወጣቶችና በሳል ጤናማ ምሁራን ጉልኅ ሚና መጫወት ይችላሉና ጊዜው ብዙም ሳይመሽ ቢጥሩ መልካም ነው፡፡ ተሰሚነት ያላችሁና ማኅበራዊ ተፅዕኖ ማድረግ የምትችሉ እንደ ታዬ ቦጋለ፣ ኅሊና ደሣለኝ፣ “ሙክታሮቪች”ና መሰል ዜጎች ዕንቅልፍና ዕረፍት ሳያምራችሁ ሀገራችንን ከሦርያዊነትና ሶማሊያዊነት ዕጣ አድኗት፡፡ ይህን ዕድል ካሣለፍነው ለጸጸት እንኳን ጊዜ የሚኖረን አይመስለኝም፡፡ የሰሙነ ህማማት ማብቂያ ዐርብ ከሰዓት ላይ ነን፡፡ እሁድ ሲመጣ ወደ ቀኝ እንነሣ ወደ ግራ አናውቀውም፡፡ ዕድል ደግሞ 50፣50 ነው፡፡ ሦርያውያን የ“ምነው በዕንቁላሌ በቀጣሽኝ”ን ሙሾ እያወረዱ በጸጸት መነፋረቅ ከጀመሩ አሥር ዓመታትን ሊደፍኑ ነው፡፡ አስተዋይ ሰው ከሰው ጠባሣ ይማራል፤ ሞኝ ሰው ግን ከራሱ ጠባሣም አይማርምና ከሞኝነታችን በአፋጣኝ እንላቀቅ፡፡ “ጨው ለራስህ ስትል ጣፍጥ” ነው ተረቱ…

በአሁኑ ወቅት እጅግ ብዙ ዜጎች በቤቶች ድራማ ገጸ ባሕርይ በእከደከን ማን ችሎት ቋንቋ ለሽ ብለው ተኝተዋል፡፡ ውጪ ሀገር ያሉትም በሀገር ቤት ያሉትም በጠሊቅ እንቅልፍ ውስጥ ናቸው፡፡ የነገ ጣጣችን ገብቷቸው የሚጨነቁና የሚጠበቡ በዚያም ምክንያት ያለ ዕረፍት የሚታትሩ ዜጎች ከጠቅላላው ሕዝብ አንጻር ሲታዩ እጅግ ኢምንት ናቸው፤ ይህ ሁናቴያችን ክፉኛ ያሳስባል፡፡ “ምን ነካን?” በሚል ጤንነታችንንም ጥያቄ ውስጥ መክተቱ የማይቀር ነው፡፡ ለብዙዎች ዝምታ ሰበቡ ምናልባትም ሁሉንም ነገር ለፈጣሪ ሰጥተው እርሱ ራሱ እንደፍጥርጥሩ ያድርጋት ብለውም ሊሆን ይችላል፡፡ ምናልባትም ከችግሮች መወሳሰብ አኳያ ተስፋ ቆርጠው ሊሆንም ይችላል፡፡ ምናልባትም “እኔ ምን ማድረግ እችላለሁ? ምንስ አቅም አለኝ?” ብለው ራሳቸውን በአቅመ ቢስነት በመፈረጅ ለቀንና ለታሪክ ፍርድ ትተዋትም ሊሆን ይችላል – ይሄም ያው ተስፋ እንደመቁረጥ ነው፡፡ ዋናው ግን ሀገራችን ካምሱሩ የተፈታ ቦምብና ፈንጅ ላይ ተቀምጣ እያዩ ምንም ነገር ላለማድረግ የወሰኑ ዜጎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከተ መምጣቱ እውነት ነው፡፡ መፍትሔው መሸሽ እየመሰላቸው በቦሌም በባሌም በየቀኑ ወደ ውጭ የሚጓዙ ዜጎችም ብዙ ናቸው፡፡ ይህ ሁሉ ያስጨንቃል፤ እጅጉን ያሳስባልም፡፡

ምንም ልባል ምን እኔ ግን እናገራለሁ፡፡ ዝም አልልም፡፡ “ሩጫየን ጨርሻለሁ” በሚልም ይሁን በሌላ በማላውቀው ምክንያት የተነሣ አንዳንድ እያሉ ከአግልግሎታቸው እየወጡ ያሉ፣ አቋማቸውን በ“ዩ ተርን” (በቀኝ ኋላ ዙር?) ወደ አዲሶቹ ኦነጋዊ ወያኔዎች የለወጡ እንዲሁም እንደመስቀል ወፍ በስንት ጊዜ አንዴ ብቅ የሚሉ ሚዲያዎችም ሲፈልጉ ያስተናግዱኝ፡፡ ካልፈለጉም በ15 ቁጥር ምስማራቸው ጥርቅም አድርገው ይዝጉኝ፡፡ ለምጄዋለሁና ግዴለኝም፡፡ ሰው በወደደው የሚቆርብ በመሆኑ እንደየአመለካከቱና እንደየእምነቱ ይራመድ፡፡ ከአጥፊነት ለመቆጠብ ግን ይሞክር፡፡ የተቻለው እሳቱን ለማጥፋት ውኃ በማቅረብ በትግሉ ሂደት ይሣተፍ፡፡ ክብሪት ለኳሾችም ልብ ሰጥቷቸው አብረን ከመንደድ ይልቅ ከዕቶኑ የምንተርፍበትን መንገድ ይቀይሱ፡፡ ያም ይቻላል፡፡ በጣም ይቻላል፡፡ ካልተጠበቀ ተጨማሪ ኪሣራም ይታደገናል፡፡ ከሽንትና ከዕዳሪነት ለማያልፍ ምድራዊ ሀብት ብለው ለታሪካዊ ጠላቶቻችን አሽከርና ባንዳ ሆነው ወገናቸውን በከንቱ አያስጨርሱ፡፡ ከጥፋት መንገዳቸው በጊዜ ካልተመለሱ መጨረሻቸው ከኛም የከፋ እንደሚሆን ይረዱ፡፡ የዛሬ ገንዘብና ሰይጣናዊ ዝና ለነገ ስንቅ አይሆንም፡፡

ቀጥዬ የምለው ትልቅ ቁም ነገር ነው፡፡

ኢትዮጵያን ለማዳን አማራዊነት እጅግ ፍቱን መድኃኒት ነው፡፡ በየጎጡ የመወተፍን ውጤት ባለፉት 30 እና 40 ዓመታት በደምብ አየነው፡፡ ወያኔዎች በገቡ ሰሞን ነው – በፖስታ ቤት ውስጥ የምትሠራ አንዲት ትግራዋይ ለአንድ ትንሽዬ ዕቃ ለቀረጥ ይሁን ለሌላ የክፍያ ርዕስ አንዷን ትግራዋይ ከ40 ብር ወደ 40 ሣንቲም እንድትከፍል አድርጋለች – ይህ የሆነው በመስኮት የቆመችው ሴት በተጠየቀችው ክፍያ መብዛት የተነሣ “ቧይ!” ስላለችና ወያኔይቱ የፖስታ ቤት ሠራተኛ “ትግራወይቲ ዲኺ” ብላ ስትጠይቃት የ“ጠራች” ትግሬ ሊያውም ዐድዋ መሆኗን በትግርኛ ከነገረቻት በኋላ የቀደመውን ሠርዛ የቀጠለውን ታሪፍ በሰጠቻት ጊዜ ነው፡፡ ይህን መሰል ተዘርዝሮ የማያልቅ ወያኔያዊ ዘረኝነትን መሠረት ያደረገ አድልዖ በሀገራችን ብዙ አይተናል፤ (ይህ እንግዲህ ሕወሓቶች በታሪክ መዝገብ ላይ ካስቀመጡት በየእሥር ቤቶች የፈጸሙት የሚዘገንን ግፍና በደል፣ ሀገራዊ ዘረፋና ሙስና በተጓዳኝ መሆኑ ነው)፡፡ የአሁኑን የኦህዲድ/ኦነግን አስቂኝና አስገራሚ ድራማም ገና ከጅምሩ እያየነው ነው፡፡ ግም ለግም ተያይዘይው እያዘገሙ ሀገራችንን መሣቂያና መሣለቂያ እያደረጓት መሆናቸውን ሳንወድ በግዳችን እየተከታተልን መታዘባችንንና ለወደፊት የታሪክ ፍጆታ በድርሳናት ማኖራችንን ቀጥለናል፡፡

በአማራዊነት ግን እንዲህ ያለ ቅሌት እምብዝም አናስተውልም፡፡ እንደሚባለውም አማራነት በኢትዮጵዊነት ውስጥ በመቅለጡ አማራ በአማራነቱ ከአማራ የሚያገኘው አንዳችም ልዩ ጥቅም የለም፡፡ እውነቱን መናገር ኃጢኣት አይደለም፡፡ ለምሣሌ አንድ ሀብታም አማራ ባለሙያ ሲቀጥር አሁን አሁን እንጃ እንጂ በተለይ ቀደም ባለው ዘመን “ከየት ነህ?” ብሎ አይጠይቅም፡፡ ባህሉም፣ ሃይማኖቱም፣ አስተዳደጉም፣ ሥነ ልቦናውም ለዚህ “አላደለውም”፡፡ ይህ ጠባዩ ባለፉት 30 እና 40 ዓመታት በተወሰነ ደረጃ እንደጎዳው መገመት አያስቸግርም – የሚካስበት ዘመን መምጣቱ የሚጠበቅ ነውና ግን ግዴለም ይጉዳው፡፡ የሌሎችን ግን አሁንም ድረስ የምናየው ነው፡፡ ይህ የዘረኝነት ወይም የጎጠኝነትና የጎሠኝነት ደዌ ሀገራችንን እያሽመደመዳት በመሆኑ ብቸኛ መፍትሔው ታዲያንስ አማራዊነት ነው – አማራነት አላልኩም!

በመሠረቱና እንደእውነቱ ከሆነ አማራ ሆኖ ከአማራ ቤተሰብ መወለድ የአጋጣሚ ጉዳይ እንጂ የምርጫ ጉዳይ አይደለም፡፡ በሌሎቹም ጎሣዎች ውስጥ መወለድ እንደዚሁ ነው፡፡ እናም ወደንና ፈቅደን ባልተወለድንበት የዘር ጣጣ ውስጥ ተዘፍቀን ልንለያይበት ባልተገባ ነበር – ከጅምሩ፡፡ ዕድላችን ሆኖ ወደዚያ አጥር ውስጥ ከገባን አማራን በሆነ ነገር በመጥላታችን ምክንያት አማርኛንና አማራነትን ብንጠላም ከኢትዮጵያዊነት የጋራ ዕሤቶች አኳያ ግን አማራዊነትን ለስትራቲጂዊ ጠቀሜታ ብለን ብንይዝ ከመበታተንና ከመጥፋት እንድናለን፡፡ ወደ አንድ የአማራ ባለሥልጣን ዘንድ ሂድ – የምለውን ለመረዳት ከፈለግህ፡፡ “አማራ ነኝ፡፡ እንዲህ እንዲህ ያለ ውለታ እንድታደርግልኝ እፈልጋለሁ፡፡ እባክህን …” በልና ፀጉርህን ባምስት ጣትህ እያሻሸህ ለምነው፡፡ ይስቅብሃል፡፡ እንዲህ ያለ ነገር እኔ በማውቀው አማራ ዘንድ የለም፤ ነውርም ነው፡፡ ባይሆን በመንዜነትህ፣ በጎንደሬነትህ፣ በአቸፈርነትህ… መጠነኛ ግን ከችሎታህና ብቃትህ ጋር በተገናኘ መልኩ የምታገኘው ነገር ሊኖር ይችል ይሆናል፡፡ በቋንቋ? በአማራነት? ፈጽሞ! እንዳንኮነን፡፡ (Of course, I don’t want to deny the existence of exceptions, for, as the saying has it, ‘every generalization has an exception’.) በተረፈ አንዳንድ በዱሮ ዘመን በአንዳንድ ፊዩዳሎች እንደተፈጸሙ የሚነገሩ ግለሰባዊ በደሎች እንዳሉ ሆነው ሰፊው የአማራ ሕዝብና ኤሊት ግን ጠላቶቹ የሚያወሩበትንና የሚያስወሩበትን ያህል አጥፊና በዳይ እንዳልሆነ መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

አማራ የሚመካበት ሌላ ሀገርም ሆነ ጎጣዊ ማንነትና ስሜት የለውም፡፡ በቅርብ “አብን” ብለው የወጡ ወጣቶችን እንርሳቸው፡፡ ጊዜ የወለዳቸውና ምናልባትም ሁኔታዎች እየተሻሻሉ ሲመጡ በገዛ ፈቃዳቸው የሚከስሙ የወያኔያዊ ፍልስፍና ውጤቶች ናቸው፡፡ በመላ ሀገሪቱ በደምም በአጥንትም ተዋህዶና ተወራርሶ የሚኖርን አማራ በአማራነት ስሜት ማደራጀት የሚቻል አይመስለኝም፤ አይሆንምም፡፡ ከፈጣሪም ከምድርም ህግጋት ባፈነገጠ ሁኔታ በዘር ተደራጅቶ ጊዜያዊ ግርግር መፍጠርና የተወሰኑ ድሎችንም ማስመዝገብ አይቻልም ማለት እንዳልሆነ ግን ከአብን አነሳስና አካሄድ መረዳት ጠቃሚ ነው፡፡ ሰው በቁስሉ ስትመጣበት አበረታች አጸፋዊ ምላሽ አታጣም፡፡ እንዲህ ስል ደግሞ አብንን መቃወሜ እንዳልሆነ ይታወቅልኝ፡፡ አንዳች መጥፎ አጋጣሚ ሌላ ያልተፈለገ መጥፎ አጋጣሚ መፍጠሩን ማስታወስ ተገቢ ነው፡፡ እሾህን በእሾህ እንዲሉ ዓይነት ለጊዜውና ነገሮች መስመር እስኪይዙ ድረስ አስፈላጊ መጥፎ (necessary evil) በሚባል ደረጃ የአብንን መኖር የሚደግፉ እንዳሉ በግሌ እረዳለሁ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን አማራ ከሌሎች ወንድምና እህቶቹ ጋር ድርና ማግ ሆኖ የፈጠራት ኢትዮጵያ አማራን ባገለለና ባላሣተፈ መልክ ማንም መሠሪ በራሱ ፍላጎት ቀርፆ የሚያቆማት ገዳዳ ኢትዮጵያ እውን ትሆናለች ብሎ ማሰብ ከቅዠት አይተናነስም፡፡ እርግጥ ነው – “ከመረቁ አውጡልን፤ ከሥጋው ጦመኞች ነን” ባይ አንዳንድ አንጋፋ አማራ ጠል ፖለቲከኞች በአንድ ራስ ሁለት ምላሶችን ይዘው እዚያና እዚህ በሚናገሯቸው እርስ በርስ የሚቃረኑ መልእክቶቻቸው አማራን በቅጡ ያላካተተች ኢትዮጵያን ለመፍጠር ላይና ታች እንደሚሉ እናውቃለን፡፡ ይህ የሌሊት ወፍን መሰል አስቀያሚ ዘመን ሲያልፍ የምናወራው “ምሥጢር” ነው ይሄ እንኳን፡፡

የሆኖ ሆኖ ማንኛውም ለኢትዮጵያ እጨነቃለሁ የሚል ዜጋ ከየትኛውም ጎሣ ቢወጣ በስሜት ልክ እንደአብዛኞቹ አማራና ኢ-አማራ አማራውያን ለአንዲት ሀገር ሕዝብ ኅልውና መቆም ከፈለገ አማራዊ አስተሳሰብ ቢኖረው ሀገርን ከጥፋት ይታደጋል፡፡ ጎሣዊ መንጋደድ እያደረሰ ያለውን አጠቃላይ ውድመት እያየነው ስለሆነ ጥቂት ወሮበሎችን እንጂ እኛን ብዙኃኑን አልጠቀመንም ብቻ ሣይሆን ክፉኛ እየጎዳንና የጋራ ኅልውናችንን መሠረት እየሸረሸረው ነው፡፡ በመሠረቱ አማሮችን በጅምላ መጥላት ዕብደት ነው፤ ከዕብደት በላይ ሌላ ቃል ማከል አግባብ አይደለም እንጂ በደምሳሳው አንድን የሰው ዘር ሐረግ መጥላት ወንጀልም ኃጢኣትም ድንቁርናም ነው፡፡ አንድ ጎሣ ወይም ማኅበረሰብ በጅምላ አይጠላም፡፡ አጎናፍር በፈጸመው ጥፋት አዝብጤ ከተወቀሰ ወቃሹ ከሌሎች እንስሳትም ያነሰ ድምባዣም ነው፡፡ ከብት ባልዋበት ኩበት አይለቀምም፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ ደቻሣ ላጠፋ ጉርሜሣ፣ ሐጎስ ላጠፋ ፍትዊ፣ መሀመድ ባጠፋ ዑመር፣ ገ/ክርስቶስ ባጠፋ ገ/ጂዎርጂስ፣ ሻሽቱ ባጠፋች ጠጂቱ የሚወቀሱ ከሆነ ከእንስሳነትም መውረድ ነው፡፡ ይሄ ዓይነቱ ችግር ነው እንግዲህ ሀገራችንን ሰቅዞ የያዛት፡፡ ጥሩ ትግሬዎች እንዳሉ መጥፎዎችም አሉ፡፡ መጥፎ አማሮችና ኦሮሞዎች እንዳሉ ጥሩዎችም ሞልተዋል፡፡ ይህ አንዱን በሌላው እየተካን የምንሰጠው አጉል ፍረጃ ሀገራችንን እንጦርጦስ እያወረዳት ነውና ቆም ብለን ማሰብ አለብን፡፡ ደግሞም የዛሬ 200 እና 300 ዓመት በተፈጸመ የየትኛውም ወገን ጥፋትና ስህተት ዛሬ ላይ መነታረክና ሌላ ጥፋት ማድረስ ሰው ነኝ ከሚል ምክንያታዊ ሊሆን ከሚገባው አሳቢ ፍጡር አይጠበቅምና ከዚህ ዓይነቱ መሣቂያና መሣለቂያ አድራጎትም እንቆጠብ፡፡ እመት አህይት “አያ ጅቦ ሳታመካኝ ብላኝ” ያለችው እውነቷን ነው፡፡

በአጭሩ አማራዊነትን እናጠናክር፡፡ አማራዊነትን ማጠናከር አማራ መሆን ማለትም አይደለም፡፡ መልካም ነገር ቢኮረጅ ጠቃሚነቱ ሚዛን እስከደፋ ድረስ ክፋት የለውም፡፡ ያደለው ከአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ጠባብ አስተሳሰብ ወጥቶ ኮዝሞፖሊታን/ዩኒቨርሳል የሆነ አስተሳሰብን ይላበሳል እኛ ግን እዚችው ጎጣችንና ሸጣችን ውስጥ ተወትፈን ፍዳችንን እናያለን፡፡ ሰው እንሁን እንጂ! ማን እስኪቀሰቅሰን እንጠብቃለን?
* * *
10 አክሎም እንዲህ አላቸው፦ “ወደ አንድ ቤት ስትገቡ አካባቢውን ለቃችሁ እስክትሄዱ ድረስ እዚያው ቆዩ። 11 ነገር ግን የሚቀበላችሁ ወይም የሚሰማችሁ ካጣችሁ ከዚያ ቦታ ስትወጡ ምሥክር እንዲሆንባቸው የእግራችሁን አቧራ አራግፉ።” 12 እነሱም ከዚያ ወጥተው ሰዎች ንስሐ ይገቡ ዘንድ ሰበኩ፤ 13 ብዙ አጋንንትም አስወጡ፤ እንዲሁም ብዙ ሕመምተኞችን ዘይት እየቀቡ ፈወሱ። ማርቆስ 6፡ 10 – 13

ሰሎሞን ንጉሡ (khartoum71@gmail.com)

 

Filed in: Amharic