>
5:13 pm - Wednesday April 20, 3205

የትግራይ ብሔረተኞች በአማራ ላይ ያላቸው ጥላቻ ከምን የመነጨ ነው?”  (ክፍል ሦስት - ጌታቸው ረዳ )

የትግራይ ብሔረተኞች በአማራ ላይ ያላቸው ጥላቻ ከምን የመነጨ ነው?” 
  (ክፍል ሦስት)
– አሰፋ ሃይሉ– ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ ጌታቸው ረዳ (ኢትዮጵያን ሰማይ አዘጋጅ)
(Ethiopian Semay:  http://ethiopiansemay.blogspot.com/  )
«የማንበብ ችሎታ እያለው ምንም የማያነብ ሰው፥ የማንበብ ችሎታ ከሌለው ሰው እኩል ተደርጎ ይቆጠራል።»
 ( – ማርክ ትዌይን፥ አሜሪካዊ ደራሲ)
ኑ ፡ እውነትን ፡ እናንብብ !  |  {የዕለቱ መልዕክት}
… ምኒልክ በ1882 ዓ.ም ወደ ትግራይ ሲመጡ፤ የዮሐንስ ዘሮች የሆኑ መሳፍንቶች እና ተወልጄዎቹ አንዲህ ባለ ተቃውሞ ሲገልጹ፤ ሕዝቡስ ምን ዓይነት ስሜት እና ቅሬታ አንጸባርቆ ነበር?
/ጌታቸው ረዳ …ካለፈው የቀጠለ/
አሁን ወደ ዋናው የትግራይ ብሔረተኛነት ስሜት በግልጽ ለመጀመርያ ጊዜ በሕዝቡ ልቦና የተቀረጸበት እና የታየበት ወቅት እወስዳችሗለሁ::
አጼ ዮሐንስ ከሞቱ በኋላ ራስ መንገሻ ዮሐንስ እና የመሳሰሉት የትግራይ ገዢዎችን ከአዲሱ ጉልበተኛ እና ጥበበኛው ንጉሥ ምኒልክ ጋር በፈጠሩት ቅራኔ ‘ሥልጣኑን ትግራይ ውስጥ ለማቆየት የአካባቢው ገጠሮች ከምኒልክ ሠራዊት ጋር ያካሄዱት መጠነኛ ፍትግያ/ውግያ ሲደረግ የዓይን ምስክር የነበሩ “ይሓ” (ዓድዋ) ውስጥ የተወለዱ የትግራይ ተወላጅ የሆኑት “ታሪኽ ኢትዮጵያ” የሚል በእጅ ጽሑፍ በ1891 (ኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር) በናፖሊ/ ጣሊያን አገር የተጻፈ ባለ 169 ገፅ የያዘ ብደብተራ ፍስሐ ጊዮርጊስ ዓቢየዝጊ የጻፉት በትግርኛ እንደመግቢያ አንዲህ የጻፉትን ላንብላችሁ። በአማርኛ የተረጎምኩትም አነበዋለሁ።
“….ሽዕቱ ገጽ ሸወታይ ጥምት አቢልካ ናብ ገጽ ትግራዋይ ቁልሕ እንተበልካ ዳርጋ ክንዲ ናይ ለይትን ናይ ቀትርን ዚአክል ምፍልላይ ይርኤ ነበረ” (ታሪኽ ኢትዮጵያ ገጽ ፻፴፬ (134) ደብተራ ፍስሐ ዓብየዝጊ ናፖሊ/ኢታሊያ-1891/ ብአውሮጳዊያን ዘመን 1899)
ወደ አማርኛ ሲተረጐም፤
“ያኔ የሸዌዎቹ ገጽታ ተመልክተህ ወደ የትግሬው ሰው ገጽታ ፊትህን ዞር ብለህ ስትመለከት የምትታዘበው የሁለቱ ሰዎች ገጽታ ልዩነት ልክ የቀን ብርሃን እና የሌሊት ጨለማ የገጽታ ልዩነት ይታይ ነበር።” (ታሪኽ ኢትዮጵያ ገጽ ፻፴፬ 134) 1891/ ኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር (1899/አውሮጳ ዘመን) ደብተራ ፍስሐ ዓብየዝጊ ናፖሊ/ኢታሊያ) ትርጉም (የኔ)።
ከላይ የጠቀስኩት ግልጽ ስዕል ምን ማለት እንደሆነ እና በወቅቱ የታየው የወደፊት መጻኢ ባሕሪው ወዴት እንደሚወስድ እና አሁን ካለው ነባራዊ ክስተት ስታገናዝቡት የወያኔዎች የገጽታ ተማሳሳይ ቅጅ ምንጩ “ያቺኛዋ ወቅት” እነደሆነች መገንዘብ ትችላላችሁ።
ከላይ የተመለከተው የታሪኩ አጭር ዝርዝሩ በአማርኛ የተረጎምኩትን እነሆ ፡-
“ራስ መኮንን ለዲፕሎማሲያዊ ስራ በአፄ ምኒልክ ናፖሊ/ከጣሊያን አገር ደርሰው በምፅዋ አድርገው ወደ መቀሌ ከተማ ሲገቡ አጼ ምኒሊክም መቀሌ ከተማ ውስጥ ስለነበሩ ራስ መኮንን ለመቀበል ደራሲው ደብተራ ፍስሃም በግራዝማች ዮሴፍ ስር ስለነበሩ ከሳቸው እና ከነደጃች ስብሐት እና ከመሳሰሉት ከትግራይ መኳንንት ጋር ሆነው ራስ መኮንን ወደ መቀሌ ለማጀብ ወደ ከተማዋ የሚወስደው ቁልቁል መንገድ ሲደርሱ (የመሶቦ ዳገት/ ቁልቁለቱ ማለታቸው ነው) እንዲህ ይላሉ።
“ለደጃች ሥዩም ገብተው የነበሩ የተምቤኑ ደጃዝማች ሐጎስ ከሳቸው ጋራ የነበረው ተፈሪ የተባለ ዘመዳቸው አብሯቸው በነበረበት ወቅት ‘ሁለት ሰናድር’ ይዞ ወደ ግራዝማች ዮሴፍ በመግባቱ ‘አጠፋህልኝ’ ብለው ተማጸኑት። ዳኛውም ራስ መኮንን ሆኑ። ያኔ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት አፄ ምኒሊክ ናቸው። ተማጓቾች ሁሉ በሙግታቸው ጣልቃ የተሟጋች-ቻቸውን አንደበት ስርዓት ለማስያዝ ሲፈልጉ “ዝባን ዮሐንስ ” (በዮሐንስ አምላክ)እያሉ ተቸገሩ። ሆኖም “በዮሐንስ አምላክ” እንዳይሉ ዳኛው ራስ መኮንን ሆኑባቸው፤ በሚኒልክ አምላክ እንዳይሉ ደግሞ አዲስ ነገር ሆኖባቸው ከእጅህ ለማማልጥ ሙሉጭልጭ እያለ እንደሚያስቸግርህ ዓሳ “በዮሐንስ አምላክ” እያሉ ምላሳቸው እያዳለጠባቸው ተቸግረው ነበር። ካፋቸው ሲያመልጣቸው ግን፤ ልክ አንድ ጎረምሳ ጎበዝ ጭቃ አዳልጦት ወድቆ ሲነሳ ሰው አይቶት እንደሆን ‘አካባቢው ግራ እና ቀኝ በሐፍረት እንደሚቃኝ ሁሉ’ ተሟጋቾቹም ወደ አድማጩ ዞር ዞር እያሉ የሰውን ስሜት በሰቀቀን ሲለኩ ነበር።
“ፍርዱ ላይ በችሎቱ አካባቢ የነበረው ተሰብሳቢ ሕዝብም እርስ በርሱ በስሜት እየተጠቃቀሰ ይተያይ ነበር። ሁኔታው ሰውን ሁሉ በጣም አቅል የሚያሳጣ ሆነበት። ያችን ችሎት ተሎ ባለቀች እያለ ያልተመኘ አንድም ሰው አልነበረም።በውስጡ በብዙ ሃሳቦች ተውጦ ይታይ ነበር።” (ታሪኽ ኢትዮጵያ ገጽ ፻፴፪-፻፴፫/132-133 ደብተራ ፍስሐ ዓብየዝጊ ናፖሊ/ኢታሊያ-አቆጣጠር 1899/ፈረንጆች ዘመን አቆጣጠር (ትርጉም የኔ፤- ጌታቸው ረዳ)።”
ደራሲው ይቀጥሉ እና “አጼ ሚኒልክ ራስ መኮነንን ሲቀበሉ” በሚል ርዕስ ሲተነትኑ (ራስ መኮንን ከናፖሊ ጣሊያን አገር ዲፕሎማሲ ስራ ሰርተው በምፅዋ በኩል ወደ መቀሌ ሲመለሱ የተደረገላቸው አቀባበል ማለታቸው ነው):-
“አጉላዕ በተባለች ትንሽ መንደር ለአዳር ሰፈራ አድርገን ትንሽ ቆይታ ካደረግን በኋላ በወቅቱ መቀሌ ከተማ ይገኙ ከነበሩት ከአፄ ጋር (ምኒሊክ ጋር) ለመገናኘት ጫን ተባልን።በወቅቱ ራስ መኮንን ከሐረርጌ ወደ ዜላ ከዚያ ወደ ናፖሊ ከዚያ ወደ ምፅዋ፤ ያ ሁሉ መንገላታትና አስቸጋሪ ጉዞ እና ባሕር አቋርጦ በሰላም መመለስ የሸዋ መኳንንትም ሆኑ በእነ ራስ ሐጎስ በኩል ከፍተኛ ደስታ ነበር። ይኼ ደግሞ ግልጽ ነው። …
“…ወደ መቀሌ የሚያስገባው ቁልቁሉን መንገድ እንደ ጨረስን የአፄው ብዙ ጭፍራ ቆዩን። ደጃዝማች ስብሐት ግን ለራስ መኮንን የሚከተለው ቃል ተናገሯቸው። “እኔ ቆየት ብየ እደርሳለሁ፤እርስዎ ግን ቅድሚያ ይሂዱ”አሏቸው። ራስ መኮንንም “እሺ ደግ ይኹን” ብለው በሃሰባቸው ተስማሙ። ሰው ግን “አይ ተደርበው እንዳይገቡ” ብለው ነው፤ በማለት ተረጎመው። ቁልቁለቱን ጨርሰን ታች እንደወረድን ወዲያውኑ ከሸዋ ሰራዊት ጋር ዓይን ለዓይን ተያየን። “ጸንዓ ደግለ” እያለሁ ድሮ የማውቀው የአጋሜ የአጉዕዳይ ተወላጅ የሆነው ፊታውራሪ ተስፋይ የተባለ ጎን ለጎን እንጓዝ ነበር እና “ወይኔ! ይበለን! ራሳችን ያመጣነው ጣጣ ነው፤ አስታጣቂዎች የነበርነው አሁን ታጣቂዎች ሆን!” አለ።
“ከዚያ በኋላ ይህ ያዳመጡ ራስ መኮንን ለመሸኘት የተከተሉ እነ ‘ኮንቲ አንቶኖሊ’ እና ራስን አጅበው እየተጓዙ የነበሩት ትግሬዎች በሞላ ማለትም-ዓጋሜውም፤አከለ-ጉዛዩም፤ሐማሴኑ፤የአሕሳአውም፤ ተምቤንየውም ሁሉ ከሸዋዎቹ ጭፍራዎች ጋር ዓይን ላይን ተገጣጥሞ ሲተያይ ‘ኪፍ’ አለው። (ደራሲው የተጠቀሙበት ቃል “ኪፍ” የሚል ነው። “ኪፍ” ማለት ድመት ወይንም ነብር ጠላት ስታይ ‘ካንገቷ በላይ ያለው ጸጉር’ በማቆም ‘በጉብታ ስሜት’ የጥላቻ እና የመከላከል ገጽታዋ እንደሚለዋወጥ የሚታይ ስሜት ማለት ነው) ስሜቱ ሁሉ ተለዋወጠ።
“…ያኔ “የሸዌዎቹ ገጽታ ተመልክተህ” ወደ “የትግሬው ሰው ገጽታ ፊትህን ዞር” ብለህ ስትመለከት የምትታዘበው የሁለቱ ሰዎች ገጽታ ልዩነት ልክ “የቀን ብርሃን እና የሌሊት ጨለማ የገጽታ ልዩነት” ይታይ ነበር። የደጃች ሐጎስ አሽከር የነበረ አንድ የተምቤን ሰው ይህ ትርኢት ሲመለከት የአፄ ዮሐንስ ሕልፈት ትዝ ብሎት “እንባው” ዘረፍ አደረገ። እውነት ለመናገር እንኳን “የትግራይ የወንዝ ልጅ የሆነ” የአከለ ጉዛይ እና የሐማሴን ሰው ሁሉ እንባ ተናነቀው። … (ታሪኽ ኢትዮጵያ ገጽ ፻፴፬ 134) 1891/ኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር 1899/ፈረንጅ ዘመን ደብተራ ፍስሐ ዓብየዝጊ ናፖሊ/ኢታሊያ) (ትርጉም የራሴ፤ ጌታቸው ረዳ )።
“…የትግራይ ሕዝብ ወቅቱ ንፍሮ ቆሎ የሚመገብበት እና በተቅማጥ ወረርሺን በሽታ ሲሰቃይ የነበረበት አስከፊ ወቅት ነበር። በወረራው ወቅትም ብዙ ሰው አልቋል። ወደ ትግራይ መሻገራቸውም ከሸዋ ሰራዊቶች መሃል ያልተደሰቱ ነበሩ።….ትግራይ ለምና እንዳመጣቻቸው ትግራይን መራገም ጀመሩ። “የአማራ ወታደር” ወደ አጋሜ ከዚያም ወደ አክሱም ሕዝብ እያጠፉ ለመሸጋገር አልመው ነበርና ፤ የአማራ ወታደር ወደ አጋሜ መሻገር አቀበት ሆነበት። ትግራይን መራገም ጀመሩ። ቋንቋውን ሁሉ መስማት አስጠላቸው።
“ይህ እንደዚህ እያለ የራስ መንገሻ በሰላም እጃቸውን መስጠት ‘ደስታ’ ሆነ። በወቅቱ ራስ መንገሻ ዮሐንስ እጃቸው ለአፄ ሚኒልክ ሲሰጡ ራስ አሉላ እጄን ለሸዋ አልሰጥም ሲሏቸው ራስ መንገሻ ዮሐንስ ግን “ሰውና አገር ጠፍቶ እኔ ብቻየን ብቀር ምን ይረባኛል፡ እናንተ ግን የመሰላችሁን ቀጥሉበት፤እኔ ግን ገቢ ነኝ ብለው እጃቸውን ሰጡ።”
ካሉ በኋላ ደራሲው በ፰መጋቢት፲፰፹፪ (መጋቢት 8/1882) ራስ መንገሻ ወደ ሚኒልክ ሲገቡ መቀሌ ከተማ የተደረገው ስነ ስርዓት በስፋት ከዘረዘሩ በኋላ፤ ያ አስገራሚ ትርኢት ባጭሩ እንዲህ ሲሉ ያሰቀምጡታል፦
“በ፰መጋቢት፲፰፹፪ (መጋቢት 8/1882) ራስ መንገሻ ወደ ምኒልክ ሊገቡ በመዘጋጀት እንዳሉ ከተነገረ በኋላ አጼው ወዲያ ወዲህ ሳትል በጥዋቱ ነገ በየአለቃህ ተሰልፈህ እንድትገኝ ብለው አዋጅ አስነገሩ። መቀሌ የሚገኙት አጼ ምኒልክ ይህን ካዘዙ በኋላ ጠዋት ጸሐይ ሰትወጣ ሰልፈኛው ከአፄው ደንኳን ጀምሮ በሁለት ረድፍ እንደ ግድግዳ ግራ እና ቀኝ ረዢም ረድፍ በመስራት ይጀምር እና ወደ ታች ራስ ስዩም ይመጡበታል ወደ ተባለው የተምቤን አቅጣጫ ሲደርስ ወደ አራት እና አምስት ረድፍ ሰልፈኛ ግራ እና ቀኝ በረዢሙ በመሰለፍ ረድፍ ያዘ። በዛው ላይ የራስ መንገሻን መልክ ለማየት እየተጋፋ በብዙ የሚቆጠር ሕዝብ እርስ በርሱ እየተጋፋፋ ነበር።
“ቀጥሎም ትልልቆቹ ደጃዝማቾች እና ሹሟሙንቶች ወደ ንጉሱ ጃንጥላ ተሰበሰቡ። የንጉሡ ጃንጥላም ተዘረጋ። ከንጉሡ ዱንኳን ጀምሮ በሁለት ረድፍ ግራ እና ቀኝ እንደ ገመድ የተወጠረው የሰልፈኛው ጫፍ የት እንደ ሆነ ለዓይን እስኪያዳግት ድረስ ቀጥ ብሎ በረዢሙ እና በተንጣለለው ሰፈው ሜዳ ወደ ታች የዘለቀው ሰልፈኛ ስትመለከት በግራ እና በቀኝ በተሰለፈው እመሃል ላይ ለራስ መንገሻ ዮሐንስ መምጪያ ክፍት ቦታ ሰርቶ የተንጣለለ የማሳለፊያ ክፍት መንገድ ሰርቷል።
“የአማራዎቹ ሠራዊት ብዛት ያኔ ነው ለማየት የተቻለው። ብዛታቸው የመሬት አፈር ያህል ነበር። ከዚያ በኋላ ረፋዱ ላይ ራስ መጡ። ቢያንስ ፼ (10,000) የሚሆን ሠራዊት አስከትለው መጡ።
“እሳቸውን ለመቀበል ግራ እና ቀኝ በተሰለፈው ሰራዊት መሃል ለማሃል ሰንጥቀው በመጓዝ ወደ ንጉሡ ድንኳን ደረሱ። አፄ ምኒልክ ድንቅ ሰው ናቸው እና በብዙ አክብሮት ተቀበሏቸው፡መድፍ ተተኰሰ፡ ወዲያውኑ እያንዳንዱ እሳቸውን ለመቀበል የተሰለፈው ሠራዊት በነፍስ ወከፍ የደስታ መግለጫው ጥይት ወደ ሰማይ ተኰሰ። ሰማይ እና ምድር ድብልቅልቁ የወጣ መሰለ። እንዳይጠፉ ታስረው ከነበሩበት በረት ፈረሶች እና በቅሎዎች ማሰሪያቸውን እየነቀሉ እየበረገጉ እንጣጥ እያሉ ሸሹ።
“በወቅቱ ራስ መንገሻ በአባታቸው (አፄ ዮሐንስ) ሞት ምክንያት ሐዘንተኛ ስለነበሩ በሰልፈኛው መሃል ሰንጥቀው ሲያልፉ የሐዘን ልብስ ለብሰው ነበር የመጡት። ይህንን ሲመለከት ሰው እንዳለ በሙሉ ምርር ብሎ ሐዘን በሐዘን ሆነ።……”
“… በወቅቱ ራስ መንገሻ እጃቸው ባይሰጡ ኖሮ ካሁን በፊት ከታየው ውጊያ በከፋ መልኩ ትግራይን ያጠፏት ነበር። ራስ መንገሻ ከመግበታቸው በፊት አፄ ምኒልክ አጋሜ አውራጃን ለማጥፋት ዝግጅት አድርገው ነበር። የአጋሜ አውራጃም “ከአማራ ጋር ተናንቀን አብረን እንሞታለን እንጂ አይገዛንም” ብለው ዝግጅት አድርገው በየምሽጉ እና ጉራንጉሩ መዋጊያ ቦታ ይዘው ተዘጋጅተው ነበር።
“ከደጃች ሥዩም በቀር ከሸዋ ጋር የወገኑት እና ያልወገኑት መኳንንት መሃል መጠኑ ያለፈ ጥላቻ በትግሬዎች አርስ በርስ ይንጸባረቅ ነበር። ይህ ጥላቻ የርስ በርስ ጥፋት ማስከተሉን አይቀሬ እና ትርፍ እንደሌለው ከተገነዘቡ በኋላ ሕዝቡ ካለቀ በኋላ ብቻየን ብቀር ምን ትርጉም አለው በማለት፤ እነ ራስ አሉላን የፈቀዳችሁ አድርጉ ብለው እነሱን ትተው ራስ መንገሻ ዮሐንስ እጃቸውን ለመስጠት ነበር የተገደዱት። (ታሪኽ ኢትዮጵያ ገጽ ፻፵፪-/፻፵፬ 142-144) 1899/ፈረንጅ ዘመን አቆጣጠር ደብተራ ፍስሐ ዓብየዝጊ ናፖሊ/ኢታሊያ) (ትርጉም ጌታቸው ረዳ ለወደፊቱ ከሚታተመው መጽሐፍ የተቀነጨበ)።
መደምደሚያ፤
– ደብተራ ፍስሐ የምኒልክን ወታደሮች ለመግለጽ የተጠቀሙት ቃል “የአማራ ወታደር” እያሉ ነው። በዚህ ላሳርግላችሁ፡-ከወያኔዎች ጋር ያልሰመርነው “ሸዋውያን ተጋሩ” እያሉ እኛን ለመሰየም የበቁት እና ሸዋ/እና ትግሬ የሚለው የጥላቻ መነሻ ወያኔዎች ከየት እንደለቀሙት ታሪኩን እንደሚከተለው ከደብተራ ፍስሓ አብየዝጊ ባጭሩ ተመልክቱ።
“…… (ምኒልክ) ዓይባ የተባለ ቦታ ከመስፈራቸው በፊት እዚያው ዙርያዋ ሜዳ በከበባት አንድ አምባ በውስጧ የተጠናከሩ ምሽጎች ላይ 7 ትግሬዎች ሆነው የሸዋዎቹን ጦር እና መድፈኛ ገትረው አቆሟቸው። መድፍ ሁሉ ተተኩሶ ፍንክች ማለት አቃታቸው። የአፄው ጋላዎች (በመስለብ) ሱሰኞች ነበሩ እና ሰውን እየሰለቡ መፈከር ጀመሩ። ንጉሡም መሳሪያ ሳይማርክ “ገዳይ“ ብሎ የፎከረ ሰው ወዮለት! በማለት አዋጅ አወጁ። ቢሆንም ስለ ሕልፈተ ትግራይ ልብ ላለው ብዙ አሳዝኗል። እነኚያ የቤገምድር አማራዎች ግን በጣም ይቆጩ እና ያዝኑ ነበር።
(ጐንደሬው አማራ ለትገሬው አዛን ፤የሸዋ አማራ ግን ለትግሬው ጨካኝ እየተባለ የሚነገረው የተሳሳተ ይህ አባባል ዛሬም በእነ አቶ አብርሃም ያየህ በተደጋጋሚ ሲጠቀሙበት ተደምጠዋል። አምና ዴሰምበር 2013 ኤርትራን ከድቶ ለጂቡቲ እጁን የሰጠ ‘ሃብቶም ካሕሳይ’ መቀሌ “የዓይደር ህጻናት” በክላስተር ቦምብ ደብድቦ የፈጃቸው ኤርታራዊ ፓይለት መሆኑን እየተወቀ፤ እነ አብርሃም ያየህ ግን “ደብዳቢው የሸዋ አማራ ነው” “የጎንደር አማራ በትግራይ የወንድሞቹ ልጆች አንዲህ አያደርግም” እያሉ ኤርትራዊያንን ላለመወንጀል ሲሉ ድሮ ከእነ ደብተራ ፍስሃ የተረከቡት ትምህርት ዛሬም ሲደግሙት ሰምተናል)።
/…የተመራማሪውን የመጨረሻ ክፍል ጽሑፍ በቀጣይ አቀርበዋለሁ።/
Filed in: Amharic