>
5:13 pm - Monday April 20, 3114

ፕሮፌሰር ሕዝቅኤል እንኳን የጥንቱ ቤተ አማራ (የዛሬው ወሎ) እርስዎ የተወለዱበት ወለጋም የኦሮሞ አይደለም! (አቻምየለህ ታምሩ)

ፕሮፌሰር ሕዝቅኤል እንኳን የጥንቱ ቤተ አማራ (የዛሬው ወሎ) እርስዎ የተወለዱበት ወለጋም የኦሮሞ አይደለም!

 

አቻምየለህ ታምሩ

 

ፕሮፌሰር ሕዝቅኤል ጊቢሳ ከሰሞኑ በአዲስ አበባ የሚሊንዬም አዳራሽ ወሎን በሚመለከት ባደረጉት ዲስኩር የተለመደውን የኦነግን የፈጠራ ትርክት በማስተጋባት ወሎን የኦሮሞ ምድር አድርገው አቅርበዋል፤ አባ ገዳ ሆነው ወደ ወሎ የሚደረገውን ዘመቻ ለመምራት እንደተዘጋጁ በሚመስል መልኩም  የጦርነት ነጋሪት ጎስመዋል። ሰውዬው ገራሚ ሰው ናቸው!

እውነቱ ግን በታሪክ እንኳን የጥንቱ ቤተ አማራ የዛሬው የወሎ ምድር ይቅርና እሳቸው የተወለዱበት ወለጋም ከኦሮሞ መስፋፋበት በፊት የኦሮሞ አልነበረም። ወለጋ የጥንት ስሙ ቢዛሞ ሲሆን ኦሮሞ ነባር ብሔረሰቦችን አጥፎቶ እንደ ዋርካ የተስፋፋበት ምድር ነው። ይህንን እውነት የሚነግረን ደግሞ  ኦነጋውያን ደብታራ የሚሉት የታሪክ ጸሐፊ ሳይሆን ራሳቸው ፕሮፌሰር ሕዝቅኤል ጊቢሳ ናቸው።

ፕሮፌሰር ሕዝቅኤል ጊቢሳ በ1977 ዓ.ም. ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በታሪክ ትምህርት የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ሲያጠናቅቁ ያቀረቡት የጥናት ወረቀት ርዕስ “From Animosity to Mutual Understanding: Oromo Relations with the Gumuz of the Didessa Valley” ይሰኛል።

ፕሮፌሰር ሕዝቅኤል በዚህ የዲግሪ ማሟያ ጥናታቸው ውስጥ ኦሮሞ ወደ ወለጋ ከመምጣቱ በፊት ማኦ፣ ሳኢና ገበጣ የሚባሉ የኢትዮጵያ ነገዶች በጥንቱ ቢዛሞ በዛሬው ወለጋ ምድር ተስፋፍተው ይኖሩበት እንደነበር፤ ኦሮሞ ወለጋን ሲወር ግን እነዚህን ነባር የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች አጥፎቶና ወደ ዴዴሳ ሸለቆ ገፍቶ  በማባረር  በቢዛሞ ምድር እንደ ዋርካ እንደተስፋፋ ከኦሮሞ አፈ ታሪክ ጭምር  አገኘሁት ያሉትን  ማስረጃ በማከል  ከኦሮሞ ወረራ በፊት የነበሩትን የወለጋ ነባር  ነገዶች ታሪክ በጥናታቸው አቅርበዋል።

እንግዲህ! ፕሮፌሰር ሕዝኤል ራሳቸው ለዲግሪ ማሟያ ባጠኑት ጥናት መሰረት የዛሬው ወለጋ ኦሮሞ አካባቢውን  ሊወር  ከመምጣቱ በፊት ማኦ፣ ሳኢና ገበጣ የተባሉ በመላ ወለጋ ተሰራጭተው ይኖሩ የነበሩበት  ምድር  እንደነበርና  ኦሮሞ እንደ ዋርካ በወለጋ የተንሰራፋው  የወለጋን ነባር  ብሄረሰቦች አጥፍቶና መሬታቸውን በወረራ ወስዶ መሆኑን የነገሩንን የራሳቸውን  ጥናት ባፍጢሙ ደፍተው ነው እንግዲህ ዛሬ  ደግሞ ሌላ ትርክት የሚነግሩን።

ባለፈው ጊዜ ለዶክተር ነጋሶ በሰጠሁት መልስ ውስጥ በሳቸው ጥናት መሰረት ኦሮሞ ወለጋን በመውረር ከዋጣቸው ነገዶች መካከል አንዱ የሆነው አማራ ሲሆን ይህ የአማራ ክፍል የሆነው ነገድ በኦሮሞ ከተዋጠ በኋላ ስሙ ቅጥያ ወጥቶለው መጠሪያው አማራ ካንቺ እንደሆነና ይህ አማራ ካንቺ የተባለው የጥንት የወለጋ አማራ ዛሬ ኦሮሞ ሆኖ ዛሬም በወለጋ እንደሚኖር ያወሳሁትን ልብ ይሏል።

ሌላው ገራሚው ነገር ወሎን የኦሮሞ ነው የሚሉን  ፕሮፌሰር ሕዝኤል ጊቢሳ ሕገ መንግሥት የተባለውን የወያኔ ፕሮግራም ካላከበራችሁ በሕልውናችን እንደመጣችሁ እንቆጥረዋለን ከሚሉ የኦሮሞ ብሔርተኞች  መካከል ቀዳሚው ሰው እሳቸው ራሳቸው መሆናቸው ነው። እነ ፕሮፌሰር ሕዝቅኤል ገቢሳ ካላከበራችሁ በሕልውናችን እንደመጣችሁ እንቆጥረዋለን የሚሉን ሕገ መንግሥት  ወሎን  የአማራ ምድር [ክልል] እንደሆነ ይደነግጋል።

ጤና ይስጥልኝ ፕሮፌሰር ሕዝኤል ጊቢሳ! ካልተከበረና ካላስከበርነው ሞተን እንገኛለን የምትሉት ሕገ መንግሥት የአማራ ያደረገውን ወሎን «የኦሮሞ ነው» ስትሎ ካልተከበረና ካላስከበርነው ሞተን እንገኛለን የምትሉትን ሕገ መንግሥት መጣስ አይደለምን? ነው ሕገ መንግሥት ተብዮውን እንድናከበር የተፈረደብን እኛ ብቻ ነው? ሕገ መንግሥት ይከበር የሚለው እናንተን አይመለከትም ማለት ነውን? እናንተ ራሳችሁ ካልተከበረና ካላስከበርነው የምትሉትን ሕገ መንግሥት አናት በየአደባባዩ እያፈረሳችሁ ሌላውን በአፍራሽነት የመክሰስ የሞራል ልዕልና እንዴት ሊኖራችሁ ይችላል?!

ሕገ መንግሥት የተባለውን የወያኔ ፕሮግራም ካላከበራችሁ በሕልውናችን እንደመጣችሁ እንቆጥረዋለን የሚሉን ፕሮፌሰር ሕዝኤል ጊቢሳ ካላከበራችሁት የሚሉንን ሕገ መንግሥትና የራሳቸውን ጥናት ባፍጢሙ ደፍተው ወሎን የኦሮሞ ለማድረግ ለዘመቻ እንደተዘጋጁት ሁሉ ለዲግሪ ማሟያነት የጻፉትን ወረቀታቸውንም ዋቢ በማድረግ ወለጋ ከኦሮሞ መስፋፋት በፊት ለነበሩትና ኦሮሞ በግፍ መሬታቸውን በወረራ ለቀማቸው ለማኦ፣ ሳኢ፣ ገበጣ፣ ወዘተ ነገዶች  ይመለስ ዘንድ በመከራከር የመርህ ሰው መሆናቸውን ማስመስከር አለባቸው።

Filed in: Amharic