>

አ.ዴ.ፓም ሆነ ት.ህ.ነ.ግ ህዝብ በማይደርስበት ስፍራ መቀመጥ ያለባቸው አደገኛ ገዳይ መርዞች ናቸው!!!  (ዘመድኩን በቀለ)

አ.ዴ.ፓም ሆነ ት.ህ.ነ.ግ ህዝብ በማይደርስበት ስፍራ መቀመጥ ያለባቸው አደገኛ ገዳይ መርዞች ናቸው!!!
ዘመድኩን በቀለ
ከብአዴን የሰማሁት አዲስ ነገር ቢኖር ህወሓትን በትግርኛም በአማርኛም ከነትርጉሟ መጥራቱ ብቻ ነው። የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጪ ግንባር [ ትህነግ ] ብሎ መጥራቱ
በትግል ወቅት እርስ በራሳቸው ተራ በተራ ካራ መዘው በመተራረድ ተበላልተው የረሃብ ቀን ያመለጡ አረመኔዎች ዛሬ ደርሰው ድንገት ተሰዳደቡ ብሎ ጮቤ መርገጡም የጤና አይመስለኝም። 
 
★ ስድድቡ ወደ ጦርነት ቢሸጋገር ኦህዴድኦነግ እሰይ ስለቴ ሰመረ ብሎ መዝሙሩን እንደሚያቀልጠው መጠርጠርም ያስፈልጋል
~ አዳሜ በአዲስ ድርሰት እንዳትሸወድ ተጠንቀቅ። እነሱ እንደሁ መርዞች ናቸው። ሁለቱም ህዝብ በማይደርስበት ስፍራ መቀመጥ ያለባቸው አደገኛ ገዳይ መርዞች ናቸው።
•••
ሩቅ በማይባል ጊዜ ውስጥ “ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ዕረፍትና መዳን የግድ መምጣቱ አይቀርም። ለዐማራም፣ ለትግሬም፣ ለኦሮሞም ለኢትዮጵያውያንም ሁሉ ከሌላ ስፍራ መዳን እንዲሆንላቸው፣ እንዲመጣላቸውም በቅዱሳኑ ዘንድ የታወቀ የተረዳም ነገር ነው። ይሄ ካንሰር፣ ጋንግሪን የሆነ ኢህአዴግ የተባለው ክፉ ሳጥናኤል የሉሲፈር ልጅ፣ አጋሮቹ ተብለው የሚጠሩትና  ጠፍጥፎ የፈጠራቸው ኮተት ድርጅቶች ግን ዐይናችን እያየ፣ ጆሮአችንም እየሰማ ድራሽ አባታችውን ያጥፋልን። አሜን። ኢህአዴግ በጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ሳይቀበር ኢትዮጵያ ትድናለች ማለት ዘበት ነው።
•••
ወደጄ የኢትዮጵያ የህመሟ ምንጭ የሆኑት። ትክትኮቿ፣ ቀኬና ሷሎቿ፣ እከክ የሆኗት፣ እንደ አልቅት፣ እንደመዥገርና ትኋን በላይዋ ላይ ተጣብቀው ደሟን የሚመዘምዙት እነ ሻአቢያ፣ ህወሓት፣ ብአዴንና ኦህዴድም፣ ደኢህዴንና ኦነግ የመሳሰሉት በህይወት እያሉ ኢትዮጵያ እንደሆነ አትፈወስም።
•••
ለእኔ የህወሓትና የማደጎ ልጇ የብአዴን የትናንቱ እንካ ሰላንቲያና ስድድብ ታክቲካልም ቴክኒካልም ነው ብዬ ነው የማምነው። የህወሓት ነውር፣ የብአዴን ድፍረት የሆነ ወከክ የሚያደርግ ነገር ቢኖረውም ነገር ግን ውሸታቸውን ነው። ከምር ውሸታቸውን ነው። በዚህ አጋጣሚ ህወሓት ትግሬን፣ ብአዴንም ዐማራን ለማጀዘብ የፈጠሩት አዲስ ድራማ ነው ብዬ ነው የማምነው። ተመካክረው ሁሉ ሊሆን ይችላል እነሱ እንዲህ የሚሰዳደቡት።
•••
ሁለቱም ሌቦች ናቸው። ሁለቱም ውሸታሞች ናቸው። ሁለቱም ፀረ ህዝብ ናቸው። ሁለቱም ፀረ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ናቸው። ሁለቱም ፀረ ዐማራ ናቸው። ሁለቱም ነፍሰ ገዳዮችና አፈናቃዮች፣ ጨካኝ ወንበዴዎችም ጭምር ናቸው። ሁለቱም ነውር ጌጡዎች ናቸው። እናም እኔ ሁለቱንም አላምናቸውም። ዝንቦች ናቸው። ተፈጥሮአቸው የዝንብ ዓይነት ነው። ከዝንብ ደግሞ ማር መጠበቅ ሙትቻነት ነው።
•••
በዚያ በኢህአዲግ ቤት ባለ አእምሮ የለም። ዐቢይ አህመድ፣ ህዝቅኤል ጋቢሳ፣ ሌንጮ ለታ፣ የቀን ጅብ እያሉ ሲሰድቡት የከረሙትን ትግሬ፣ ከመሃል ሀገር ወደ መቀሌ ሸኘነው ያሉትን ትግሬ እኮ ዐማራው የጠነከረ ሲመስላቸው ሁሉን ረስተው ጋብቻ ሊፈጽሙ መቀሌ የከተሙ ጉዶች ናቸው። የጃዋር ቃጥራ ህዝቅኤል አቦይ ስብሃት እግር ስር ተደፍቶ ዳይፐር ሲቀይርላቸው አምሽቶ ነው የተመለሰው። ስኳሬ ዓባይ ፀሐዬን አግኝቶ፣ ከጌታቸው አሠፋ ትእዛዝ ተቀብሎ ነው የሚመጣው። ዐቢይና ደብረ ጽዮን ከአክሱሙ ስምምነት በኋላ 4 ዐማራ 2 ትግሬ ቀርጥፈው መብላታቸው ወይም ማስበላታቸው ይታወቃል። የጃዋር አሽከር የሕዝቅኤክ የመቀሌው ጉዞ ደግሞ የሚያመጣውን አብረን እናያለን።
•••
አጅሪት ህወሓት ጌታቸው አሰፋን የመሰለ ገዳይ በጉያዋ አቅፋ ይዛ፣ እነ ስኳሬ ዓባይን በጉያዋ አቅፋ ይዛ ስለ ዲሞክራሲ፣ ስለፍትህ ስትጮህ ውላ ብታድር ማን ይሰማታል። አዛኝ ቅቤ አንጓቿ ህወሓት ስትገለው፣ ስትዘርፈው የኖረችውን ዐማራ አሁን ደርሳ ድንገት “ዐማራ እኮ ትልቅ ህዝብ ነህ” ብትለው ማን ይሰማታል። እኔ በበኩሌ አልሰማትም። ሌባ ደግሞ ዲሞክራሲ የትአባቱ ያውቃል።
•••
ብአዴን ንጉሡ ጥላሁንን የመሰለ የጃዋር ጓደኛ በጉያው አቅፎ፣ ላቀ አያሌውን፣ አሰማኸኝ አስረስን የመሰለ ከሃዲ፣ ዋሾ፣ ቀጣፊ፣ አድርባይ ይሁዳ በጉያው አቅፎ። እነ ኮሎኔል አለበልን ቀፍድዶ አስሮ፣ እነ ዘመነ ካሴንና እነ ማስረሻ ሰጤን በየዱሩ እያሳደደ እያየሁት፣ ህወሓትን ሙልጭ አድርጎ ሰደበ ብዬማ ጮቤ አልረግጥም። ከምር በስድብማ አልሸወድምም። ለስድብ ለስድብማ ዮኒ ማኛና ጂጂ ኪያ አሉልኝ አይደለ እንዴ። እስከ ዶቃ ማሰሪያ የሚያስታጥቁ።
•••
ይሄ የትናንቱ የሁለቱ ስድብ ልክ እንደ ቲም ለማ ኦሮማራ ዓይነት ፈጠራ ነው። መንጋውን ማስተንፈሻ ፈጠራ ነው። ልክ እንደ ኦቦ ለማ ኢትዮጵያዊ ሱሴ፣ ልክ እንደ አቢይ አህመድ ስንሞት ኢትዮጵያዊ እያለ ሚልዮኖችን ወደ መቃብር እንደሚሸኝበት መፈክር ያለ ነው። የቀን ጅቦች እያለ ትግሬን ሙሉውን ሰድቦ ለሰዳቢ እንደሰጠበት ያለ ጊዜያዊ የመተንፈሻ ታክቲክ ነው። እናም ሁለቱም ውሸታቸውን ነው። ቀዳዶች፣ ቡትርፎች በሉልኝ።
•••
ኦሮሞ ስለሆኑ ብቻ እነ ጃዋርን የመሰሉ ሀገር አማሾችን በመከላከያ ጦር አስጠብቆ፣ እነ ክርስቲያን ታደለን በዐማራነታቸው ብቻ ወደ ወህኒ ሲጋዙ እያየ፣ በየክልሉ ዐማራዎች በገፍ እየታደኑ እየተለቀሙ ወደ ዘብጥያ ሲወረወሩ እየተመለከተ ዝም ጭጭ ጮጋ ያለ ፓርቲ ድንገት ደርሶ ህዝቤ ዝንተ ዓለሙን ሲወቅስበት የነበረውንና የሚያውቀውን የድሮ ስድብ እንደ አዲስ አሁን ሰብስቦ በመዘርገፍ ህወሓትን ሰደበ ብዬማ ንቅንቅ አልላትም። አላጨበጭብምም።
•••
ቆይ ግን ብአዴን ህወሐትን ተሳደበ ብለው እነ ኢዜማ ለምን ጨፈሩ? እነ ልጥ ለምን ቦረቁ? ኦነግና ኦነግ ሸኔ ለሃጫቸውን ለምን አዝረከረኩ ብለህ ጠይቅ ወዳጄ። ጠይቅ ነው የምልህ ጠይቅ ዝም ብለህ አትበጥረቅ። ህወሓትና ብአዴን ሲሰዳደቡ እነ ጃዋር ምን እየሠሩ ነው ብለህ መርምር። ለማ መገርሳ የዐማራን የመሳሪያ ግምጃቤት በርብሮ ለምን ዘረፈ ብለህ ጠይቅ። ኦነግ ተወካዮቿን ለምን መቀሌ ላከች ብለህ ጠይቅ። ጠይቅ፣ መርምር። ዝም ብለህ አትነዳ።
•••
ኢህአዴግ የሚባል የአውሬው መንፈስ ከኢትዮጵያ ምድር እስካልከሰመ፣ እስካልተወገደ ድረስ በሁለቱ ፓርቲዎች ስድድብ ኢትዮጵያ አትፈወስም። አከተመ። ሁለቱ ፓርቲዎችም ሆኑ እነዚያ የሙሁራን ደናቁርት የተሰባሰቡባቸው የ60 ዎቹ መጦሪያ የሆኑት ገሌ ፓርቲዎች በሙሉ ራቅ ተደርገው መቀበር አለባቸው። እነሱ ካልተቀበሩ በስተቀር ኢትዮጵያ አትድንም። ኢትዮጵያ አትፈወስም።
•••
አሁን ትርምስ ቢኖር እንኳ ብአዴንና ኦህዴድ በባህርዳር፣ ኦህዴድና ህወሓት በአዲስ አበባ ያፈሰሱት የ6 ቱ ንፁሐን ዜጎች ንፁህ ደም ነው እንዲህ የሚያበጣብጣቸው። አሁንም የእናት የአባቴ አምላክ ቸሩ መድኃኔዓለም ያበጣብጣቸው። እረፍት ያሳጣችሁ። ሰላም እጡ፣ እንቅልፍ ያሳጣችሁ። ፌክና ፎርጅድ ፀባችሁን ኦሪጅናል ፀብ የድርግላችሁ። አሜን።
•••
ይልቁኑ እናንት ትግሬዎችና ዐማሮች ግን ልብ ግዙ። በታቦተ ጽዮን ይሁንባችሁ ልብ ግዙ። ኦሮሞዎችም ተረጋጉ። አቢይ በለው ለማ፣ ደመቀ በለው ገዱ፣ ደብረ ጽዮን በለው ጌታቸው ኢህአዴጎች ናቸው። አንድ ናቸው። ትናንትም ረግጠው የገዙህ እነሱ ናቸው። ዛሬም ያሉት እነሱ ናቸው። እነሱ ነገ አፈር ይሆናሉ። የምትኖሩት ግን እናንተና ኢትዮጵያ ናችሁ።  የእነዚህን አጋንንታምና በስማችሁ የሚነግዱ ሸቃላ ሁለት ፓርቲዎችን እንካሰላንቲያ ሰምታችሁ እርስ በእርስ እንዳትጣሉና ተስሎ አንገታችሁ ላይ ለማረፍ ሩብ ጉዳይ ፊሽካ ለሚጠብቀው ለእነ ጃዋር ሜንጫ እንዳትመቻቹ ተጠንቀቁ። ተጠንቀቁ ተናግሬአለሁ።
•••
ወዳጄ እናንተ ብትጣሉ የምትጎዳው ኢትዮጵያ ናት። ተዋሕዶ ናት። ሀገር ወዳዱ ኢትዮጵያዊው ጥንታዊ ሙስሊም ነው የሚጎዳው። የትግሬም ሆነ ዐማራ፣ የኦሮሞም ሆነ የደቡብ ክርስቲያን ሙስሊሙ ይጎዳል። በአንጻሩ ለእነ ሜንጫ ሠርግና ምላሽ ይሆንላቸዋል። ለእነ ወሃቢያም ጮቤና ዳንኪራ ያስጨፍራቸዋል። እናም አትስሟቸው። ራሳቸውን በራሳቸው በልተው እስኪጨርሱና ከላያችሁ ላይ እስኪወገዱ በትእግስት ጠብቋቸው።
•••
እናም ወዳጄ መግለጫው ደስስ ይላል ብለህ ማንገጭላህ ሳይወልቅ በፊት በጊዜ ንቃ። “በዐማራ የመከራ ወቅት ማንም እየተነሳ ዐማራውን የከረመ ሂሳቡን እንዲያወራርድበት አንፈቅድም” የሚለውን የብአዴንን መግለጫ እየሰማህ ጮቤ አትርገጥ። ብአዴን እንዲህ ማለት ልማዱ ነው። አዲስም አይደል። ወልቃይትን የሸጠ፣ ራያን የሸጠ እኮ ነው ብአዴን። እሱን ነው ልደግፍህ የምትለው። የምታጨበጭብለት።  ብአዴን እየሰጠ ያለው መግለጫ ቀለሙ ሳይደርቅ በዚህ ሰዓት እኮ ዐማራው ቤቱን እየተወ ከመተከል እየወጣ ነው። እየተሰደደ ነው። ንብረቱን በኦቦ ለማ መከላከያ ሠራዊት ሳይቀር እየተዘረፈ እየተገደለም ጭምር ነው። የፖለቲካ አመራሮች ሳይቀር በቀን በብርሃኑ ሲዘርፉ እየታያዙ መሆኑን ዜና እየሰማን ነው። የመተከል ማንዱራ አማራ ሙሉ በሙሉ ተፈናቅሎ ቻግኒ ገብቶልሃል እኮ። ግልገል በለስ ማንቡክ እና ጉባ ያለ ዐማራም የወገን ያለህ ድረሱልኝ እያለ እየጮኸ መሆኑ እየተነገረ እኮ ነው። በመላ ሀገሪቱ ዐማራ እንደ ማርያም ጠላት ተቆጥሮ በኦሮሞው የዐቢይ መንግሥት እየታደነ ነው። እየታሠረ እየተገደለም ነው። እናም ይሄን ሁሉ አጀንዳ ውጦ ከህወሓት ጋር ስለተሰዳደበ የአንተ አብረህ ማጫፈር ነው ያልገባኝ። ብአዴንን አባላቱ ያድኑት። አንተ ራስህን አድን። እሱን ሥራው ያውጣው። አንተ ሥራህን ሥራ።
•••
አሁን በዚህ ጊዜ ህወሓት በሃዘኔ ሰዓት ሰደበችኝ ብሎ ወገብ ታጥቆ አፍን አሞጥሙጦ ለስድብ መንጠራራት የዐማራን ዘርፈ ብዙ ችግር አይቀርፈውም። ደግሞስ በፓርቲ ደረጃ መሰዳደብ ምን ይሉት ሙያ ነው? በየዕለቱ የሚገድልህን፣ እንደ ከብት ወደ መታረጃ ቄራ እየነዳ ወደ ማጎሪያ ካምፕ የሚነዳህን፣ ከቀዬህ፣ ከመንደርህ አፈናቅሎ የሚያስርብህን፣ አጅሬ ኦህዴድኦነግን በአናትህ ላይ ፊጥ አድርገህ አስቀምጠህ የምን ከሙትቻዋና መቃብሯ ተምሶ፣ ልጧ ተርሶ ሞቷን ከምትጠባበቀዋ የጃጀችዋ ኮማሪት ከህወሓት ጋር ለመሰዳደብ ምላስን ማሾል፣ ከንፈርን ማሞጥሞጥም ነው። በሉ ንኩት ምደረ ሙጢ ሁላ።
•••
ይልቅ አሁንም ዐማራ ሆይ ተደራጅ። ተሰባሰብ፣ ተመካከር፣ በጎጥ በሰፈር፣ በመንደር መከፋፈልህን አቁም። ኢትዮጵያን ይዘህ በዐማራነትህ ጥላ ስር ተደራጅ። የእነ አሳምነው ጽጌን፣ የእነ ዶር አምባቸውን፣ የእነ ምግባሩን፣ የእነ እዘዝን ዓርማ አንሳ። ወጥረህ ተደራጅ። ተደራጅና ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን ከዚህ አዘቅታም፣ ቅሌታም፣ ነውር ጌጡ ከሆነው ከእነ ዐቢይ አውሬው ኢህአዴግ ተገላገል። እኛንም ገላግለን። ለእነ ተረኞና የኬኛ ፖለቲከኞች ብቸኛው የኃይል ማስጠበቂያ ሚዛኑ “ የዐማራው መደራጀት ብቻ ነው። ”
•••
በአሁኑ ሰዓት ብአዴን ይፍረስ ባይም እንዳይደለሁም። እንዳልሆንኩም ይታወቅልኝ። ነገር ግን ይሄ ሲቀርቡት የሚሸሽ፣ ሲያምኑት የሚከዳ፣ የተስፋ ጨላንጭል የሚደፍን። የጎባጣ አሽከር፣ የተረኛ ፈረስ ሆኖ የተፈጠረን ፓርቲ የማምንበት አምኜም የምሰማበት ህሊናና ጆሮም የለኝ። ሥራው ያውጣው። እሱን ትታችሁ እናንተ የራሳችሁን ሥራ ሥሩ ነው እያልኩ ያለሁት።
ስትፈልግ ፈንዳት እንጂ ለእኔ እውነታው ይሄው ነው። 
•••
ሻሎም !   ሰላም ! 
ሐምሌ 5/2011 ዓም
ከራየን ወንዝ ዳር።
Filed in: Amharic