>

የህወሓት የፖለቲካ ስትራተጂ! (አብርሀ ደስታ)

የህወሓት የፖለቲካ ስትራተጂ!
አብርሀ ደስታ
 * “በትግራይ ላይ ሆን ተብሎ ባነጣጠረ የዘር ጥቃት ህዝቡ የመገንጠል ስሜት ውስጥ ገብቷል”
ደብረፅዮን ገብረሚካኤል 
የህወሀትን የመደራደሪያ አቅም ለማዳበር የተጠነሰሰች ሴራ መሆኗ ነው።
መፍትሔው መደራደር ሳይሆን ህወሓትን ከስልጣን ማባረር ነው። ህወሓት ከስልጣን ከተባረረ ኢትዮጵያ ሰላም ትሆናለች።
እንዴት ሆነ?
ህወሓት በ27 ዐመት የጭቆና አገዛዟ ምክንያት በትግራይ ህዝብ ስም ሌሎች ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንን አሰቃየች። ከዛ በህዝብ ዓመፅ ከስልጣን ተባረረች፤ ወደ ትግራይ አፈገፈገች!
ከትግራይ እንዳትባረር ደግሞ “እኔን እያሯሯጡ ያሉ ሐይሎች የትግራይን ህዝብ ሊያጠፉ ነውና አግዙኝ፤ በመሃላችሁ ልደበቅ፣ እንዳታባሩኝ” አለች። በብሄሬ ምክንያት ነው ከስልጣን የተባረርኩኝ አለች።
“ህወሓትና የትግራይ ህዝብ አንድ ናቸው” በማለት ህወሓትን ለመበቀል የሚፈልጉ ሐይሎች በትግራይ ተወላጆች ላይ እንዲያነጣጥሩ አደረገች። ተጋሩ ዒላማ እንዲሆኑ ሁኔታ አመቻቸች!
የትግራይ ህዝብ የመገንጠል ሐሳብ እንዲኖረው ጥረት አደረገች። ለዚህም ከትግራይ ህዝብ ውጭ ያለ ህዝብ ጠላት እንደሆነ ሰበከች። “እኔ ከስልጣን ከወረድኩ ኢትዮጵያ ትፍረስ” አለች። ለዚህም ስለ ኢትዮጵያ መልካም ነገር የሚናገሩ ተጋሩ እንዲሸማቀቁ ተደረገ። “ባንዳ”ም ተባሉ።
በህወሓት ህግ ሦስት ተግባራት “ባንዳ” ያስብላሉ
1. ከዶር ዐብይ ጋር የታየ፣ ፎቶ የተነሳ ወይ ዶር ዐብይን የማይቃወም ትግራዋይ … ባንዳ ነው።
2. የአማራ ህዝብን የማይሳደብ ወይ የአማራ ህዝብን የማያጥላላ ወይ ስለ አማራ ህዝብ መልካምነት የሚመሰክር ትግራዋይ ባንዳ ነው።
3. ህወሓትን የሚቃወም ወይ ህወሓትን የማይደግፍ ትግራዋይ “ባንዳ” እንዲባል ተደርጓል።
በዚህ ገንጣይ አሰራር ተጋሩ የመገንጠል ስሜት እንዲያዳብሩና ኢትዮጵያም እንድትዳከም ተሰርቷል።
ለምን?
ተጋሩ የመገንጠል ስሜት እንዲያዳብሩ የተፈለገበት ምክንያት የህወሓትን የመደራደርያ ዓቅም (Bargaining Power) ለማሳደግ ነው። ምክንያቱም ተጋሩ የመገንጠል ስሜት ካዳበሩ … ይህንን ነገር ማስተካከል የሚችል አካል ህወሓት ነው። ስለዚህ ትግራይ እንዳትገነጠል ህወሓትን መንከባከብ አለብን የሚል አቋም ተወስዶ ህወሓቶች እንደፈለጉ በአዲስ አበባ ጎደናዎች እንዲፈነጩ እንዲደረግ ነው።
ስለዚህ በትግራይ የመገንጠል ስሜት እንዲዳብር ሲሰራ የነበረው ሆን ተብሎ የህወሓትን አስፈላጊነት እንዲጨምር ለማድረግ ነው፤ ለመደራደር!
በዚህ ምክንያት የትግራይ ህዝብ “ዐብይ ይወረሃል፣ አማራ ጠላትህ ነው፣ በብሄርህ ምክንያት እየተጠቃህ ነው፣ ኢህአዴግ የለም፣ ኢትዮጵያ ፈርሳለች … ወዘተ” ኢያሉ ሌት ተቀን አጭበርብረዋል።
የብሄር ፖለቲካ አስፋፍተው ዜጎች በብሄራቸው ምክንያት ሲጠቁ “በማንነትህ ምክንያት ተጠቃህ” ብለው ራሳቸው በፈጠሩት ችግር መልሰው ለራሳቸው የፖለቲካ ጥቅም ያውሉታል። “ህወሓትና የትግራይ ህዝብ አንድ ናቸው” እያሉ ተጋሩ ዒላማ ይደረጉና ከተጋሩ ጥቃት የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ይሞክራሉ።
ባጭሩ ህወሓት የትግራይ ህዝብ የመገንጠል ስሜት እንዲያዳብር ትቀሰቅሳለች። ተመልሳ “የመገንጠል ስሜቱ” ለመደራደርያ ታቀርበዋለች። ደብረፅዮን እየተናገረ ያለውም የዚህ የህወሓት የመደራደርያ ዓቅም ግንባታ (የፖለቲካ ስትራተጂ) አንድ አካል ነው። የዚህ ሁሉ ችግር ህወሓት ራሷ ናት።
ህወሓት ሙሉ በሙሉ ከኢትዮጵያ (ከትግራይም ጭምር) ብትባረር ኖሮ የትግራይ ህዝብ በማንነቱ ምክንያት አይጠቃም ነበር። የመገንጠል ስሜትም አያሳድርም ነበር።
ስለዚህ መፍትሔው መደራደር ሳይሆን ህወሓትን ከስልጣን ማባረር ነው። ህወሓት ከስልጣን ከተባረረ ኢትዮጵያ ሰላም ትሆናለች።
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር! አሜን!!!
Filed in: Amharic