>

የጣሊያኑ ማፊያና የኢትዮጵያው ግንቦት ሰባት (አሊጋዝ ይመር)

የጣሊያኑ ማፊያና የኢትዮጵያው ግንቦት ሰባት

አሊጋዝ ይመር

በዘመነ ደርግ አንድ አሣዛኝ ታሪክ በፖሊስና እርግጫው ሬዲዮ ሲተረክ ሰምቻለሁ – ይቅርታ ካልዘነጋሁት “ፖሊስና እርምጃው” ይባል መሰለኝ፡፡ እሱም ፖልጌቲ ስለሚባለው በማፊያዎች ስለታፈነና ልጁን ለማስለቀቅ ቤተሰቦቹ የተጠየቁትን ብዙ ገንዘብ መክፈል ባለመቻላቸው ምክንያት ሕጻኑን እየቆራረጡ መንገድ ላይ ያሰጡበት የዐረመኔነት ተግባር ነው፡፡ እመኑኝ በተለይ ይህ ማፊያ ድርጅት ሰሞኑን በግፍ ባባረራቸው የቀድሞ የኢሣት ባልደረቦች ላይ ተፈጸመ የተባለው ድብደባና የግድያ ሙከራ እውነት ከሆነ ግንቦት ሰባትም ከዚህ ድርጅት የባሰ ለኢትዮጵያ አደገኛ የመርዝ ብልቃጥ ነው፡፡ ይህን የሰሞኑን ቅሌታቸውን ይበልጥ ለመረዳት የድርጅቱን ግለ ታሪክ ከኤርትራ በረሃ ጀምሮ በንጹሓን ዜጎች ላይ የፈጸሙትን ግፍና በደል መከታተል ይገባል፡፡ አንዴ ሲገለጥ ሌላ ጊዜ ሲደበቅ የነበረው እፍርታሙ አስነዋሪ ጭራቅ ግ7 መለመላውን ወጥቶ በሕዝብ ዘንድ ሲዖላዊ ጥርሶቹን ማግጠጥ ጀምሯል፡፡ ከዚህ ዐውሬ እንዲታደገን በየእምነታችን መጸለይ ለነገ የማይባል ወቅታዊ ጥሪ ነው፡፡ ቁጭ ብለን በሰቀልናቸው ነገሮች ፍዳችንን እያየን ዓለማችን እስክታልፍ መሰቃየት የለብንም፡፡ ለሁሉም ነገር ለከት አለው፡፡ …

አንዳንድ ጽሑፎችን ሳነብ አእምሮየ ክፉኛ ይረበሻል፡፡ በሰው ልጅ ከንቱነት ዙሪያም አጥብቄ እመራመራለሁ፡፡ ለአንዲት እንጀራና ለአንዲት ዘመን ዝና ሰዎች ይህን ያህል ከሰውነት ተራ ለምን እንደሚወጡ ሳስብ እጅግ እገረማለሁ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ያሰቡት ነገር ካልተሳካ ዕድሜና የጉልበት መዛል ሳይገድባቸው እስከለተ ሞታቸውም ቢሆን ሁለገብ ጥረታቸውን ይቀጥላሉ፡፡ ከሕይወታቸው ውጣ ውረድም ሆነ ከታሪክ በፍጹም ሊማሩ አይፈልጉም፡፡ አንዴ ስለዘጋባቸው በሚያደርጉት ሰይጣናዊ ዕኩይ ድርጊት ቆርበው እስከመጨረሻው ይዘልቃሉ፡፡

በመሠረቱ ግመል ሰርቆ አጎንብሶ አይኬድም፡፡ ሣል ይዞ ስርቆትም አይቻልም፡፡ በዚህ የዕውቀት ዘመን ደግሞ አንድን ድርጊት ማን እንደፈጸመው ወይም ቢያንስ ማን ሊፈጽመው እንደሚችል ማንም ደንቆሮ ሊገምተው የሚችል ተራ ነገር ነው፡፡ ሰው ግን ከንቱ ነው፡፡ የከንቱ ከንቱ፡፡ ዕቅዱን ያሳካለት ይምሰለው እንጂ ስለሚሠራው መጥፎ ተግባር ቅንጣት አይጨነቅም፡፡ የሚሠራው ሸርና ተንኮል እንዲሁም የግፍ ተግባር ደግሞ በሕዝብ ዘንድ ታወቀ አልታወቀ ጉዳዩ አይደለም፡፡ እንጂ በነኤርምያስ ላይ የተሞከረውና ከደቂቃዎች በፊት በተቦርነ በየነ የፌስቡክ አካውንት ላይ እንዳነበብኩት (እውነትም የርሱ አካውንት ከሆነ) በነዚህ ልጆች ላይ ይህን አስቀያሚ ድርጊት ሊፈጽመው የሚችለው ከግንቦት ሰባት በስተቀር ሌላ ምድራዊ ኃይል ሊሆን አይችልም፡፡ ገንዘብ ያለው ጉልበትም አለውና ዱርየዎች ዱርየን መግዛት አይሳናቸውም፡፡ ትዝብቱና ታሪካዊ ቅጣቱ ግን ከፊት ለፊታቸው እንደተደቀነ አልተረዱም – ምናልባትም አይረዱትም፡፡ ለምን ቢባል በበቀልና በሤራ ፖለቲካ አንዴውኑ ታውረዋልና፡፡ ያሳዝናል፡፡ እያደሩ ጥሬና ከርሞ ጥጃ ማለት በቁም ትርጉሙ እንደነዚህ ዓይነት በሥልጣንና በሀብት አራራ ያበዱ ሰዎች ማለት ነው፡፡ ለዕኩይ ተግባራቸውና ለውሸታቸው ደግሞ በጭራሽ መሥፈሪያ አይገኝም፡፡ እመብርሃን ትጎብኛቸው፡፡

የክንፉ አሰፋን ጽሑፍ ethiomediaforum.com ላይ አንብቤ ስጨርስ ተደንቄ ወደቤቴ ልሄድ ስል ዘሀበሻ ላይ የግንቦት ሰባት አንዱ ማፈሪያ ማፊያ የጻፈው የሚመስል – እንዲህ መባል ስላለበት ነው እንዲህ የምለው – አዎ፣ የግንቦት ሰባት ዱርዬ የጻፈው የሚመስል ዜና በዘሀበሻ ስም መሠራጨቱን አነበብኩ፡፡ እኔም ተናደድኩ፡፡ ተናደድኩናም ይህችን አጭር ማስታወሻ ጽፌ ላክሁ፡፡ ነገርዬው እውነት ይሁን ሀሰት ሌላ ጉዳይ ሆኖ ዘሀበሻ ድረገፅ እንደዘገበው ከርሱ ዕውቅና ውጭ ማለቴ በርሱ ስም በተከፈተ የሀሰት አካውንት በስሙ ተነግዶበታል፡፡ በእግረ መንገድም ተሰሚነትና ብዙ ጎብኚ አላቸው ብለው የሚያስቧቸውን ድረገፆች ስምም ለማጠልሸት ብዙ ማይል መጓዛቸውን ይህ ክስተት ይጠቁማል፡፡ በነሱ ድረገፆች ለምሣሌ በኢካድፍ ቢያወጡ ይችሉ ነበር፡፡ ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥረው እንደልብ በሚፈነጩበት ኢሳትም ሊዘግቡት ይችሉ ነበር፡፡ የነዚህ ሰዎች አካሄድ በጭራሽ ግራ እያጋባን መጥቷል፡፡ ሰው ተስፋ ሲቆርጥ ይቶብታል፤ ንስሃውን አውርዶ ገዳም ይገባል፤ ወደ ኅሊናው ተመልሶ በአርምሞ መኖር ይጀምራል፡፡ የነዚህ ግን በካፈርኩ አይመልሰኝ ወያኔን በሚያስከነዳ ጭካኔና ዐይነ ደረቅነት ያዝጉን ገቡ – በልጆች ቋንቋ፡፡ መጨረሻቸውን ያሣምርላቸው፡፡የሥልጣን ሱስ እንዲህ የሚያሳብድ ከሆነ ግን ባፍንጫችሁ ይውጣ፡፡ እየባሰባቸው ሄደ እኮ፡፡ ዱሮ ብዙዎች ስለነዚህ ማፍያዎች ሲናገሩ አላመንናቸውም ነበር፡፡ የምቀኝትና የድንቁርናም ይመስለን ነበር፡፡አሁን ግን ሁሉም ለዬ፡፡ ቂጣውም ጠፋ፤ ሽሉም ገፋና ተወለደ፡፡ ከአሁን በኋላ የጦርነቱ ጎራ ሳይሆን የድሉ ባለቤት ብቻ ነው በጉጉት የሚጠበቀው፡፡

ለራሳቸው ስል ሥልጣን እንዳይዙ ከምታገልላቸውና በሌላ ማኅበራዊ የሙያ ዘርፍ ሀገራቸውን እንደሚያገለግሉ በማመን እጅግ የምሳሳላቸው ሰዎች አሉ – ክፉም ሆኑ ደግ፤ አምባገነንም ሆኑ ዴሞክራት፡፡ ከነዚህ አንዱ የግንቦት ሰባት የዕድሜ ልክ ሊቀ መንበር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ናቸው፡፡ ይቅርታ ይደረግልኝና የተማመኑበትን አላውቅም ፕሮፌሰሩ በስተርጅና ዕድሜያቸው ገደማ ለይቶላቸው ወደ ማፊያነት ሳይገቡ የቀሩ አይመስለኝም – የነኚያ የፈረደባቸው የሤራ ፖለቲካ ጠንሳሾች የኢሉሚናቲ ተብዬዎቹ አለቃ ሚስተር ሉሲፈር ፕሮፌሰሩ ከመሰሎቻቸው ጋር ተባብረው ኢትዮጵያን ካጠፉለት ልዩ ሽልማት ሳያዘጋጅላቸው አልቀረም፡፡ የማፊያነት መጨረሻው ደግሞ አንድም ማበድ አሊያም እውነተኛ የፍትህ ሥርዓት ሲመጣ የሥራን ማግኘት ነውና ሰውዬው ይህንንም አውነታ እንዳይዘነጉት ይሁን – ሰውን እያሳሰሩ፣ እያስደበደቡና እያስገደሉ በመጨረሻ የጽድቅ አክሊል እንደማይገኝ ከሂትለርና ከሙሶሊኒ መማር አለባቸው – ፕሮፌሰሩ፡፡ ሰውዬው ከያዙት የመጥፎ መጥፎ አማራጭ ይልቅየስ ታዲያ በተማሩበት ሙያ ሀገርን ማገልገል ያባት ነበር፡፡ ሟች ይዞ እንደመሞቱ የት ይደርሳሉ የተባሉ ዕውቅና ምሥጉን ጋዜጠኞችንና አክቲቪስቶችን ሳይቀር ይዘውብን ጠፉ፡፡ እኔንማ በኢሳት ምክንያት ከተቆራረጥኩት ቤተሰቤ ጋር አስታረቁኝ፡፡ እግዜር ይስጣቸው፡፡ አሁን ወደ ጤንነቴ ተመልሼ በተቅጠፍጣፊ ሸንጋይ ምላስና በግንቦት ሰባት ሳቢያ ከቤተሰቤ ጋር መጨቃጨቁን ተውኩኝ፡፡ በፍቅርና ውዴታ ምትክ ፊት መዟዟር ሲመጣ ለካንስ መጥፎ ነው፤ በብዙ ፍቅር ውስጥ ብዙ ጠብ የመኖሩ ምሥጢር አሁን ገና ገባኝ፡፡ እነዚህ በፍቅር ጭልጥ ብለው የከነፉ የኦህዲድና የግንቦት ሰባት ሊቃነ መናብርት የቀሙኝን ጊዜና ትኩረት ስለመለሱልኝ በአንድ በኩል ባለውለታየ ናቸው፡፡ “አጭበርባሪ አይተኛኝም” የምትል ተራ ሴተኛ አዳሪ ቅኔ በምትዘርፍባት ሀገር እነዚህን የመሰሉ ቁጭ በሉዎችንና የፖለቲካ ማጅራት መችዎችን ማየት የሰው ልጅን ተፈጥሮ ደግመን ደጋግመን እንድንመረምር ያስገድደናል፡፡ ተማረ የተባለው በዚህ ደረጃ ወርዶ ሕዝብን ካታለለና ካጭበረበረ ያልተማረው የኔቢጤ መደዴማ ምን ያደርግ? ብርሃኑ ነጋ ኢሳትን በዚህ መልኩ ከዘወረና ዓለምን በተለይም ጦቢያውያንን እንደዚህ በሸፍጥና በኢንትሪግ ካመሰ ከእንግዲህ ማን ይታመናል? በዴሞክራሲ እየተቀለደ እንዲህ መሥራት የተቻለው በርግጥም በዓለማችን የዴሞክራሲ ኅልውና አንጻራዊ እንጂ ፍጹም ባለመሆኑ ነው፡፡ እውነት ነው – ትንሹ ጆርጅ ቡሽም ሆነ ትራምፕ የመጡት በዴሞክራሲ ነው፡፡ ሆኖም ከነብርሃኑ በሚሻለው የፌክ ዴሞክራሲ እንደመጡ የሚገባን አሠራራቸው ይበልጡን ወደነብርሃኑ የተጠጋ አምባገነናዊ መሆኑን ስንመለከት ነው፡፡ ግንቦት ሰባት እግዜር ይይልህ…. ላይጠቅመኝና ላይጠቅመን በከንቱ ያስለፈልፈኛል፡፡ ወይ ይቺ አንዲት እንጀራ!!!

ከሀብት ሀብት፣ ከትምህርት ትምህርትና ከልምድም ልምድ እጅግ በብዙው ያላቸው እኚህ ታዋቂ ሰውዬ ቀደም ሲል ስለድርጅታቸው ዓላማ ሲጠየቁ “በማንኛውም ሥልትና ዘዴ ወያኔን ከሥልጣን ማባረር ነው” ብለው ነበር፡፡ በርሳቸው ሁለንተናዊ የትግል ሥልትም ይሁን በሰይጣን እገዛ ትንቢታቸው ሠምሮ ወያኔ ከአራት ኪሎ በብዙ ኪሎ ሜትሮች ተባርሯል – ምንም እንኳን ጥላው ገና በተተኪው ሰውዬ አልጋ ላይ እንደ አጎበር ሆኖ በግልጽ ቢታይም፡፡ ፕሮፌሰሩ የተናገሩት – ልድገመው – “በማንኛውም ዘዴ ወያኔን ከአራት ኪሎ ማባረር” የሚለው መዝሙር እውን ከሆነ በኋላ ሰውዬው ዕብሪታቸው ከወትሮው ለዬት ባለ ሁኔታ ጨምሯል፡፡ ማንንም የመናቅ “ሣይንሳዊ ችሎታቸው” መለኪያ አጥቷል፡፡ ጥጋብ አንብርሯቸዋል፡፡ የኦህዲድ የተስፋ ቃል በሥልጣን የሰማይ ሠረገላ አክንፏቸዋል፡፡ ይሰብኩት ከነበረው ዓላማቸው 360ዲግሪ ዞረው ከተቃቀፉት ፀረ-አማራና በእግረ መንገድም ፀረ-ኢትዮጵያ ከሆነው ገዢ ፓርቲ ጋር የመሠረቱት ፍቅር የሮሚዮና ዡልየትንና የበዛብህና የሰብለ ወንጌልን የፍቅር እስከ መቃብር ምናባዊ ሮማቲክ ቁርኝት የሚያስንቅ ሆኗል፡፡ ግን ግን ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን አላወቋቸውም – በጭራሽ፡፡

ዛሬ ልትገድል ትችላለህ፡፡ ዛሬ በማንኛውም ዓይነት ሥነ ልቦናዊም ይሁን አካላዊ ጥጋብ ተወጥረህ ልታቅራራ ትችላለህ፡፡ ዛሬ በትዕቢትና በትምክህት ተወጥረህ አገር ይያዝልኝ ልትል ትችላለህ፡፡ ዛሬ ባለህ ሀብትና ዝና ዜጎችን ልታንበረክክ፣ ልታሰግድና የፈለግኸውን ሌላ ነገር ልታስደርግ ትችል ይሆናል፡፡ ዛሬ ሁለመናህ እንደ እፉኝት አባብጦ ንግግርህ ይቅርና ድርጊትህ ሁሉ እንደኢዲያሚንና እንደቦካሣ ሊሆን ይችላል፡፡ ግን የነዚህንና የሌሎቹንም መሰል ደምባራ አምባገነኖች የመጨረሻ ዕጣ ካላወቅህ ጅል ነህ፡፡ እባክህን ይህን መሰሉን ጅልነትህን ከባሕርይ መዝገብህ አውጣው፡፡ ደግሞም ታረጃለህ እኮ — በትንታ ሳይቀር በትንሽ ምክንያት ከዚህች ቆሻሻ የዲያብሎስ ዓለም ታልፋለህ እኮ… ትታመምና ትሞታለህም… ትከብርና ትደኸያለህ… ምን ነካህ ታዲያ?
ብርሃኑን አምነውና እንደእግዜር አይተው አሁን ሲጃጃሉ የምናያቸው ትልልቅ ጋዜጠኛና አክቲቪስቶችም በገቡበት አሮንቃ ያሳዝናሉ፡፡ የኢትዮጵያ አምላክ ይድረስላቸው፡፡ ከግለሰብ አምልኮት አውጥቶም ለሚወዳቸው ሕዝብ ያብቃቸው፡፡ የነመንግሥቱንና የነመለስን፤ የነዚያድባሬንና የነጋዳፊን መጨረሻ ያዬ እንኳንስ ቤተ መንግሥት ሳይገባ ከገባም በኋላ በነፍሱና በቀሪ ታሪኩ ሊቀልድ አይገባም፡፡ ሰዎች ግን ምን ነካን? ወዴትስ እያመራን ነው? አያ ዲያብሎስ ምን አዞረብን? ሱባሃን አሏዋህ!

መሰነባበቻ፡፡ አንድ ሰውዬ በሠጋር በቅሎው አንድ ጫካ አቋርጦ ወደ ጉዳዩ ይገሰግሳል፡፡ ወገቡን ዳበስ ሲያደርግ ሽጉጡን ያጣታል፡፡ ያኔ “እመብርሃን ሽጉጤን ያስገኘሽልኝ እንደሆነ አንድ ድፎና አንድ ጋን ጠላ ስለትሽን አስገባለሁ” ብሎ ይሳላል፡፡ ጥቂት ወደ ኋላው እንደተመለሰ ሽጉጡ መንገድ ላይ ወድቃ እንደፀሐይ እያበራች ያገኛታል፡፡ ሰውዬው አፍታም ሳይወስድበት “እመብርሃን የነገርኩሽን ተይው፣ አትቸገሪ ሽጉጤን አግኛቻታለሁ፡፡” ይልና ቃሉን ያጥፋል፡፡ ይህ ሰው ሸፍጠኛ ነው፡፡ ይህ ሰው የማይታመን ጋጠወጥ ነው፡፡ ይህ ሰው ሃይማኖት የለሽ ነው፡፡ ይህ ሰው ለራሱ ጥቅም ሟች እንጂ ለእምነቱና ለፍልስፍናው ግድ የለውም፡፡ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ትልልቅ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ቦታዎችን ሲያገኙ ሀገር ትጠፋለች፤ ሕዝብም ይቆረቁዛል፡፡ ባለፉት 50 ዓመታት ኢትዮጵያን የገጠሟት የፖለቲካና የኢኮኖሚ (ንግድ) ሰዎች ልክ እንደዚህ ቀጣፊ ሰውዬ ይመስላሉ – ግንቦት ሰባትም፡፡ እንዘደዚህ ከመሆን ያውጣን፡፡ ለመማርና ለመመማማርም ልብ ይስጠን፡፡ ሁሉም አለቀ፤ የቀረ የለም፡፡ የመቀዳደም ካልሆነ ሁላችንም የምንሄደው ሌሎችን ሳይወዱ በግዳቸው ሕይወታቸውን እየቀጠፍን ቀድመን ወደምንልካቸው ቦታ ነው – እንዲያውም የነሱ መጨረሻ ከኛ የተሻለ ነው፡፡ ስለዚህ ወደ ኅሊናችን እንመለስና ሰዎች እንሁን፡- የታሪካችን ሞራላዊ ጭብጥ ይህ ነው፡፡ሰዎች ስንሆን ዘረኝነትንና ጎጠኝነትን፣ ስግብግብነትንና ሆዳምነትን እንጠየፋለን፡፡

ጸሃፊውን ለማግኘት

aligazyimer@gmail.com

Filed in: Amharic