>

ብሔር፥ ብሔረሰብ፥ ሕዝብ፥ ነገድ!!! (ጌታቸው ሀይሌ)

ብሔር፥ ብሔረሰብ፥ ሕዝብ፥ ነገድ!!!
ጌታቸው ሀይሌ
እነዚህን ቃላት እንድተች ብዙ ጊዜ እጠየቃለሁ። ብዙዎችን የሚገድ ጥያቄ ስላልመሰለኝ ጥያቄውን ችላ ብየው ነበር። የማይገዳቸው ላያነቡት ይችላሉ ብዬ ከዚህ በታች ያለውን አረቀቅሁ። ረቂቁ ሙሉ በሙሉ ጥንታዊ (original) አይደለም። ካሁን በፊት ከጻፍኳቸው ውስጥ “የተኮረጁ” አሉበት።
“ብሔር” የግዕዝ ቃል ነው። ትርጉሙ “ሰው የሚኖርበት ሀገር” ማለት ነው። “እገሌ ዘብሔረ ቡልጋ፥ ዘብሔረ ጅማ፥ ዘብሔረ ሸዋ፥ ዘብሔረ ኢትዮጵያ፥ . . .” ይባላል። (“እግዚአ ብሔር” ማለት “የመላዋ ምድር ጌታ” ማለት ነው።) ፖለቲከኞች የሚጠቀሙበት ግን “ትንሽ ጎሳ” ለማለት ነው። ስሕተት ነው። ብሔር የሚያመለክተው ምድሩን (ቀየውን) እንጂ፥ በምድሩ ላይ የሰፈረውን ሰው አይደለም። ግን አጉል ልማድ ሆኖ ተለምዷል።
“ብሔረሰብ” የሚለው “ብሔር” እና “እሰብ[እ]” ተናብበው የተፈጠረ ቃል ነው። “ብሔር” ያው እንዳልኩት “ሀገር፥ ምድር፥ ቀየ” ማለት ነው። “ሰብ[እ]” በግዕዝ “ሰው” ማለት ነው። “እ” ወድቃ ቃሉ “ሰብ“ ሆኗል። “ቤተሰብ” (የአንድ ቤት ሰው) የሚለውን ቃል እናውቃለን። በዚያው ዘዴ፥ “በአንድ ሀገር የሚኖሩ ሰዎች” ለማለት “ብሔረሰብ” የሚለውን ቃል ፈጠሩ። የብልጥ ፈጠራ ነው።
“ጎሳ” የኦሮሞ ቃል ነው። ትናንሽ ነገዶች ጎሳ ይባላሉ። የኦሮሞና የሱማሌ ሕዝብ የብዙ ጎሳዎች ስብስብ ናቸው። ነገድ ከጎሳ ይበልጣል። አማራ፥ ትግሬ ነገድ ናቸው። ቦረን እና በረይቱማ ራሳቸውን የቻሉ ነገዶች ነበሩ። ጎሳና ነገድ በባህል አንድ ዓይነት ሕዝብ ነው። አንድ የሚያደርጋቸው ባህል ሆኖ ሳለ፥ ፖለቲከኞች የሥጋም ያደርጉታል።
 –
“ሕዝብ” የሰው ስብስብ ማለት ነው። አንድ ዓይነት ሊሆንም ላይሆንም ይችላል። ገበያ ላይ የምናየው፥ ንግግር ለመስማት የሚመጣው ሕዝብ ያሰባሰባቸው ዝምድና አይደለም። ገበያው ሲፈታ፥ ንግግሩ ሲያልቅ ሕዝቡ ይበተናል። “የእገሌ ነገድ አባል ነኝ” ማለት ይቻላል። “የሐሙስ ገበያ ገበያተኞት አባል ነኝ” አይባልም። “የእገሌ ንግግር ሰሚዎች አባል ነኝ” አይባልም።
 –
“ብሔር፥ ብሔረሰብ” የሚሉት ስሞች የወጡት “Nations and Nationalities” የሚለውን ለመተርጐም ነው። ግን መጀመሪያ በመተርጐም ምክንያት የተፈጸሙትን ሁለት ታላላቅ ስሕተቶች ማረም ያስፈልጋል። አንደኛ፥ አንድ የውጪ ቃል ወይም ስም የሚተረጐመው፥ አንድ እቃ ወይም አንድ ፅንሰ-ሐሳብ ከነስሙ ከውጪ ሲመጣ ነው እንጂ፥ እኛ ዘንድ ላለ ነገር አይደለም። ለምሳሌ፥ “ወምበር” ከነስሙ እኛ ዘንድ ካለ፥ “chair” ለሚለው ስም መተርጐሚያ ቃል ፈልጉ አይባልም። “ነገዶችና ጎሳዎች” ነገዶችና ጎሳዎች ከመባል ይልቅ “Nations and Nationalities” እንበላቸው ማለት ሳይቸግር ጤፍ ብድር ይሆናል።
 –
ሁለተኛ፥ ነገዶችና ጎሳዎች በ“Nations and Nationalities” መተርጐም ሳይቸግር ጤፍ ብድር ብቻ ሳይሆን፥ “Nations and Nationalities” ላይ የሰፈረውን ጣጣ አብሮ ማምጣት ይሆናል። ያ ጣጣ እኮ ነው መፍትሔ ጠፍቶለት ስለ ኢትዮጵያ ፖለቲካ በተወያየን ቍጥር ስናገላብጠው የምንኖረው። “Nations and Nationalities” እዚያው ሀገራቸው መንግሥት አላቸው (ወይም ነበራቸው)።
ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ነገዶች ከኢትዮጵያ ውጪ መንግሥት ያቋቋሙበት ዘመን አልነበረም። ኖሯቸው ከሆነ፥ በዘመነ መሳፍንት ሸዋ፥ ጐጃም፥ ትግሬ፥ ወሎ፥ አደል (አዳል) ውስጥ እንደተቋቋሙት አናሳ መንግሥታት ቢሆን ነው። ግራኝ ያመፀው እኮ “አልገብርም፥ በክርስቲያን ንጉሥ ስር ያለች አናሳ አገር ኢማም መሆን ያንሰኛል” ብሎ ነው እንጂ፥ ከቀይ ባሕር እስከ ህንድ ውቅያኖስ የተንሳፈፈውና የነገሠባት የአዳል ሀገር የኢትዮጵያ ግዛት አይደለም ብሎ አይደለም።
ብሔርማ ትርጕሙ “አገር” ስለሆነ፥ የሚያመለክተው ምድሩን እንጂ ሕዝቡን አይደለም። ይህ ሁሉ ሳይመረመር፥  ነገዶችና ጎሳዎች በ“Nations and Nationalities” ትርጐማ ጊዜ “ብሔር፥ ብሔረሰቦች” ስለተባሉ፥ እንደ “Nations and Nationalities” ተገንጥለን መንግሥት እናቋቁም ማለትን አምጥተው ታሪካዊቷን ኢትዮጵያ ውጥረት ላይ ጣሏት፤ መሠረቷን አናጉት። ታሪካዊት ያደረጓት የሁላችንም ወላጆች መሆናቸውን የሚያሳይ ማስረጃ ሲያቀርቡላቸው፥ “አታሳዩን” አሉ። “ሃይማኖታችሁን ለውጡ” የተባሉ መሰሉ።
የነገዶችና ጎሳዎች ፍላጎትና ሚና
ሚሲዮናውያን በደረሱበት ቦታ ሁሉ ያገኙትን ቋንቋ የጽሑፍ ቋንቋ ሲያደርጉት የኢትዮጵያ መንግሥት ሲያይ፥ የሀገሪቱን አንድነት የሚያሰጋና የመገናኛውን ቋንቋ (አማርኛን) ከመስፋፋት የሚገታ ስለመሰለው፥ ከአማርኛ በቀር ሌሎቹ በጽሑፍ እንዳይውሉ ከልክሎ ነበር።
ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ ይሆናል እንጂ፥ መንግሥት ማድረግ  የነበረበት ከአማርኛ ጋራ የጎሳ ቋንቋዎችን እንዲያስተምሩ መፍቀድ ነበረ። አሁን እነዚህን ቋንቋዎች ከሚናገሩ አንዳንድ ፖለቲከኞች የሚሰማው ወቀሳ በቋንቋቸው እስከጭራሹም እንዳይናገሩበት ተከልክለው ነበረ የሚል ነው።
 –
ማናቸውም የኢትዮጵያ ቋንቋ እንዳይሞት መጠበቅ፥ በጽሑፍም መዋል አለበት። መጻፊያውን ፊደል የሚመርጡት እነሱ ናቸው። ግን እኔ ብጠየቅ፥ አገር በቀሉን የኢትዮጵያ ፊደል እንዲመርጡ እመክራለሁ። በኢትዮጵያ ፊደል ላለመጻፍ የሚሰጠው ምክንያት ጥላቻን መሸፈኛ ነው።
ነገዶችና ጎሳዎች፥ የሃይማኖት ምእመናንም በፖለቲካና በሀገሩ ኢኮኖሚ ውስጥ የሚጫወቱት ትልቅ ሚና አላቸው። ግን ሚናቸው ማኅበራዊ ድርጅት (civic organization) ሆኖ ወገናቸውን ማገልገል እንጂ ብሔራዊ የፖለቲካ ፓርቲ አቋቁሞ አይደለም። የፓርቲዎች መሠረት አገር-አቀፍነት ነው።
የአማራ፥ የወላይታ፥ የሲዳማ፥ የኦሮሞ፥ ወዘተ. ፓርቲ አገር-አቀፍ ሊሆን አይችልም። ደግሞም እኮ፥ “የኔ ነገድ፥ የኔ ሃይማኖት ይግዛ” ማለት ሰብአ-ትካትነት፥ ኋላ ቀርነት ከመሆኑ በላይ፥ የትኛውም ነገድ የሀገሪቱ አርባ በመቶ እንኳን ስለማይሆን፥ የነገድ ፓርቲ ምርጫ የማሸነፍ ዕድል የለውም። ግፋ ቢል የኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታዮች ፓርቲ ቢያቋቁሙ ያሸንፉ ይሆናል። የሀገር ወዳዱ ምኞች ግን በሀገሩ ኢኮኖሚ ላይ የተመረኰዘ ሞላውን ኢትዮጵያን የሚወክል ፓርቲ እንዲቋቋምና እንዲያሸንፍ መሆን አለበት።
የነገድ ተቈርቋሪዎች በማኅበራዊ ድርጅት ግን ብዙ ሥራ ሊሠሩ ይችላሉ። ባህላቸውን (ቋንቋቸውንና ሃይማኖታቸውን) ያስፋፋሉ፤ የቀያቸውን ኢኮኖሚ ያዳብራሉ፤ መንግሥት ያላሟላውን የትምህርት፥ የጤና ጥበቃ፥ የመንገድ ሥራ ያሟላሉ። በምርጫ ጊዜ ድምፃቸውን ለሚፈልጉት ተወዳዳሪ ይሰጣሉ።
ናፍቆታችን የኢትዮጵያ ሕዝብ በጻፈው ሕገ መንግሥት ተጠብቆና ሕጉን እነሱም ጠብቀው፥ ረኀብ፥ በሽታ፥ ድንቁርና የሚወገዱበትን መንገድ እየፈለጉና እያደረጉ በነፃ መኖር የሚችሉት እነዚህን እርምጃዎች ሲወስዱ ነው።
Filed in: Amharic