>

ሽብር በአዋሳ እና የመንግሥት ዝምታ (ፀሀፊ፤ ዳሞ ጎታሞ (Damo Gotamo) ትርጉም፤ መስፍን ማሞ ተሰማ)

ሽብር በአዋሳ እና የመንግሥት ዝምታ

ፀሀፊ፤ ዳሞ ጎታሞ (Damo Gotamo)
ትርጉም፤ መስፍን ማሞ ተሰማ

 

የሲዳማ ፅንፈኞች የአዋሳን ህዝብ ማሸበር ከጀመሩ እነሆ ዓመት ሆናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው አንድ ዓመት በፊት መንግሥታዊ ሥልጣናቸውን ተጠቅመው ሲዳማ ያልሆነውን ህዝብ ያስፈራሩና ያዋክቡት ነበር፤ አሁን ደግሞ በግላጭ የከተማዋን ህዝብ ማሸበርና አካላዊ ጥቃት ወደ መፈፀም ተሸጋግረዋል። ዘግናኝ ወንጀሎችን እየፈፀሙ የሚጠይቃቸውም በሌለበት የሥልጣን ከለላ ውስጥ ይኖራሉ።

ባለፈው ዓመት በፍቼ ጨምበለላ በዓል ወቅት የሲዳማ ፅንፈኞች ሰዎችን ከነነፍሳቸው አቃጥለዋል፤ በሺዎች የሚቆጠሩትን የከተማዋን ነዋሪዎች አፈናቅለዋል። የወላይታዎችን መኖሪያ ቤቶች አውድመው ንብረቶቻቸውንም ዘርፈዋል። ይህንን ወንጀል የፈፀሙ ሽብርተኞች አሁንም በህብረተሰቡ ውስጥ የተናኙ ሲሆን ተጨማሪ ወንጀሎችንም እየፈፀሙ ናቸው።

ከጥቂት ወራት በፊት አሸባሪዎቹ ሲዳማ ያልሆኑ የህብረተሰቡ አባላት ንብረት የሆኑትን መደብሮች አንድደዋቸዋል። አነስተኛ የሸቀጥ መደብሮችን ለማቆም እድሜያቸውን ሙሉ የደከሙ በአንድ ጀንባር ድካማቸው ሁሉ ወደ አመድነት ተለውጧል። ብዙዎች ወደ ጎዳና ተዳዳሪነትና ለማኝነት ተለውጠዋል። ይህ ሁሉ ሆኖም እስካሁን ለፍርድ የቀረበ አንድም የለም።

ባለፉት ጥቂት ወራት የሲዳማ አሸባሪዎች በተደጋጋሚ የመንግሥት መስሪያ ቤቶች፤ ትምህርት ቤቶች፤ ባኖኮችና መገበያያ ስፍራዎችን እንዲዘጉ አድርገዋል። በዚህም ሳቢያ ለተራዘሙ ቀናት የመንግሥት መስሪያ ቤቶች ለደንበኞቻቸው አገልግሎት እንዳይሰጡ አድርጔቸዋል። ባንኮች በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ከስረዋል። ህፃናት በመደበኛነት ትምህርታቸውን እንዳይከታተሉ በማድረግ እድገታቸውን አስተጔጉለዋል። ለነዚህ እኩይ ተግባሮቻቸው ወደ ህግ አደባባይ አንድም የቀረበ የለም።

የልብ ልብ የተሰማቸው የሲዳማ አሸባሪዎች ባለፉት ጥቂት ወራት በከተማዋ የሚገኙትን የቢዝነስ ባለቤቶችን ገንዘብ ለማስገበር ሞክረዋል። ለዓላመቸው ማስፈፀሚያ የሆቴል ባለቤቶችን ገንዘብ እንዲሰጡ የሚያዝ ደብዳቤዎችን አድለዋል። የከተማዋ የቢዝነስ ባለቤቶች የህልውና አጣብቂኝ ውስጥ ቢወድቁም የሲዳማ አሸባሪዎች ግን ገንዘብ እንዲከፍሏቸው ከማስገደድ አልታቀቡም።

ከጥቂት ሳምንታት በፊት የሲዳማ ፅንፈኛ ብርጌድ በደህዴን ስብሰባ ላይ በጉልበት በርግደው በመገኘት የፓርቲውን አባላት ሲደበድቡ የሀገሪቷን ባንዲራ አውርደው የነሱን ምንጣፍ ሰቅለዋል። የመንግሥት ባለስልጣን በዚህ ድብደባ ወቅት ክፉኛ ተጎድቷል። ይህንን ወንጀል የፈፀሙት ወኔ ቢሶቹን ይዞ ለፍርድ ያቀረበ ግን እስካሁን የለም።

ከጥቂት ቀናት በፊት እኒሁ አሸባሪዎች በወላይታ ዲቻ እና በአዋሳ ከነማ ቡድኖች መካከል በተደረገው ውድድር ወደ ስታዲዮሙ በመግባት በእግር ኳስ ደጋፊዎች ላይ የሽብር ጥቃት አካሂደዋል።

ወንጀለኞቹ ከቀናት በፊት ከከተማዋ ፖሊስ እና ከሚታወቁት የጋንጉ መሪዎች ጋር በመሆን ወንጀሉን ለመፈፀም በሚገባ ተዘጋጅተውበታል። የእግር ኳሱ ውድድር ከመጀመሩ በፊት አሸባሪዎቹ ወደ ስታዲየሙ በመግባት ሰላማዊ ተመልካቾችን እና በግዳጅ ላይ ያልነበሩ የወታደሩ አባላትን በመደብደብ አቁስለዋል። በመቀጠልም ይህንኑ አሸባሪ ወንጀላቸውን ከስታዲየሙ ውጪ በሚገኙ ሰዎች ላይ ፈፅመዋል፤ ንብረቶችን አውድመዋል፤ በስፋትም ዘርፈዋል። ይህ የአሸባሪዎች ወንጀል እስካሁንም እንደ ቀጠለ ሲሆን ፅንፈኝነታቸውን በሚቃወሙ የሲዳማ ተወላጆችም ላይ የጥፋት በትራቸውን እያሳረፉ ናቸው።

የከተማዋ የፖሊስ ሀይል የወንጀሉና የሽብርተኖቹ ተባባሪ እና ንቁ ተሳታፊ በመሆኑ ጥፋቱን ለማስቆም አንዳችም ጥረት አያደርግም። ህዝቡ የፖሊስ ሀይሉን ዘራፊዎቹን እንዲያስቆሙ ሲጠይቅ ፖሊስ የሚሰጠው መልስ <የሚበሉት የላቸውምና ምን ይሁኑ፤ ይዝረፉ> የሚል ነው።

የአዋሳ ህዝብ ከሲዳማ አናሳ ከተማ በፈለቁ የተደራጁ ሽብርተኞች የቁም ስቅሉን እያየ ነው። የሲዳማ ፅንፈኞች ምንጭ ለከተማው አዲስ በሆኑና የባህል ግጭት ውስጥ በወደቁ የቤኒሳ (Benesa) አካላት የተነሳ ነው። እኒህ አካላት ከከተማዋ ነዋሪዎችም ሆነ በከተማዋ ዳርቻዎች ከሚገኙት የሲዳማ ወንድሞቻቸው ጋር አንዳችም መግባባት የላቸውም። የአዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ለሰው ህይወት አንዳችም ቁብ በሌላቸው እኒህ አሸባሪዎች እየተሰቃየ ይገኛል።
የሽብርተኞቹ መሪዎች ተግባራት ለባለ ስልጣናቱም ሆነ ለከተማዋ ነዋሪዎች ግልፅ ነው። በመንግሥት ውስጥ ቁልፍ የሥልጣን መቀመጫ ያላቸው ሽብርተኞቹ በከተማዋ ለሚካሄደው ወንጀል ሃላፊዎች ናቸው። በአዋሳ የሽብርተኞቹ አፈ ቀላጤና አደራጅ ታሪኩ ኪማ (Tariku Kima) ይባላል። እሱ በግልፅ የሚንቀሳቀስ ሲሆን የአሸባሪዎቹን ተግባር በሌሎች በማላከከ ይከላከላል።

ግልፅ ሆኖ መታወቅ ያለበት አብይ ጉዳይ ግን ከክልሉ (Regon) ፕሬዚዳንትና ከከተማዋ ከንቲባ ዕውቅና እና ይሁንታ (blessing) ውጪ የሚከናወን አንዳችም ወንጀልና ሽብር እንደሌለ ነው። በከተማዋ የሚካሄደው እያንዳንዱ የአሸባሪዎች ተግባር የሚቀነባበረው በመንግሥት ውስጥ በተለያየ የሃላፊነት ደረጃ በሚገኙ ከፍተኛ ባለስልጣናት ነው።
ወንጀለኞቹን ከማስወገድ ይልቅ አቶ ሚሊዮን ማቲዎስ እጅግ የሚጠላውን ሽብርተኛውን ኢጀቶ ወደነበረበት ለመመለስ አበክሮ እየሰራ ይገኛል። ባለፈው ሳምንት የከተማዋን ቢዝነስ ባለቤቶች ለሲዳማ ዕቅድ (cause) ብሎ በመሰብሰብ ገንዘብ እንዲያዋጡ ሲጠይቅ ባለፈው ዓመት በከተማዋ በወላይታ ተወላጆች ላይ ለተፈፀመው ጥቃት ተጠያቂዎቹ የማይታወቁ ሌሎች ሀይሎች እንደሆኑ ነው የተናገረው። ነገር ግን እሱ ሚሊዮን ማቲዎስ ለተፈፀሙት ወንጀሎች ሁሉ ተጠያቂ ነው።
የሲዳማ ፅንፈኞች በአዋሳ ከተማ ቅጥ የለሽ ወንጀሎች ሲፈፅሙ የፌዴራል መንግሥት ፍፁም ዝምታን መርጧል። ጭው ያለው የፌዴራል መንግሥት ዝምታ እና ዜጎቹን ከዝርፊያና ከሞት መከላከል አለመቻሉ ብዙዎችን ግራ አጋብቷል። ብዙዎች መንግሥት በተዘዋዋሪ ሽብርተኞቹን እየደገፈ ይሆናል ብለው እንዲያስቡ አድርጓል። አሸባሪዎቹም ሃይ የሚላቸውና ላለፈው ወንጀላቸው ጠያቂ አለመኖር ወደ ላቀ የወንጅል ተግባር እንዲሰማሩ እየረዳቸው ይገኛል። ከዓመቱ መጠናቀቂያ በፊት የራሳቸውን ክልል የሚያውጁ ስለመሆናቸውም በድፍረትና በግልፅ እስከ መናገር ደርሰዋል።

በቀደመው መንግሥት ዘመን እኒህ ሁሉ የሽብርተኞቹ ወንጀሎች የማይታሰቡ ናቸው። በወለጋና ሶማሊያ ክልሎች ያሉትን አሸባሪዎች ለመደምሰስ የተንቀሳቀሰው መንግሥት ለምንድን ነው እነዚህን የነጠሩ አሸባሪዎች በዝምታና በለሆሳስ የሚያልፈው? መገናኛ ብዙሃንስ የአዋሳ ህዝብ በሲዳማ አሸባሪዎች እጅ ሲሰቃይ ዝምታቸው ከምን የመነጨ ነው? መንግሥት ዜጎቹን ከአሸባሪዎች ጥቃት የሚታደገውስ መቼ ነው?

የአዋሳ ህዝብ በመንግሥት ዝምታ የተሰላቸ መሆኑ መታወቅ ይኖርበታል። ህዝብ ንብረቱ እየወደመበትና እየተመዘበረ ታክስ ሊከፍል እንደማይችል መታወቅ አለበት። በየትኛውም ዓለም የሚገኝ መንግሥት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቹ በሽብርተኞች የቁም ስቅላቸውን እያዩ ከዳር ቆሞ አይመለከትም።

መንግሥት በአዋሳ ዜጎቹን ከአሸባሪዎች ጥቃት መጠበቅ ስለ ምን እንዳልቻለ ለህዝቡ በግልፅ መናገር ይኖርበታል። በየሁለት ቀኑ ወላጆች ልጆቻቸውን ከትምህርት ገበታ ላይ አውጥተው ሲሸሹ ለልጆቻቸው ምን ይንገሯቸው? መንግሥት ህዝቡን የመጠበቅ አቅም ከሌለው ምክንያቱን ይናገር። ህዝቡ ላም አለኝ በሰማይ በሆነ ቀቢፀ ተስፋ መኖር ሰልችቶታል።

 

ኤፕሪል 22/2019
ማስታወሻ፤ የእንግሊዝኛውን ፅሁፍ ያገነሁት ከታች ከሚገኘው አድራሻ ነው።
https://www.zehabesha.com/terrorism-in-awassa-and-the-silence-of-the-federal-government/

Filed in: Amharic