>
5:14 pm - Monday April 20, 3739

ም/ከንቲባው የባልደራስን የአቋም መግለጫ "አልቀበልም" አሉ!!!!  (ኤልያስ ገብሩ)

ም/ከንቲባው የባልደራስን የአቋም መግለጫ “አልቀበልም” አሉ!!!! 
ኤልያስ ገብሩ
በዛሬው ዕለት፣ መጋቢት 30 ቀን 2011 ዓ.ም፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማና የአዲስ አበባ ባለአደራ ምክር ቤት ሰብሳቢ እስክንድር ነጋ ጋር ተገናኝተው ተወያይተዋል፡፡ በውይይቱ ወቅት፣ እንደመነሻ ሃሳብ ሆኖ፣ በአዲስ አበባ ጉዳይ ልዩነቶች እንዳሉ፣ ልዩነቶች ግን በሰላማዊ መንገድ መፈታት እንዳለባቸው ተስማምተዋል፡፡
በቀጣይነትም፣ ወደ ዋናው አጀንዳ ለመግባት፣ መጋቢት 1 ቀን 2011 ዓ.ም በባልደራስ አዳራሽ የተሰበሰቡ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ያወጡትን የአቋም መግለጫ በፅሁፍ እንዲቀበሉ በእስክንድር በኩል ጥያቄ የቀረበ ሲሆን፣ አቶ ታከለ ጥያቄውን ለመቀበል ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ እስክንድርም ለአቶ ታከለ በሰጠው ምላሽ፣ የህዝቡን ጥያቄ እንዳልተቀበሉ ለህዝብ ይፋ እንደሚደረግ ገልፆላቸዋል፡፡
በአዲስ አበባ ጉዳይ ያሉትን ልዩነቶች በሰላማዊ መንገድ መፍታት እንዲያስችል፣ ህዝባዊ ስብሰባዎች ሊፈቀዱ እንደሚገባ በእስክንድር በኩል ሃሳብ ቀርቦም፤ አቶ ታከለ ኡማ  ሃሳቡን ሙሉ በሙሉ ተቀብለው ከከተማዋ የፀጥታ ኃላፊ ጋር በስልክ አገናኝተውታል፡፡ በዚህ መልክ ህዝባዊ ስብሰባዎች ያለምንም ችግር እንዲደረጉ ከከተማዋ ባለስልጣናት ጋር ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
በዚህም መሰረት፣ ከሚቀጥለው ቅዳሜና እሁድ ጀምሮ፣ በየክፍለ ከተሞች በሚጠሩ ህዝባዊ ስብሳባዎች በኩል  የአደረጃጀት ስራ የሚጀምር መሆኑን እንገልፃለን፡፡
የአዲስ አበባ ባለአደራ ምክር ቤት (ባልደራስ)   
 አዲስ አበባ
 መጋቢት 30/2011 ዓ.ም
Filed in: Amharic