>

ይድረስ ለኢትዮጵያ መንግስት እንደ አንድ ዜጋ እጠይቃለሁ !! (አርቲስትና አክቲቪስት ታማኝ በየነ)

ይድረስ ለኢትዮጵያ መንግስት
እንደ አንድ ዜጋ እጠይቃለሁ !!

አርቲስትና አክቲቪስት ታማኝ በየነ

እኔ በደረሰኝ መረጃ ከትናንት ጀምሮ በወሎ ከሚሴና በሽዋ አጣዬ በደረሰ ግጭት ንጹሃን ዜጎች እዬሞቱ ነው፡፡

ለመሆኑ ሰላም የነበር አካባቢ በአንዴ ወደ ጦርነት ቀጠና እንዴት ሊለወጥ ቻለ?

የእማራ ክልል መንግስት በእካባቢው የታጠቁ ሃይሎች ሲገቡና ሲወጡ አላየም ነበር?

የኦሮሚያ መንግስትስ ከራሱ ሃይል ውጭ የታጠቀ ሃይል ሲያይ ማን ነህ ብሎ አይጠይቅም ወይ?

ኦዴፓና አዴፓ በእርግጥ እየተነጋገራችሁ ነው የምትሰሩት? ከሆነስ የአንድ ንጹህ ዜጋ ህይዎት ከማለፉ በፊት ለምን ግጭቱን ተነጋግራችሁ አትፈቱትም ነበር?

የፌደራል መንግስት እንደ እኛ ውጭ እንዳለነው እኩል ነው ግጭቱን የሰማው?

በአጠቃላይ ለተፈጠረው ቀውስ ከፌደራል መንግስቱና ከሁለቱ የክልል መንግስታት ውጭ በዚህ ጉዳይ ተጠያቂ የለም

በአጠቃላይ በየቦታው የሚታዩት ግጭቶች ነገን አስፈሪ እያደረጉት ነው፡፡ መንግስት ሁሉንም በእኩል አይን አይቶ በጥፋተኛው ላይ የማያዳግም እርምጃ ካልወሰደ ወደ ፈራነው እልቂት እንደምንገባ ለመናገር ትንቢት ተናጋሪ መሆን አያስፈልግም፡፡

ገና በጠዋት የአብዮታዊ ዲሞክራሲ የዘረ ፖለቲካ መሰረት ሲጣል አይበጀንም ብዬ አደባባይ የወጣሁት የዘረ ፖለቲካ መጨረሻው ዛሬ የምናየው በእጅጉ በከፋ ሁኔታ ነገ የምንጋፈጠው መሆኑን በመረዳት ነበር።

ዛሬ የዘር ፖለቲካ በድርስ ዘዋሪ አፍላ ጎረምሳዎችም እድሜ በተጫናቸው በችግሩ አምጪ አዛውንቶችም በአስፈሪ ሁኔታ እየተራገበ እሳቱ ደግሞ በየቀኑ አገር የቆመችበትን ምሶሶ እየለበለበ፤ የዜጎችን ነፍስ እየቀጠፈ ነው።

አስገራሚው ነገር በተመሳሳይ ወቅት ያልተማርንበት የሩዋንዳ የዘር ፍጅት መታሰቢያ ለ25ኛ ጊዜ በዓለም መድረክ እየታወሰ ነው። እኛ እንደሌሎቹ ካለፈው መማሩ ቢሳነን ዛሬ እየሆነ ባለው በራሳችን ውድቀት ለመማር እንኳን ዝግጁ የሆንን አንመስልም።

እርግጥ ነው መንግስት በቅርቡ የአገራችን መሰረታዊ ችግር የምንከተለው የብሔር ፖለቲካ ነው ሲል የደረሰበትን ድምዳሜ በግልፅ ማሳወቁ የተስፋ ምልክት ሆኖ ሊታይ ይችላል።

ይህ በራሱ ግን ከዛሬው እልቂት የሚታደገን አይደለምና የፌደራል መንግስቱም ሆነ የሁለቱ ክልል መንግስታት በአፋጣኝ ይህን ሁኔታ ቀልብሰው ከዚህ በላይ ሌላ ጉዳት እንዳይደርስ እንዲከላከሉ ይህንን ሰይጣናዊ ተግባር የሚፈፅሙ አካላትንም በህግ ተጠያቂ እንዲያደርግ እንደ አንድ ዜጋ ለመጠየቅ እወዳለህ።

Filed in: Amharic