ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ
“ሰዎች የሀይማኖት መፅሐፍን ፍች እየተነጋገሩ በሚያሻሽሉበት 21ኛው ክፍለ ዘመን ላይ እየኖርን ትናንት ብልጭ ያለልንን ሀሳብና ገብቶንም ሳይገባንም መመርያ ያደረግነውን ርዕዮተ ዓለም ለድርድር አናቀርብም ብለን የሚደራደሩንን አስረን የምናሰቃየው ገለን የምንጥለው ሰብአዊነትን መሰረት ባደረገ ጠንካራ ምክንያታዊነት ላይ የተሰመረተ ስነ ምግባር ስለሌለን ነው።
ደርግ በአብዮቱና በሰፊው ሕዝብ ጥቅም አይደራደርም ነበር። ሕወሓት /ኢህአዴግ በመሬት ባለቤትና በአብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመሩ ላይ አይደራደርም ነበር። የዛሬዎቹ መሪዎችና የፖለቲካ ኢሊቶችም በፌደራሊዝም ላይ እንደማይደራደሩ ይናገራሉ። አለመወያየትና አለመደራደር ሰብአዊ አይደለም። መወያየትና መደራደር ሰብአዊ ተፈጥሮ ነው። ሰዎች እስካሉ ይኖራል። ሰዎች ሀሳብን የሚያዳብሩት ወይም የሚቀይሩት በድርድር ወይም በውይይት ነው።
“አልደራደርም” የሚለው ቃል ውስጥ የሌላውን ቃል መቀበል ቀርቶ ማዳመጥ አልፈልግም የሚል ትምክህትና ንቀት አለ። አልደራደርም የሚለው ቃል ውስጥ የዜጎችን በሀገራቸው የመሳተፍ መብት የማይቀበል የአምባገነንነት ቡቃያ አለ። ይህን ይዘን ፖለቲካዊ ዲስኮርሳችን ወደ ዲሞክራሲ ሊያደርሰን አይችልም። ይህ መሞረድ አለበት። ሞረዱ ደግሞ ስነምግባራዊ ውይይት ነው።
ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ