>
5:13 pm - Monday April 18, 1825

ከምታደርገው ይልቅ የምትናገረው ብዙ ርቀት ይጓዛል (ይኄይስ አእምሮ)

ከምታደርገው ይልቅ የምትናገረው ብዙ ርቀት ይጓዛል

ይኄይስ አእምሮ 

የሀገራችን ወቅታዊ ሁኔታ አላስቆም አላስተኛ ብሏል፡፡ ይህችን ዐረፍተ ነገር ስጽፍ ከሌሊቱ 7፡31 ይላል፡፡ ከእኩለ ሌሊት 1፡30 ገደማ አልፏል፡፡ በልጻፍ አልጻፍ ክርክር ከግማሽ ሰዓት በላይ ከራሴው ጋር ተሟግቻለሁ – “መጻፉ ብቻውን ምን ዋጋ አለው?” በሚል፡፡ ግን ይሁን ግዴለም – ከዕንቅልፋችን ስንባንን ለ“እንዲህም ተብሎ ነበር” የታሪክ ማኅደራችን አንድ ነቁጥ ግብኣት ነው፡፡
ከትምህርቱ ዓለም ወደ ሥራው ዓለም እየገባሁ ሳለ ያየሁት አንድ ፊልም መቼም አይረሳኝም፡፡
ታሪኩ ባጭሩ እንዲህ ነበር፡፡ የአሜሪካው ፕሬዝደንት በአሜሪካ ጠላቶች ይጠለፋል፡፡ ለማስለቀቅም ድርድር ይጀመራል፡፡ አሜሪካ የተጠዬቀችው ጥያቄ ግን ከባድ ይሆንና የድርድሩ ስኬት ከዕይታ ውጭ ይሆናል፡፡ ጠላፊዎቹ የተጠለፈው ፕሬዝደንት በሚገኝበት ሽፍን መኪና ውስጥ የሰዓት ቦምብ አስቀምጠዋል፡፡ ሰዓቱ አልቆ ስብርባሪ ሴከንዶች ብቻ ቀርተዋል፡፡ በዋናው ፕሬዝደንት ምትክ የሀገሪቱ ፕሬዝደንት ሆኖ የሚያገለግለው ምክትሉ ነበር፡፡ ይህ ሰው ድርድሩ እንዲሳካ በጣም ይጥር ነበር፡፡ ሚስቱ ግን የድርድሩን ስኬታማነት ስለማትፈልግ በድርድሩ ዳተኛ እንዲሆን ትመክረዋለች፡፡ ምክንያቱም ባለቤቷ ፕሬዝደንት እንዲሆንላት ትፈልግ ነበርና፡፡ ያኔ በቤታቸው ውስጥ ሌላ ቅራኔ ይፈጠራል፡፡ ትዝ የሚለኝን ጭቅጭቅ በራሳቸው ቋንቋ እንደነገሩ ላስታውሳችሁ፡፡
ሚስት በጣም ተናዳ – Don’t you want to be the President of the US?
ባል በተረጋጋ ሁኔታ – Why not? I would like to be a President through out my life, but not in this way. (አጽንዖት የተጨመረ)
ትርጉሙ – ሚስት ለባል “የአሜሪካን ፕሬዝደንት መሆን አትፈልግምን?” ስትለው ባል ደግሞ “ለምን አልፈልግ? ዕድሜ ልኬን ፕሬዝደንት ብሆን ደስ ይለኛል፤ነገር ግን በዚህ መንገድ አይደለም፡፡”
እውነትንና ስሜትን የሚያስታርቅ ግሩም አባባል ነው፡፡ ዓለማችንም ሆነች ኢትዮጵያችን ያጣችው መልካም ስብዕና ይህንን መሰሉን ነው፡፡
ሮበርት ኤፍ ኬኔዲ (Robert F. Kennedy) እንደተናገራት ተጠቅሶ ከፌስ ቡክ መንደር ተለጥፋ ያገኘኋትን አንዲት ጥቅስ ቢጤ ደግሞ ላስታውሳችሁ፡-

“What is objectionable, what is dangerous about extremists is not that they are extremists, but that they are intolerant. The evil is not what they say about their cause, but what they say about their opponents [perhaps ‘foes’ in our case, just to maintain a rhythm with ‘cause’?].”

“አክራሪዎች ሊወገዙና በአደገኛነትም ሊፈረጁ የሚገባቸው አክራሪ በመሆናቸው ሳይሆን ከፈሳቸው የተጣሉ ጠብ ያለሽ በዳቦ በመሆናቸው ነው፡፡ ስለመነሻ ዓላማቸው የሚናገሩት በራሱ ክፋት የለውም፡፡ ነገር ግን ስለሚቃወሟቸው ወገኖች የሚናገሩት መርዛማ ንግግር ፈጽሞ የሚያቀባብር አለመሆኑ ነው ዋና መጥፎ ነገራቸው፡፡”

ብሂላችን “ከአፍ ከወጣ አፋፍ ነው” ይላል፡፡ አፍ ወይ አንደበት የሚሰብረውን አካል ወይም ጂስም ምንም ዓይነት ጥበብና ዕውቀት ያለው ወጌሻ የሚጠግነው አይመስለኝም፡፡ እመለስታበለሁ፡፡
ስለ አየር መንገዳችን ቀደም ባለ ወቅት ባወጣሁት አንድ አጭር መጣጥፍ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዐይን ባወጣ ሁኔታ ከላይ እስከታች በይሉኝታ-ቢስ ወያኔ ትግሬዎች መያዙን ለሥልጠናና ምረቃ የበቁ 27 ይሁኑ 25 የትግሬ ሆስተሶችን ምሣሌ በማድረግ መግለጼ ይታወሳል፡፡ አሁን በአዲሱ ለውጥ ማግሥት ደግሞ ያው ተመሳሳይ ታሪክ መልኩን ቀይሮ መከሰቱን እየሰማን ነው፡፡ ያንን አስቀያሚና አሣፋሪ ታሪካችንን የተናገረ አንደበት አሁን ሌላ ወገን የሚፈጥረውን ተመሳሳይ ችግር ለመናገርና ለመኮነን ካፈረ ችግር አለ ማለት ነውና ሲሞቅ በማንኪያ እንደሚሉት ሊሆን ነው፡፡
የኢትዮጵያ ሲቪል አቪየሽን ላሉት ክፍት ቦታዎች 350 ሠራተኞች ተመልምለው እንዲሰለጥኑና እንዲቀጠሩ የሚመለከተውን ክፍል ያዛል አሉ – ከሁነኛ ምንጮች የሰማሁት ነው፤ በሚዲያም ተገልፆ ከሆነ አላውቅም፡፡ ትዕዛዙ የደረሰው ክፍል በአጭር ጊዜ ውስጥ ምልመላውን አካሂዶ የ350 ሰዎችን ስም ዝርዝር ያቀርባል – የሰውነት ደረጃችሁን ያልሳታችሁ ጤናማ ወገኖቼ እንዳትደነግጡ እነዚያ ሰዎች ሁሉም ኦሮሞ ናቸው፡፡ የበላይ ማኔጅመንቱ ውስጥ የሰው ሽታ ያላቸው ጥቂት ርዝራዥ አሳቢ ሰዎች ኖረው መሆን አለበት “አይ፣ በዚህ የለውጥ ጊዜ ይህማ እንዴት ሊሆን ይችላል? አየር መንገዱ እኮ የሁሉም ኢትዮጵያውያን ነው፤ ከሁሉም ዜጎች በአዲስ መልክ ምልመላው ይካሄድና ይምጣ” ተብሎ ይመለሳል፡፡ እንዲያም ሆኖ ተሻሽሎ በቀረበው ዝርዝርም ከ350ው ከ170 በላይ የሚሆኑት ኦሮሞዎች ናቸው፡፡ የገባንበትን አረንቋ እግዚአብሔር ያሳያችሁ፡፡ ወያኔዎች ጥቁር ውሻ ይውለዱ፡፡
እንደወረዱት ወርጄ ይህን መሳይ አሣፋሪ ትርክት ለመናገር የተገደድኩት አካሄዳችን በጊዜ ካልታረመ የሚያመጣው መዘዝ ለማንም እንደማይበጅ ለመግለጽ ነው፡፡ እንጂ በትክክለኛው መሥፈርት ምልመላ ተካሂዶ ሁሉም ኮንሶና ጀምጀም ወይ ጠምባሮና ደራሳ ቢሆኑ ጉዳየ አይደለም፡፡ ይሄኛው ግን ብቁ ሆኖ የመገኘት ጉዳይ ሳይሆን “ጊዜያችን አሁን ነው በደምብ እንጠቀምበት” ከሚል ወያኔ ከተከለው የዘረኝነት ዛፍ ላይ ያቆጠቆጠ በመሆኑ አምርረን ልንቃወመው ይገባል፡፡ ወያኔ የበላውን ዕቁብ በድጋሚ ለመብላት መሞከር ወያኔ ከሚከፍለው ዕዳ በበለጠ ለመክፈል መዘጋጀትን ይጠይቃል፡፡ አንዱ ከሌላው ካልተማረ የሰውነት መለኪያው ሚዛኑ ጠፍቷል ማለት ነውና ጉዳዩ እጅግ አሳሳቢ ነው፡፡
በአንድ የመንግሥት መሥሪያ ቤት ደግሞ እንዲህ ሆነ አሉኝ – የሚሰማው ታሪክ ብዙ ነው መቼም፡፡ ለተወሰኑ የኃላፊነት ቦታዎች የውስጥ ውድድር ይደረጋል፡፡ ያለፉት ሰዎች ሲፈተሹ አብዛኞቹ ከ“ተረገመው” አንድ ነገድ የወጡ ናቸው፡፡ በየቦታው ያሉት አለቆችና ወሳኝ የሥራ ቦታዎች በወቅቱ ተረኞች የተያዙ እንደመሆናቸው ይህ ድልድል ይቆይ ይባላል፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላም ያ የውድድሩ ውጤት ይሰረዝና በበላይ ትዕዛዝ ከተለመደው አሠራር ውጪ አዲስ ድልድል ይወጣል፡፡ ተሹዋሚዎቹ ሲታዩ ሁሉም ኦሮሞ ናቸው፡፡ ፈርዶበት ያ የሚጠላ ነገድ ስሞቹን ለኦሮሞውም ለትግሬውም በማዋሱ ምድረ ሐጎስና ገመቹ በአምበርብርና በስንሻው የማይገዙና የማይከለከሉ ስሞች አማራ እንደሆነ ለማስመሰል ቢሞክርም እውነትን ለጊዜው መሸፈን እንጂ ቀብሮ ማስቀረት ባለመቻሉ በአማራ ስም የገቡት ሁሉ ሲፈተሹ ኦሮሞ መሆናቸው ተረጋገጠ – የሚገርመው በተጋሩ ዘመን ቅን አሳቢና ሀገር ወዳድ ትግሬዎች ወደ ዳር ይገፉ እንደነበር ሁሉ አሁንም የሚሾሙት አማራ ጠልና አፈንጋጭ ኦሮሞዎች መሆናቸው የታሪክን ተደጋግሞ መከሰት በጉልኅ ያሳያል፡፡ ባልጠፋ የተማረና ተራማጅ አስተሳሰብ ያለው ኦሮሞ አሁን አሁን የሚሾሙት ከቀን ጅቦቹ የማይተናነሱ ሆዳሞችና አጋሰሶች ናቸው – ምናልባትም ወንጀለኞችም ጭምር፡፡ በ83 ዓ.ም 1ኛ ክፍል የነበረ፣ በነዚህ አጭር ዓመታት ውስጥ የአዲስ አበባ ዙሪያ ከተሞችን ግጦ እንደበላ የሚነገርለት፣ ለወንድሙ ሠርግ መኪና ይሁን ቪላ ቤት ወይንም ሁለቱንም በስጦታ መልክ በአደባባይ ያበረከተ… ወጣት የኦሮሞ ባለሥልጣን ማየት የቻልነው የዴሞክራሲ ጮራ በፈነጠቀልን ማግሥት ነው፡፡ ይሄ “‹ከነሱ መጥፎ› ‹የኛ መጥፎ› ይሻላል” የሚለው ሸውራራ አካሄድ መቼ ይሆን የሚቀረው? በፍትህና ርትዕ ማላገጥ ታሪክ የሚሆንበት ጊዜ ናፈቀኝ፡፡
ከፍ ሲል እንዳልኩት ኦሮሞነታቸው በራሱ ችግር ሆኖ ሳይሆን ብቁ የሆኑ ተወዳዳሪዎችን በጎሣ መሥፈርት በማግለል ብቁ ያልሆኑ የራስ የሚባሉ ዜጎችን መቅጠር ለሥራውም ሆነ ለሀገራችን ዕድገትና የወደፊት ዕጣ ፋንታ አደጋ ያለው በመሆኑ ነው፡፡ ኢትዮጵያም ሆነች ኦሮሞነት በአሁኑ ወቅት ልክ ከአንድ ዓመት በፊት በተጋሩ ላይ የነበረውንና አሁንም ድረስ ዕዳው ተወራርዶ ሊያልቅ ያልቻለውን ከባድ የታሪክ ፈተና በመጋፈጥ ላይ ናቸው፡፡ “ፈተናውን በድል ይወጡታል ወይንስ አይወጡትም?” የሚለውን ምላሽ ለማወቅ በግድ ሌላ 27 ዓመት የመከራና የስቃይ ጉዞ የሚያስፈልገን አይመስለኝም፡፡ ያለፉት 27 የሲዖል ዓመታት በቂ ትምህርትና ተሞክሮ ስለሰጡን ከአሁን በኋላ የሚኖረው ትግል የትግል ሥልትን በመቀየስና አዋጩን በመምረጥ እንጂ ሁሉም በነቃበት በዚህ የቴክኖሎጂ ዘመን ወያኔያዊ ያረጀ ያፈጀ ብልጣብልጥነት ብዙ የሚያስኬድ አይመስለኝም፡፡
እመለስበታለሁ ወዳልኩት ጅምር ሃሳብ ተመለስኩ፡፡ ጊዜው የኛ ነው የሚሉ ወገኖች ወያኔን ሆነውና መስለው ትያትሩን በከፍተኛ ፍጥነት እየተወኑ ይገኛሉ፡፡ ይሁን፡፡ እንደነሱ ሆኖ ማሰብ ስለማይቻል አቅል እንዲሰጣቸው ከመጸለይ ውጪ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ ቢችሉ ወያኔ የተጓዘበትና የከሰረበት መንገድ ለማንም እንደማያዋጣ ተረድተው አሁን ከመሸ በኋላም ቢሆን ከሰይጣናዊ ድርጊቶቻቸው ቢቆጠቡ መልካም በሆነ ነበር፡፡ በተለይ አማራን እያሰሱ ማጥቃት ቢያቆሙ የመጀመሪያ ተጠቃሚዎቹ እነሱው ናቸው፡፡ አማራ ብዙ ግፍ የደረሰበት ሕዝብ ነው – በወያኔና ከዚያም በፊት፡፡ “ቀን ጥሎታልና ምንም አያመጣም” ማለት ግብዝነት ነው፡፡ እርግጥ ነው አማራ ምንም ላያመጣ ይችላል፡፡ነገር ግን መታወቅ ያለበት ትልቅ ቁም ነገር አለ፡፡ እርሱም አማራ የትልቅ ኒኩሌር መሣሪያ ባለቤት መሆኑ ነው፡፡ ያም ኒኩሌር ዕንባው ነው፡፡ የአማራ ዕንባ በተለይ ላለፉት 30 እና 40 ዓመታት ያለማቋረጥ ሽቅብ ይፈስ ነበር – ዕንባ ወደላይ እንጂ ወደታች እንደማይፈስ በዚህ አጋጣሚ ልብ እንበል፡፡ እናም የምሥኪኑ አማራ ዕንባና ደም ያለገደብ ፈሷል፤ ጸሎቱም በየጊዜው ወደ ጽርሃ አርያም ተልኳል፡፡ የጊዜ ጉዳይ እንጂ የመልሱ መምጣት አያጠራጥርም፡፡ የትናንቱም ሆነ የትናንት ወዲያው ታሪካችን የሚመሰክረውም ይህንኑ እውነት ነው፡፡ ስለሆነም ጊዜ አገኘሁ ብሎ የሚደነፋና የሚታበይ ሁሉ ጉልበቱን ሳይሆን አእምሮውን፣ ስሜቱን ሳይሆን ልቦናውን ቢያዳምጥ ለርሱ ይሻለዋል፡፡ የወጣች ፀሐይ ትጠልቃለች፤ የጠለቀች ፀሐይ ትወጣለች፡፡ እየመሰለን እንጂ አዲስ ነገር የለም፡፡
ስለሆነም ውድ ኦሮሞ ወንድሞቼና እህቶቼ ሆይ! ለነዚያ እል እንደነበረው ለናንተም እላለሁ፡፡
ከሁሉም በፊት ጥጋብንና ዕብሪትን ለመቆጣጠር ሞክሩ፡፡ በተለይ የዕብሪት አነጋገራችሁን ልጓም አብጁለት፡፡ መጥፎ ንግግር ድንበር አይገድበውም፡፡ አጉል ቃል ዘመን ተሻጋሪ ነው፡፡ አሁን እንኳን ማን ምን እንዳለ ብዙ እዬሰማን ነው፡፡ በተግባር እያዘዛችሁ እየናዘዛችሁበት ባለው የጋራ የሀገር ሀብት እኛ ምንም አላልንም፤ አንልምም፡፡ ብዙዎች ኢትዮጵያውያን “ፍትህ ይስፈን፤ ብዙ ወጣቶች የተሰውለት ለውጥ ግቡን እንዲመታ ሁላችንንም እኩል የምታቅፍ የጋራ ሀገር እንፍጠር” ከማለት ውጪ ያን ወይ ይህን ነገድ በተለዬ ለመጥቀም ወይም ለመጉዳት ያለመ ዕቅድ የለንም፡፡ በወያኔና ከዚያም በፊት በደርግ ክፉኛ የተቀጠቀጥን በመሆናችን ለጊዜው ጠበንጃን ማየት አንወድ ይሆናል፡፡ ይሁንና ጠበንጃን የሚያስንቅ ልባዊ ጸሎትና በተፈራራቂ ግፈኞች የሚፈስ ዕንባ ትልቅ የነፃነት አርበኞቻችን እንደሆኑ ዕወቁልን፡፡ እናም እናንተም እኛም ለከፋ ጉዳት ከመዳረጋችን በፊት ወደ ኅሊናችሁ ተመለሱ፡፡
የቤት ፈረሳውና በአዲስ አበባ ውስጥና ዳርና ዳር ከአግባብ ውጪ ሌሎችን በማፈናቀል በሚገኝ ቦታ ላይ ኦሮሞን ማስፈሩ እንደቀጠለ እንሰማለን – ወንድሞቻችን መጠለያ ማግኘታቸው ያስደስተናል፤ ይገባቸዋልም፡፡ ነገር ግን ባልጠፋ መሬት አንዱን ነቅሎ ሌላውን መትከል የዞረ ድምሩን የማትችሉት መሆኑን የምገልጽላችሁ ወደፊት ምን ሊከሰት እንደሚችል በሦስተኛው ዐይኔ የተረዳሁትን አስቀያሚ ትርዒት በመጠቆም ጭምር ነው፡፡ ሞትንና ዕልቂትን የሚጋብዝ ያላዋቂ ሣሚ ዓይነት ዘረመላዊ የንቅለ ተከላ ህክምና እያካሄዳችሁ መሆናችሁን ሁሉም በድንጋጤ ፈዝዞ እየተመለከታችሁ ነውና ከገባችሁበት ሁለመናን የሚያጥበረብር የቅዠት ዓለም በቶሎ ውጡ – እኔ ላጥፋችሁ የያዛችሁት የይሁዳ መንገድ ክርስቶስን በ30 አላድ እንደሸጠው እንደዚያ ከሃዲ ሰውዬ ራሳችሁን ለመስቀል እንኳን ዕድል የማታገኙበት ሁኔታ ይፈጠራል፡፡ የዱባ ጥጋብ ምን ሊያስከትል እንደሚችል ጠንቅቀን የምናውቅ ዜጎች ይቺ የኦሮሞ አክቲቪስቶችና የፖለቲካ ልሂቃን ተብዬዎች አሁን የሚያቀነቅኗት ሀገር አፍራሽ ዜማ ብትውል የማታድር፣ብታድር የማትውል መሆኗን ሁሉም ሊገነዘበው ይገባል፡፡
በሲኤም ሲ አካባቢ በሚገኘው መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ግድም ከገበሬዎች መሬት ገዝተው በገደላ ገደሉ ጥጋ ጥግ ጎጆ በመቀለስ የሚኖሩ ዜጎች ነበሩ፡፡ አሁንም ትናንትም ቤታቸው እየተናደ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ጉድባውን ሻገር ብለው ጫካው ውስጥ ሸራ ዘርግተው ልጆቻቸውን ከብርድና ከፀሐይ ሊታደጉ ሲሉ ልዩ ኃይልና ፌዴራል ፖሊስ መጥቶ ያባርራቸዋል፡፡ “የት እንግባ?” ብለው ሲጠይቁ “ያፈረሱባችሁን ጠይቁ” ይሏቸዋል፡፡ ሄደው ያፈረሱባቸውን ሲጠይቁ የተሰጣቸው ግፈኛ መልስ “ዞር በሉ! ኦሮምያን ስትግጡ ከረማችሁ፡፡ ካሣ ሳንጠይቅ ስላስነሳናችሁ ነው እንዲህ የምትጨማለቁት?” የሚል ነው፡፡ ሌላው ነብራራም “ ያለህጋዊ ፈቃድ ቤት በመሥራታችሁ ከ7 እስከ 15 ዓመት ትታሰሩ ነበር፤ ያን አውቀን ትተነው ነው፡፡” የሚል ቀልድ እንደቀለደም ሰምተናል፡፡ ብዙዎች ብዙ እያሉ ነው፡፡
አዲስ አበባንም ሆነ ሌሎች አካባቢዎችን ማን ግጦ እንደበላ ጊዜ ራሱ መልሱን በቅርብ ጊዜ ስለሚሰጠን በዚያ አንከራከርም፡፡ አማራው ግን ከመሀል ከተማ ከሀብት ከንብረቱና ከተወለደበት ቀየው በባለጊዜዎች እየተፈናቀለ ወደ አዲስ አበባ ዳርና ዳር እየወጣ – ሊያውም ያንንም የቻለ – በዛኒጋባ ለመኖር የተገደደ ድሃ ሕዝብ ነው፡፡ “ጌታውን ቢፈሩ ገበር ገበሩን” ወይንም “ዐይጥ በበላ ዳዋ ተመታ” አንዲሉ ሆኖ ግን ባለ ሃያና ሰላሳ ፎቅ የገተረና በሽዎች ካሬ ሜትሮች የሚገመቱ ግቢዎች ውስጥ ትላልቅ ህንጻዎችንና መኖሪያ ቤቶችን የገነባ ህገ ወጥና ቀማኛ ዜጋ እንደልቡ በሚያሽቃንጥባት ከተማና ሀገር ይህ በየፈፋውና በየሸንተረሩ ጎጆ እየቀለሰ የሚኖር ሕዝብ በምን አበሳው እንዲህ እንደሚሰቃይ አንድዬ ብቻ ነው የሚያውቀው፡፡ ለሁሉም ጥያቄዎቻችን መልስ ከርሱ እንጠብቃለን፡፡ ያኔ ይለያል፡፡
እንስሳት እንኳን በተፈጠሩባት ምድር በነፃነት የመኖር መብት አላቸው፡፡ ምድር የምድራውያን ሁሉ እንጂ ጉልበትና ገንዘብ ያለው ብቻ እንዲገለገልባት ታስባ በባለሙያ እጅ የተሠራች የዳንቴል ሹራብ አይደለችም፡፡ እባብ ጉድጓድ አለው፤ አእዋፍ ጎጆ አላቸው፡፡ ጅቦችና ዝንጀሮዎችም ዋሻ አላቸው፡፡ ጉሬዛዎችና ጦጣዎች ማረፊያ ዛፍ አላቸው፡፡ ምድር የእግዜር ፍጡር እንጂ ማንም ሰው የጠፈጠፋት ጎታ ወይ ጉስጉሻም አይደለችም፡፡ መሬት ሰውን ስትበላው ሰው ግን መሬትን አይበላትም፡፡ ሰዎች በመሬት ባለቤትነት መጣላታቸው ከንቱነት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ ሰፊ ናት፡፡ ለሁሉም ትበቃለች፡፡ ያጣነው ጠባይ ነው፡፡ በ“የኔ ነው” ልክፍት እየተሰቃየን ነው፡፡ በመሠረቱ ራቁታችንን እንደመጣን የምንሄደውም ራቁታችንንና ባዶ እጃችንን ነው፡፡ ያኔ “የኔ ነው፤ የኛ ነው” የለም፤ ሁሉም ይቀራል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ በዚህች የስደት ዓለም የምንኮራበት አንድም ነገር የለም፤ ሊኖርም አይችልም፡፡ ጧት ወጥተህ ማታ በሰላምና በሕይወት ወደ ቤትህ ለመግባትህ ከሰማይም ሆነ ከምድር ምንም ዓይነት ዋስትና በሌለህ ሁኔታ ውስጥ እየኖርክ አገርን በሚያህል ነገር “የኔ ነው፤ ያንተ ነው” በሚል ዘመን አመጣሽ ፈሊጥ መቆራቆስ የጤና አይደለም፡፡ ሌላው ሁሉ ይቅርና የኔ ነው የምትለው ልጅህ ራሱ እንኳን ያንተ አይደለም – የኔ ናቸው የምንላቸው ብዙ ነገሮች የኛ አይደሉም፡፡ ብዙ ሞኝነት ይስተዋላል፡፡ ይልቁናስ ከዚህ በከፋ ሳንቆሳሰል በቶሎ እንመለስ፡፡ ለዚህም ፈጣሪያችን ፊቱን ወደኛ ይመልስልን፡፡ (ንጋት 11፡15)

ይኄይስ አእምሮ  yiheyisaemro mail.com)

Filed in: Amharic