>
5:13 pm - Thursday April 19, 0627

አዴፓበአዲስ አበባ የባለቤትነት ጉዳይ ላይ ጠንካራ አቋም ይዟል!!!

አዴፓበአዲስ አበባ የባለቤትነት ጉዳይ ላይ ጠንካራ አቋም ይዟል!!!
ዘጋቢ፡- በለጠ ታረቀኝ- ከአዲስ አበባ
 
“አዲስ አበባ የነዋሪዎቿ እና የኢትዮጵያ መዲና እንጅ የማንም አይደለችም!!”
የአ.ዴ.ፓ ማ/ኮ/ አባል አቶ ምግባሩ ከበደ 
 
 ‹‹አዲስ አበባ የራሷ መዋቀር እና አስተዳደር ያላት የኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ከተማ እንጅ የማንም አይደለችም!!›› 
ምክትል ከንቲባ እና የንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ ኢንጅነር እንዳወቅ አብጤ 
ባሕር ዳር፡የካቲት 16/2011 ዓ.ም(አብመድ) አዲስ አበባ የነዋሪዎቿ እንድትሆን እና አግላይ አመለካከቶች እንዲወገዱ በትኩረት እንደሚሠራ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) አስታውቋል፡፡
ድርጅቱ በአዲስ አበባ ከሚገኙ የአዴፓ አመራሮች ጋር ተወያይቷል፡፡ ዉይይቱን የመሩት የአዴፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ምግባሩ ከበደ ለአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት እንዳሉት አዲስ አበባ የነዋሪዎቿ እና የኢትዮጵያ መዲና እንጅ የማንም አይደለችም፡፡
አጀንዳውም ለዉጡን የማይደግፉ ኃይሎች የሚጠነስሱት የፖለቲካ ሤራ መሆኑን ነው የተናገሩት፡፡ ‹‹ችግር የሚፈጥሩ ግለሰቦች ወይም አመራሮች ካሉም በማጣራት እና ከሚመለከተዉ አካል ጋር በመሆን ጉዳዩ ይፈታል›› ብለዋል አቶ ምግባሩ፡፡ በአዲስ አበባ ባለቤትነት ጉዳይ አዴፓ አቋሙ ጠንካራ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ እና የንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ ኢንጅነር እንዳወቅ አብጤ በበኩላቸዉ ‹‹አዲስ አበባ የራሷ መዋቀር እና አስተዳደር ያላት የኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ከተማ እንጅ የማንም አይደለችም›› ብለዋል፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ ችግር ካለም በዉይይት እንደሚፈታና ችግር ፈጣሪዎችም እንደሚጠየቁ አረጋግጠዋል፡፡ በአዲስ አበባ የሚኖሩ የአዴፓ አመራሮችም አዲስ አበባ የሚኖረዉ የአማራ ሕዝብ መብትና ጥቅም እንዲከበር ጠንክረዉ እንደሚሠሩ ተናግረዋል፡፡
ምንጭ:- አማራ መገናኛ ብዙሀን
Filed in: Amharic