>

‹ሉሲ የሰላምና የፍቅር ጉዞ›› - ለቋሚ የጭካኔና ግፍ አዋጅ በድን አጽም የሰላምና የፍቅር አማላጅ!!! (ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ)

‹ሉሲ የሰላምና የፍቅር ጉዞ›› – ለቋሚ የጭካኔና ግፍ አዋጅ በድን አጽም የሰላምና የፍቅር አማላጅ!!!
    ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ
*  ለውጡ ያለ ጥያቄ የምንቀበለው ሀይማኖት አይደለም ፤ ይህን የሚገነዘብ የለውጥ መሪ ፣ ለውጡን ለማምጣት ከፈሰሰው የሰማእታት ደም ጋር በለውጡ ሳቢያ የሚፈስ የተበደሉ ዜጎች እንባ እንዲቀላቀል መፍቅድ የለበትም!
ግልብ አእምሮ ደርዝ ያለው፣ እየተቀናጀ የሚጎለብት ተግባር ሊከውን አይችልም፤ ይህ ደግሞ የአብዛኞቹ የለውጡ መሪዎች መለያ እየሆነ ነው፡፡
.
የለውጡ መሪዎች በህይወት ቆመው የዜጎችን ቤት እያፈረሱ፣ ህጻናትንና አዛውንቶችን ሜዳ በትነው ሰላምና ፍቅር እየነሱ፣ የበሰበሰ አጥንት ከሙዚየም አውጥተው ለሰላምና አፍቅር አማላጅነት ይልካሉ፡፡ በዚህ ዘመን ከዚህ በላይ ድንቁርና የወለደው ግልብነትና የህዝብ ንቀት የወለደው ምጸት አይገኝም፡፡
.
ከወራት በፊት የአዲስ አበባን የመንገድ ዳር ለንግድ ፈቅዶ፣ የእግረኛ መንገድ ሳይቀር በላስቲክ ዳስ ያዥጎረጎረ፣ የለውጥ መሪ ዛሬ የከተማ ውበት ጠፋ ብሎ የህዝብ ጎጆ ይደረምሳል፡፡ በፍርድ ቤት የእስር ማዘዣ የተቆረጠለትን ተጠርጣሪ ወደ ህግ አቅርቦ ህግን ያላስከበረ የለውጥ መሪ፣ ከህግ በላይ ማንም እንደሌለ ለማሳየት የዜጎችን መኖሪያ በቡልዶዘር ይንዳል፡፡
..
አዲስ አበባ ላይ ዜጎችን ፍቅርና ሰላም ነስተው ደም እያስለቀሱ፣ አጽም ለሰላምና ፍቅር ምልጃ አፋርና ሱማሌ ይልካሉ፡፡  ለነገሩ ካለማወቅ የተደረገ ቢሆንም፣ ቋሚ የጭካኔና ግፍ አዋጅ፣ በድን አጽም የሰላምና የፍቅር አማላጅ መሆናቸው ዘመኑን በሚገባ ይገልጸዋል፡፡
.
አንድ ነገር ግን መታወቅ አለበት፤  ለውጡ ያለ ጥያቄ የምንቀበለው ሀይማኖት አይደለም፤ መሪዎቹም እየበደሉ እንኳ ተንበርክከን የምንማጸናቸው መላእክት አይደሉም፡፡ ይህን የሚገነዘብ የለውጥ መሪ ፣ ለውጡን ለማምጣት ከፈሰሰው የሰማእታት ደም ጋር በለውጡ ሳቢያ የሚፈስ የተበደሉ ዜጎች እንባ እንዲቀላቀል መፍቅድ የለበትም፡፡ ያለዚያ ወደ ደምና እንባ ቅብብሎሽ ታሪካችን እንመለሳለን፡፡
Filed in: Amharic