>
5:13 pm - Tuesday April 19, 5650

ዶ/ር ብርሃኑ፤ ኦዲፒ እና አዴፓ (ሚኪ አምሃራ)

ዶ/ር ብርሃኑ፤ ኦዲፒ እና አዴፓ 
ሚኪ አምሃራ
————–
ዶ/ር ብርሃኑ ስትራቴጅካል እና ታክቲካል አጋር ብሎ የለያቸዉ አሉ፡፡ ይሄም ከ 1960ወቹ ጀምሮ ካቀነቀነዉ የፖለቲካ ርዕዮተ አለም ጋር በማወዳጀት ነዉ፡፡ በተማሪነቱ ዘመን አማራ ጨቋኝ እና የበላይ ብሎ ፈርጆ መነሳቱ ይታወቃል (ይህ የእርሱ ብቻ ችግር አይደለም ያዉ ፋሽን ነበር በዘመኑ)፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከህወሃት ጋር ባለመስማማቱ እና አማራን የሚያክል ህዝብ ጨቋኝ ነዉ እያልክ እየተናገርክ በሀገሪቱ ላይ ይሄ ነዉ የሚባል የፖለተካ ፓወር ማግኘት ከባድ መሆኑን የተገነዘበዉ እንዲሁም ባጠቃላይ ህወሃት ከልክ በላይ የጎሳ ፖለቲካን በመለጠጡ ስላልተመቸዉ የተወሰነ በማሻሻል እኩልነት የሰፈነባት ኢትዮጵያ ወደሚል ትርክት ቀይሮ መንገዱን አስተካክሏል፡፡ የአማራ የበላይነትን ማጥፋት የሚለዉ ነገር እኩልነት በሰፈነባት ኢትዮጵያ በሚል ዉስጥ ተጀቡኗል፡፡ አልፎ አልፎ በመደረክ ላይ ሳት ሲለዉ ወይም በግንቦት ሰባት የፕሮገራም ዶክመንቶች ላይ የአማራ እና የትግሬ የበላይነት (cultural dominance) challenge መደረግ እንዳለበት ይገልጻል፡፡ዶ/ር ብርሃኑ inherently የሰሜን/የአቢሲኒያ የፖለቲካን ይጠላል፡፡ ፍላጎቱ የሰሜኑን ፖለቲካ ማቀጨጭ ነዉ፡፡ በኢትዮጵያ አንድነት እንዲሁም ዲሞክራሲ ያምናል፡፡ ነገር ግን ከዉስጡ የሰሜን የፖለቲካ cultural dominance (ይሄን የሚያሳይ ተጨባጭ ሁኔታ ባይኖርም አለ ብሎ ስለሚያምን)  መሰበር አለበት ብሎ ያምናል፡፡ በዚህ ምክንያት ኦዲፒ/ኦህዴድ በሉት ኦነግ ወይም ኤርትሪያ፤ ደቡብ እና ሌሎቹ ስትራቴጅክ አጋሮቹ ናቸዉ፡፡ አማራ ታክቲካል አጋሩ ነዉ፡፡ ታክቲካል አጋሩ ስንል ኢትዮጵያዊነትን በማቀንቀን ድጋፍ ማግኘት ነገር ግን አሁን ያለችዉ ኢትዮጵያ በራሷ የአማራ/ አቢሲንያ ስሪት ናት እናም ይህ መክሰም አለበት ብሎ ያስባል፡፡ስለዚህም አማራ መረማመጃዉ እንጅ ሰዉየዉ በልቡ ያለዉ ነገር የአማራ ዶሚናንስ መቀነስን ነዉ፡፡
ዶ/ር ብርሀኑ በአንድነቱ ጎራ ዉስጥ ጠንካራ አማራ እንዳይኖር በደንብ ሰርቷል፡፡ እሱ ብቻ ሳይሆን ዶ/ር ብርሃኑ ከአማራ ዉጭ ከሆኑ ሰወች እና ፓርቲወች ጋር የቱንም ያህል ልዩነት ይኑረዉ አብሮ መስራት ይፈልጋል ሲሰራም ይታያል፡፡ ከአማራወቹ ጋር ግን አብሮ መስራት አይደለም ቢችል ማጥፋት አለያ ደግሞ ይህ ነዉ የሚባል አስቷጽኦ እንዳይኖቸዉ ያደርጋል፡፡ ሚዲያዉን በመጠቀም በዚህ ዙሪያ ላይ ዉጤታማ ስራ ሰርቷል፡፡ በራሱ ሚዲያ ዉስጥ ያሉ ደህና ደህና አማሮች ጋር እንኳን አይስማማም (ለምሳሌ ከእነ አበበ ገላዉ ጋር ምናላቸዉ ጋር)፡፡ ከላይ እንዳለኩት ከስትራቴጅክ አጋርህ ጋር እንጅ ከታክቲካል አጋርህ ጋር ጠለቅ ያለ ግንኙነት እንዲኖርህ አትፈልግም፡፡ ለምሳሌ ዶ/ር ብርሃኑ ከእነ መራራ፤ በየነ ጴጥሮስ፤ ሌንጮ እና ሌሎቹ ከአማራ ዉጭ የሆኑ በአንድነቱ ጎራ ያሉ ሰወች ጋር አብሮ የመስራት ምንም ችግር የለበትም፡፡ ከእነ ልደቱ፤ ኢንጅነር ሃይሉ፤ ኢንጅነር ይልቃል እናም ሌሎች ጠንካራ የአማራ ልሂቃን ጋር አተስማምቶ መስራት አይደለም በተለያየ ታክቲክ ከገቢያ ዉጭ ሲያደርጋቸዉ አይተናል፡፡ ከገቢያ ዉጭ እንዲያደርጋቸዉ ደግሞ ሌሎች ስትራቴጅክ አጋሮቹ ያግዙታል፡፡ አለያም ደግሞ እዚህ ግባ የማይባሉ ይህ ነዉ የሚባል ተጽእኖ የሌላቸዉ እና በአማራ ህዝብ ዘንድ እንደ አይከን የማይታዩ ጥቃቅን አማሮችን ባካባቢዉ ይሰበስባል፡፡ ኤርትራም ቢሆን የሰሜን ፖለቲካን ማክሰም አላማዋ ነዉ፡፡ በዚህም ምክንያት ዶ/ሩን ለረዥም አመታት አስተናግዳዋለች፡፡
ዶ/ር ብርሃኑ የብሄር ፖለቲካን አምርሮ አይጠላም፡፡ አሁንም እኩልነት ሲል ማን የበላይ ማን የበታች እንደሆነ አይታወቅም ነገር ግን በ60ዎቹ በተነሳበት ትርክት ስንሄድ ሌሎቹን ከአማራ ጋር እኩል የማድረግ አይነት ቅላጼ አለዉ (በእርሱ አገነዛዘብ እኩል አይደሉም ብሎ ስለሚያስብ)፡፡ ነገር ግን ብርሀኑ ፖለቲከኛ ነዉ፡፡ ፖለቲካ ደግሞ ፓወር ማግኘት ነዉ፡፡ ስለዚህም የወጣበትን ብሄር የሙጥኝ ቢል ወይም ደግሞ የብሄር ፖለቲካ ጥሩ ነዉ እናራምደዉ ካለ ጉራጌ ዉስጥ መግባቱ ነዉ፡፡ ጉራጌን ብቻ ይዞ የሀገር መሪ ይሄናል ወይ ብንል አይሆንም፡፡ ስለዚህም ወደደም ጠላም የአንድነት ፖለተካ ላይ ብቻ ሙጭጭ ማለት አለበት፡፡ ነገር ግን የመጨረሻ ግቡ ኢትዮጵያ ከብሄር ፖለቲካ ብትነጻም አዲሷ ኢትዮጵያ ከአቢሲንያዊ የፖለቲካ አስተዳደር ዘይቤ የራቀች ነገር ግን የፖለቲካ መልኳ ከሰሜኑ ወደ ደቡቡ ያመዘነ መሆን አለበት ብሎ ያስባል፡፡
ዶ/ር ብርሃኑ ከምእራባዉያኑ ጋር ባለዉ ጥሩ ግንኙነት የሰሜኑን ፖለቲካ ማጠልሸት ችሏል፡፡ ለምእራብዉያኑም ከሰሜኖች ይልቅ እርሱ ተቀባይነት እንዳለዉ አድርጎ አቅርቧል፡፡ እኔ በአማራም ከአማራ ዉጭ ባለዉም ህዝብ ዘንድ ተቀባይነት አለኝ ብሏል፡፡ ነገር ግን ከሰሜን የሚመጡ ፖለቲከኞች በደቡቡ ህዝብ ተቀባይነት እንደማይኖራቸዉ አስረድቷል፡፡ አማራን ከደርግ ጋር አያይዞ ተቀባይነት እንደሌለዉ ትግሬወቹን ደግሞ ህወሃቶች ባሳዩት ወንበዴነት እና አምባገነንነት ተጠቅሞ ለነጮቹ የሰሜን ፖለተካ ለሀገሪቱ አንድነት አደገኛ እንደሆነ ተርኳል፡፡ ከመለስ ሞት በኋላ ኢህአዴግ ድንገት ቢንገዳገድ ዶ/ር ብርሃኑ ቁጥር አንድ አማራጭ እንደሆነ ነጮቹ ወስነዋል፡፡ ለዚህም ነዉ የጉሬላ ጦርነት ዉስጥ የገባን ሰዉ የአዉሮፓ ፓርላማ ድረስ እየተጋበዘ ንግግር ሲያደርግ የነበረዉ፡፡ ይሄም የሰዉየዉን ሃሳብ የመስማት እሱን shape የማድረግ እና የማስተዋወቅ ስራ ሲሰሩ የቆዩት፡፡ ህወሃት አንድ ቀን እንደሚወድቅ ወይም እንደሚገፉት ያዉቃሉ፡፡ነገር ግን ከዉስጡ የተወሰኑ ሰወች አፈንግጠዉ በመዉጣት ኢህአዴግን ይታደጉታል የሚል እምነት አልነበራቸዉም፡፡ ዶ/ር አብይ ስርፕራይዝ አድርጓቸዋል፡፡
ዶ/ር ብርሃኑ እና ኦህዴድ
————–
ኦህዴድ የዶ/ር ብርሃኑ ስትራቴጅክ አጋር ነዉ፡፡ ኦህዴድ የሰሜኑን ወይም የአቢሲንያን (እነርሱ እንደሚሉት) ፖለቲካ ተገዳድሮ አሁን ፖለቲካዉን ወደ ደቡብ እያዞረዉ እንደሆነ ይሰማዋል ፡፡ ይህ ከዶ/ር ብርሃኑ ራእይ ጋር እጅግ ተመሳሳይ ነዉ፡፡ በዚህም ምክንያት ከኦሮሞ እንዲሁም ከደቡብ ፖለቲከኞች ጋር ጥንቃቄ በተሞላበት ሁኔታ (አማራ በማያኮርፉበት ሁኔታ) ፖለቲካዉን ያስኬዳል፡፡ ከሰሜኖች ጋር ላለዉ ነገር ብዙም አይጨነቅም፡፡ ምክንያቱም አንደኛ የትም እንደማይሄዱ ያዉቀዋል፡፡ ሁለተኛ ተጽእኗቸዉን መቀነስ አላማዉ ነዉ፡፡ ስለዚህም ከደቡብ በኩል ያለዉን አዲስ ሃይል ኦህዴድን ጨምሮ empower ማድረግ ነዉ ዋናዉ የሱ ስራ፡፡ አቢሲኒያወች ተግደርዳሪ እንዳይሆኑ እሱ እራሱን ብቸኛዉ የአንድነት ጎራዉ  መሪ አድርጎ በመሳል ሰሜነኞችንም የወከለ እንደሆነ አድርጎ በመሳል አለሳልሶ ይዟቸዋል፡፡ ለዚህም ነዉ አዲስ አበባ ላይ የኦሮሞ ፖለቲከኞች የፈለጉትን ነገር ሲያደርጉ አንድም ነገር ትንፍሽ የማይለዉ፡፡ የአቢሲንያ ፖለቲካ አዲስ ላይ መዳከም እንዳለበት በጽኑ ያምናል፡፡ በዚህ ምክንያት ነዉ ከጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ በሳምንት 3 ቀን የሚገኘዉ (አዲስ ፎርቹን እንደዘገበዉ)፤ ከአቶ ለማ ቢሮ በሳምንት ሁለት ቀን ይገኛል፤ ከታከለ ኡማ ጋር እንዲሁ በየሁለት ሳምንቱ ተገናኝተዉ ይመክራሉ፡፡ ስለዚህም ከኦፒዲኦ( ከስትራቴጅክ አጋሩ) ጋር ሁኖ አላማዉን እያሳካ ነዉ፡፡ ኢትዮጵያ ከአቢሲኒያ/ሰሜነኞች ፖለቲካ አምሳል ከተላቀቀች በኋላ ኦሮሞወች እራሱ የዘር ፖለተካን አሽቀንጥረዉ ይጥላሉ፡፡ ምክንያቱም አዲሲቱ ኢትዮጵያ በአብሲንያ አምሳል (እነሱ እንደሚሉት) ሳይሆን በገዳ አምሳል የምትሰራ ስለሚሆን፡፡ በገዳ አምሳል ከተሰራች በኋላ ብሄር ተኮር ፖለቲካ ለኦሮሞ አያዋጣዉም፡፡
ደ/ር ብርሃኑ እና ደቡብ ክልል
——-
ዶ/ር ብርሃኑ ደቡብ ክልል ወደ ሶስት እና አራት ክልል ቢከፋፈል ደስተኛ ነዉ፡፡ ደቡብ ክልል አቢሲንያዊ ሴንትመንት አለ ተብሎ የታመናል፡፡ አማረኛ የስራ ቋንቋ ነዉ፡፡ ደቡብ ክልል ያለዉ ህዝብ የሰሜነኞቹን ፖለቲካዊ አካሄድ ይቀበላል፡፡ ስለዚህም ደቡብ ተከፋፍሎ አማረኛንም ትቶ የራስ የራሱን ቋንቋ እየተጠቀመ ኢትዮጵያዊ ሆኖ እንዲቀጥል ይፈለጋል (እኩልነት የሚለዉ ይሄን ይመስለኛል)፡፡ ለ ዶ/ር ብርሃኑ እኩልነት ማለት የሰሜኑን ፖለተካ ማቀጨጭ እስከሆነ ድረስ የደቡብ ብሄሮች ከሰሜኑ ጋር የሚጋሩትን ነገር አዉልቀዉ እንዲጥሉ ይፈልጋል፡፡ ለዚህም ነዉ ዶ/ር ብርሃኑ ለክልልነት ሲታገሉ ለኖሩት ለሲዳማወች የእርሱ በሆነዉ ኢሳት ሚዲያ የአየር ሰአት ተሰጧቸዉ ህዝባቸዉን ሲያነቁ የኖሩት፡፡ ለአማራ ግን ይሄን እድል ነፍጓል፡፡የኦሮሞ ፖለቲከኞችም ዋና ስራቸዉ ደቡብን መበተን  ነዉ፡፡ ስለዚህም ዶ/ር ብርሃኑ የሲዳማን ክልልነት፤ የጉራጌን ክልልነት የወላይታን ክልልነት የሚደግፍ ይሆናል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስቴሩም በባለፈዉ የፓርላማ ንግግሩ ደቡብ ክልል ወደ ሶስት ክልል እንደሚሆን አስረደቷል፡፡ ዶ/ር ብርሃኑ ይሄን ያዉቃል፡፡ አላወገዘዉም ግን፡፡ነገር ግን ዶ/ር ብርሃኑ ከኦሮሞ ፖለቲከኞች የሚለየዉ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ችግር የለበትም፡፡ የእርሱ ትልቁ ችግሩ ኢትዮጵያ በሰሜኖች አምሳል ተሰርታለች ብሎ ብቻ ማሰቡ ነዉ፡፡ በሱ ዙሩያ ያሉት የደቡብ ልሂቃን ይሄን በግልጽ ይሉታል፡፡ ሚንሊክን በገሃድ ያወግዛሉ፡፡ ዶ/ር ብርሃኑ ምኒልክንም ሆነ አጤ ቴወድሮስን ወይም አፄ ዮሃንስን አንድ ቀን ሳት ብሎት ስማቸዉን አያነሳም፡፡የብሄር ፖለቲካ ህወሃት እንደለጠጠዉ እንዲሆን አይፈልግም፡፡ ክልል የሚለዉ ነገር እንዳለ ቢቆይም ችግር የለበትም ነገር ግን ብሄርን ከፖለቲካዉ የመነጠል ወይም የፖለቲካ ጨዋታዉን ከብሄር ላይ በማንሳት ብሄር ተኮር ፖለተካን ልክ እንደ ሰሜን ፖለተካ ብዙ ሮል እንዳይኖረዉ ማድረግ ነዉ፡፡ ሌላኛዉ የሰሜኑን ፖለተከኞች አቅም የሚቀንስበት መንገድ ከላይ እንዳልኩት አማራዉን እሱ በትክክለል  እንደሚዎክለዉ በመናገር ትግሬዉን ደግሞ ከኤርትራ በኩል ጫና እንዲደርስበት በማድረግ ነዉ፡፡
አዴፓ/ብአዴን እና ዶ/ር ብርሃኑ
——–
ዶ/ር ብርሃኑ አዴፓን ብዙም የሚፈለግበት መንገድ የለም፡፡ ክልሉ ላይ ጥሩ የፖለተካ መጫወቻ እንዲያዘጋጅለት ብቻ ነዉ የሚፈልገዉ፡፡ ከቻለ ደግሞ አብን የሚባል የወጣት ስብስብን አደብ እንዲያስይዝለት ነዉ የሚፈለገዉ፡፡ ከኦህዴድ ጋር በሳምንት 7 ቀን አንሶላ ሲጋፈፍ ከአዴፓወች ጋር ለሰከንድ እንኳን ግንኙነት የለዉም፡፡ ክልሉ ላይ የግንቦት ሰባት ቢሮወች እንዲህ ሆኑ ደጋፊዎች እንዲህ ሆኑ ለማለት ስልክ ከመደወል ዉጭ፡፡ አዴፓ በዉጭዉ አለምም ምንም አይነት እዉቅና እንደሌለዉ ያዉቃል፡፡ ኦህዴድ ትቂት ሸርተት ቢል እናብአዴን ስልጣን እረከባለዉ ቢል ነጮችን ማሳመን ይጠበቅበታል፡፡ ልክ ኦህዴድ ሁለት አመት እንደፈጀበት አሜሪካን እና አዉሮፓወችን ለማሳመን፡፡ ባንድ ወቅት ለማ መገርሳ እዲህ ብሎ ነበር ቢሮ እንዳንገባ እንኳን ይከለክሉን የነበሩ የዉጭ መንግስታት አሁን ጫማችን እየሳሙ ነዉ እንዳለዉ፡፡ በመሆኑም ከአዴፓ ይልቅ ዶ/ር ብርሃኑ መሪ የመሆን እድሉ ሰፊ ነዉ፡፡ አሜሪካኖች እና አዉሮፓወች ዶ/ር አብይን ከዶ/ር ብርሃኑ ጋር አብሮ በቅርበት እንዲሰራ አስማምተዋል፡፡ ዶ/ር አብይ stumble ቢያደርግ እንኳን ዶ/ር ብርሀኑ ቀጣይ ምርጫቸዉ መሆኑን ያዉቃሉ፡፡ ዶ/ር ብርሃኑን የሚያስቡት በሃገሪቱ ዉስጥ ከኢህአዴግ ሰወች በተሻለ ሰፊ ተቀባይነት እንዳለዉ ነዉ፡፡ ዶ/ር ብርሃኑ አዴፓን አታሎ ማለፍ ነዉ የሚፈልገዉ፡፡ ዶ/ር ብርሃኑ እና ሚዲያዉ (ኢሳት) አማራ ክልልን ከተከፋፈለ ነዉ የአማራን ፖለተካ የምናሸንፈዉ ብሎ ያስባሉ፡፡ ለዛም ነዉ ከአማራነት  ይልቅ በጎጥ ላይ የተመሰረተ ስራ የሚሰሩት፡፡ ወሎ፤ ሽዋ ጎንደር እያሉ ሰወችን በመመልመል የአማራ ብሄርተኝነት እና አንድነት እንዳይጠናከር ያደርጋል፡፡ እርሱን የሚደግፉ እንደ ጎንደር ህብረት እና ሌሎችም ድርጅቶች ጎንደር ክልል ወሎ ክልል እያሉ እንዲያራግቡ ይደረጋል፡፡ ይህ አንዱ የሰሜኑን ፖለተካ የመበጣጠስ ስልት ነዉ፡፡ አዴፓ ይህ አይገባዉም፡፡ በአሁኑ ሰአት ከአዴፓ ይልቅ ዶ/ር ብርሃኑ ቤተመንግስት አካባቢ የሚካሄደዉን ነገር በሚገባ ያዉቃል፡፡ ዉሎዉ ቤተመንግስት ስለሆነ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ከብአዴን/አማራ ቢሆን ኖሮ ዶ/ር ብርሃኑ እስካሁን 15 ጊዜ አዲስ አበባ ላይ ሰልፍ አስወጥቶ ነበር፡፡ አሁን ከኦህዴድ ጋር ባለዉ አይነት የአንሶላ መጋፈፍ አይኖረዉም ነበር፡፡ ምክንያቱም የአብሲንያ ፖለቲካ እና የአማራ የበላይነት ትርክት አለ፡፡
Filed in: Amharic