>

ህወሓታዉያንና አይዞሞርፊክ ሚሚክሬ /Isomorphic Mimicry/ (ሀብታሙ አያሌው)

ህወሓታዉያንና አይዞሞርፊክ ሚሚክሬ 
/Isomorphic Mimicry/
ሀብታሙ አያሌው
ትህነግ (ህወሓት) በ17 ዓመታት የበርሃ ቆይታው በማርክስስታዊ “ጥላትን አጥፋ እንጂ አትደራደረው”  አስተምህሮው መሰረት ለትግል የወጡ ድርጅቶችን ሁሉ ጊዜ እየጠበቀ አሰልሶ እያደባ ክህደትና ወንጀል ሲፈፅም የነበረ ድርጅት እንደሆነ ከማንም የተሰወረ አይደለም።   ድርድር የህወሓት ጠላት ብሎ የፈረጀውን ቀን ገዝቶ የማጥፊያ ዋነኛ መሳሪያው ነበር።  የበረሃ ልምዱ ብዙ ነውሩን የሚነግረን ህወሓት ደባ እየፈፀመ በጥፋት ድግስ በሴራ ወጥመዱ ስር  ከጣላቸውና ክህደት ከፈፀመባቸው መካከል :-  ኢህአፓ፣  ኢድዩ፣ ጀብሃ፣ ግግሓት ወዘተ… ሊጠቀሱ ይችላሉ።
ህወሓት ተመስርቶ ትግል ከጀመረበት ከደደቢት ሸለቆ ጀምሮ በመላው የትግል ዘመኑ ከአንድም የፖለቲካ ኃይል ጋር ተስማምቶ መስራት ያልቻለ ድርጅት እንደሆነ የፀባ-ጫሪነት፣ የክህደትና የስግብግብነት ዘመን ዘልዛላ ታሪኩ ህያው ምስክር ነው ።  ህወሓት በዘመኑ  ከአንድም ድርጅት ጋር በጋራ ተቀራርቦና ተደማምጦ የሰራበት ታሪክ ተመዝግቦ አያውቅም  አይውቅም።  ለዲሞክራሲ መርሆዎች የማይገዛ፣ ፍፁም አምባገነናዊ ሥርዓትን በዜጎች ጫንቃ ላይ ያነበረ፣ ልዩነቶችን ማስተናገድ የማይችል፣ የሚገጥመውን ልዩነት ሁሉ በአፈሙዝ እፈታለሁ ብሎ የሚያምን ገዳይ ድርጅት መሆኑን  ለማስታወስ ካልሆነ በቀር ከማንም የተሰወረ እንዳልሆነ እረዳለሁ፡፡
ህወሓት ገና በጠዋት ከምስረታው (ከ1966 ዓ/ም) ጀምሮ ከምኒልክ ቤተመንግስት ወደ መቀሌ እስካፈገፈገበት  ጊዜ ድረስ  አንድም ጊዜ ለዴሞክራሲ መርሆዎች ተገዥ ሆኖ አያውቅም።  ገጠሙኝ ያላቸውን ችግሮች ሁሉ በዓፈ ሙዝ ለመፍታት ከሚያደርው እንቅስቃሴ በቀር  በውይይት የፈታበት አንድም ተጠቃሽ ታሪክ የሌለው ድርጅት እንደሆነ የታወቀ ነው።  ይህ የግፈኞች የጭካኔ ልክ ማሳያ ሆኖ የኖረ ድርጅት በበረሃ ዘመኑ የግግሓት አመራሮችን  ለድርድር ብሎ ከጠራ በኋላ  ከሌሊቱ 9 ሰዓት ገደማ በተኙበት  የሁሉም አመራሮች አንገት ቀልቷል።  የሃሳብ ልዩነት ያላቸውን የራሱን ታጋዮች ጭምር  ረሽኗል፣  ኢትዮጵያዊ ነን ያሉ የትግራይ ኤሊት እና ልሂቃንን  በገመድ እያነቀ፣ በጭስ እያፈ፣  በጭካኔ ጭዳ ያደረገ  ድርጅት ነው።
እንደ አንዳንድ ለእውነት ያደሩ የውስጥ ሰዎች ገለፃ ከሆነ ደግሞ በህወሓት ውስጥ ታቅፈው  በትግል ሂደት ከተሰዉት  ይልቅ  ህወሓት በፖለቲካ ውሳኔ  የገደላቸው የትግራይ ልሂቃን በእጅጉ እንደሚበልጡ ይነገራል።  በጥቅሉ ህወሓት ዘመናዊና ተራማጅ ድሮጅት  አልነበርም፣  ሆኖም አያውቅም ከደደቢት በረሃ የጀመራትን የአንድ ወቅት የክላሽ ትግል የጦር ሳይንስ አዋቂነት መለኪያ፣ የጀግንነት መስፈሪያ አድርጎ ዛሬም የቀረርቶ ዜማው ማጀቢያ ማድረጉን እንደመረጠ ነው፡፡
ህወሓት ገና የምኒልክን ቤተመንስት ደጃፍ ከረገጠበት ጊዜ ጀምሮ  መላው የኢትዮጵያ ህዝብ በጥርጣሬ ከማየት ያለፈ ተቃውሞ  ለማሰማት ባይቦዝንም።  በህወሓት የጥፋት ክንድ ከመደቆስ ማምለጥ ግን አልቻለም።  ገና ከጅመሩ ተፅእኖ ፈጣሪ ያላቸውን ፖለቲከኛች፣ ምሁራኖች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ አክቲቪስቶችና ጋዜጠኞችን  በይፋም በስውርም የሞት ሲሳይ አደረጋቸው፤  እየገደለ ከመጣው በላይ ገብቶ የገደላቸው የትየለሌ ናቸው።  ብዙ የቁርጥ ቀን ልጆችን ደብዛቸው እንዲጠፋ አድርጓል፣ አስሯል፣ ለስደት እና ለመከራ  ዳርጓል፡፡
በተለይ ከምርጫ 1997 ዓ.ም በኋላ የህዝቡ የበደል ፅዋ ሞልቶ ስለፈሰሰ በሁሉም አቅጣጫ  የተፋፋመው ትግል ከባድ ዋጋ የመክፈያ ምክንያት ቢሆንም  የበደል መብዛት ግን አንገት ከማስደፋት ይልቅ የድሉን ቀን ጎትቶ ለማቅረብ ምክንያት ሆኗል።  ከብዙ እንግልት፣ ውጣ ዉረድ፣ እስር፣ መፈናቀል፣ጥፍር ነቀላ፣  ቶርች መደረግና ማምከን በኋላ የኢትዮጵያ ህዝብ ፈተናዎቹንና ስቃዩን ተቋቁሞ ባደረገው እልህ አስጨራሽ የነፃነት ተጋድሎ ህወሓት ሙሉ ለሙሉ ከማዕከላዊ መንግስት ተባራ መቀሌ እንድትመሽግ አድርጓል፡፡
በአሁኑ ወቅት መቀሌ የከተመችውን ህወሓትን ውጫዊ ሆነው ሲመለከቷት አቅም ያላት፣ የተደራጀችና ተመለልሳ ወደ ማዕከላዊ መንግስት (እንደ አዲስ ስልጣኗን የምትቆናጠጥ)  እየመሰላቸው በስጋት የሚያዩአት  ቀላል  እንዳልሆኑ እረዳለሁ፡፡  ዛሬ ረዘም ባለ ፅሑፍ  ህወሓት  አይዞሞርፊክ ሚሚክሬ (Isomorphic Mimicry) እንደምትመስል ለመግለፅ የወደድኩት ለዚያ ነው፡፡
አይዞሞርፊክ ሚሚክሬይ ፈፅሞ በማየት ብቻ ለይቶ ለማወቅ የማይቻሉ  የሁለት የእባብ አይነቶች መጠሪያ ነው፡፡  ሁለቱን እባቦች የሚያለያያቸዉ አንዱ መርዝ ያለዉ እባብ ሲሆን ሌላኛው ግን መርዝ የለዉም፡፡  መርዝ ያለዉ ተናዳፊ ነዉ መርዝ የሌለዉ አይናደፍም፣ ነገር ግን ሁለቱም እባቦች በቀለም (ከለር) እና  በቅርፅ በፍፁም የማይለዩ ተመሳሳይ በመሆናቸው  ሰዎች ሁለቱንም እኩል ይፈሯቸዋል።  መርዝ የሌለዉ እባብ መርዝ እንዳለዉ ተቆጥሮ ከመርዘኛው እባብ እኩሉ ይፈራል። ያሁኗ አቅም የከዳት ህወሓት ከለውጡ በፊት ከነበረችው መርዘኛዋ ህወሓት ጋር በመመሳሰል ያለች የመቀሌ አይዞሞርፊክ ነች።   በውጭ ስትመለከታት የመናደፍ አቅም ያላት  ውስጧን ስትፈትሻት ግን ባዶ የሆነች አይዞሞርፊክ እባብ ነች።
   ይቀጥላል …
Filed in: Amharic