ታሪኩ አበበ
–
በልጅነቱ በሥራ ምክንያት ከአዲስ አበባ አስመራ ሲመላለስ በአስመራ አሜሪካኖቹ ከፍተውት የነበረው የቃኘው ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ የሙዚቃ ፍቅሩን በእጥፍ እንደጨመሩለት ይናገራል፡፡
–
በአዲስ አበባም ቢሆን የክቡር ዘበኛ ንብረት የነበረው የጠቅል ሬዲዮ ጣቢያ አልፎ አልፎ የሚለቃቸውን ሙዚቃዎች መስማት የመንፈስ ሀሴትን ያጎናፅፉት ነበር፡፡
–
አምሃ እሸቴ ከአሜሪካ፣ ከህንድ፣ ከእንግሊዝ፣ ከኬንያ፣ ከሱዳን እና ከጣሊያን በ1950ዎቹ መጨረሻና በ60ዎቹ መጀመርያ የነበሩ ተወዳጅ የሙዚቃ ሸክላዎችን ወደ ሀገር ውስጥ በማስመጣት እና በመሸጥ ነበር የሙዚቃ ዓለምን የተቀላቀለው፡፡
–
የኢትዮጵያ ህዝብ የሀገር ፍቅር ማህበርና የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ትያትር ቤቶች በጊዜው ሙዚቃን የማሳተም መብት ከግርማዊነታቸው በፅህፈት ሚኒስቴር በኩል ቢሰጣቸውም ተግባራዊ ሳያደርጉት ዓመታት ተቆጠሩ፡፡
–
ይህን የተመለከተው ወጣቱ አምሃ ለምን እኔ አላሳትምም ሲል በድፍረት ተነሳ፡፡
–
በወቅቱ ከትያትር ቤቶቹ የተሰጠው ምላሽ “መብቱ የኛ ነውና እንዳትሞክረው” የሚል ዝግ መልስ ነበር፡፡
–
አምሃ ጉዳዩ አስጨነቀው፡፡ የንጉሰ ነገስቱን ህግ መጣስ ደሞ የሚያመጣውን መዘዝ ያውቃል፡፡
–
በሌላ ጎኑ እሱ የተለያዩ የውጭ ሀገራትን ሙዚቃ እያመጣ እየሸጠ የሀገሩ ሙዚቀኞች በሸክላ አለመቀረፅ፣ ለሌላውም ዓለም አለመተዋወቅ ከንክኖታል፡፡
–
ያለው አማራጭ በድፍረት አሳትሞ የሚመጣውን በፀጋ መቀበል ብቻ ሆነ፡፡ ለዚህ ደግሞ የሚተባበር ድምፃዊ ያስፈልጋል፡፡
–
አምሃ የሚያውቃቸውን ዘፋኞች አማከረ፡፡ ሁሉም ፈሩ፡፡” አዬ ጦስ ታመጣብናለህ “ እያሉ ወደኋላ አፈገፈጉ፡፡
–
በዚህ መሀል አንድ ወጣት ድምፃዊ ብቅ አለ፡፡ ድምፃዊው ከአምሃ ጋር የማይደፈረውን ለመድፈር ተስማማ፡፡
–
“ ከታሰርንም እየዘፈንን አብረን እንገባለን” ሲል የአምሃን ልብ በወኔ ሞላው፡፡ እናም ሆነ፡፡ እንደተፈራው እዚህ ግባ የሚባል ቅጣት ግን አልነበረም፡፡
–
ይህ ድምፃዊ ተወዳጁ አለማየሁ እሸቴ ሲሆን በአጋጣሚውም በአምሀ እሸቴ ሪከርድስ አማካኝነት የመጀመርያ የሸክላ ሙዚቃ አሳታሚ ለመሆን በቃ፡፡
–
ይህም ነጋድራስ ተሰማ እሸቴ በጀርመን ሀገር ካሳተሙት መዲናና ዘለሰኛ፣ ከነፈረደ ጎላ የሸክላ ስራ፣ እንዲሁም በጣሊያን ወረራ ወቅት ከታተሙ ጥቂት ሸክላዎች በኋላ በኢትዮጵያ ዘመናዊ ሙዚቃ ውስጥ ፈር ቀዳጅ ህትመት ለመሆን በቃ፡፡