>

"የሚያጀግነውን የሚያውቅ ህዝብ የተባረከ ነው" (በውቀቱ ስዩም)

“የሚያጀግነውን የሚያውቅ ህዝብ የተባረከ ነው”
በውቀቱ ስዩም
ባገራችን የነገስታት መታሰቢያ ሀውልት ማቆም: በጀግና ተዋጊዎች ስም ጎዳናዎችንና ትምርትቤቶችን መሰየም የተለመደ ነው:: አገሩ በሙሉ በጦርና ጋሻ  ምልክት የተሞላ ቢሆንም አሁንም  በወታደሮች: በጌቶችና በእመቤቶች ስም ሀውልት የማቆም ግፊቶች ቀጥለዋል :: በፖለቲካው ግርግር መሀል: ለህዝብ መንፈሳዊ እና አእምሮአዊ እድገት መዋጮ ያደረጉ ሰዎች ተዘንግተዋል::
ለምሳሌ ዛሬ ድረስ ላዝማሪ ሀውልት ማቆም  ተስኖናል:: ግን አዝማሪዎች ባይኖሩ ጀግኖች አይኖሩም:: ባልቻ ሳፎን የምናስታውሳቸው ወይዘሮ ፃድቄንና ሀሰን አማኑን የመሳሰሉ  አዝማሪዎች ገድላቸውን  እንዳንረሳቸው አድርገው ስለዘመሩልን  አይደለምን?   ከባልቻ ያልተናነሰ ጀብድ የፈፀሙ  ጀግኖች አዝማሪ አይንና ቀልብ  ስላልረፈባቸው ተዘንግተው ቀርተዋል::  ያጋነንሁ ከመሰላችሁ ይበልጥ ሞቅ ላርገው!! አዝማሪ  የሌለው ህዝብ ትውስታ የለውም::
ቀደምቶቻችን ቤተ -እምነት እንጂ ቤተ-ሙከራ  ገንብተው አላወረሱንም:: በዚህ ምክንያት አገሩ የሳይንስና ምርምር  ምድረበዳ ሆኖ ቆይቷል: :   በድሃ አቅማችን: ወደ ጨረቃ መንኮራኩር መላክ ብናስብ ቅብጠት ይሆናል:: ወደ ጨረቃ ዙሮ መሽናት ቂጥኝ ያስይዛል ብሎ የሚያምን ትውልድ እንዳይኖር ለማድረግ  ራሱ ብዙ ይቀረናል::  ባለምአቀፍ ደረጃ  ለሳይንስ መዋጮ ያደረጉ ሊቃውንታችን ብሄራዊ ጀግኖች አድርጎ ማስተዋወቅ  አንዱ መፍትሔ ነው ብየ አስባለሁ::
“የጋቢሳ እጄታ  ጎዳና ” : የ አክሊሉ ለማ  መታሰቢያ : አየር ማረፍያ  : “የ ተወልደ ገብረእግዚያብሄር ፓርክ ” ማየት እመኛለሁ:: አገርን ዳርድንበር ከጠላት የሚከላከልንን ብቻ ሳይሆን ከጠንቀኛ ባክቴርያና ቫይረስ  የሚከላከለንን ማጀገን ይጠብበቅብናል::
ለዘር ማንዘርህ  ብቻ መዋደቅ እርፍና በሆነበት  አገር :  ሰው ሳይመርጡ ሰው የሚያገለግሉ ሰዎች  የጀግና መታሰቢያ  ያስፈልጋቸዋል:: “የጀግነት ሁሉ አባት ፍቅር ነው” ይል ነበር ይድነቃቸው ተሰማ:: የሜቄዶኒያውን ቢኒያምና  አበበች ጎበናን የመሳሰሉትን በጎ አድራጊዎች  ሳስብ ትዝ የሚለኝ ይህ አባባል ነው::
ወዘተረፈ..
ባገራችን  ከጥንት እስከዛሬ የጀግንነት ትርጓሜ ከጦርነት አልወጣም:: ምናልባት የጀግነትን  ትርጉም ስንቀይር  ያለንበት ሁኔታ ይቀየር ይሆን?
Filed in: Amharic