>

የኦነግ መግለጫ "የኢሕኣዴግ ሠራዊት በሰላማዊ ዜጎች ላይ እየፈጸመ ያለውን ግድያ በጥብቅ እናወግዛለን!!! "

ታህሳስ 27, 28 እና 29, 2018 ዓም በምዕራብና ደቡብ ኦሮሚያ (ቄሌም ወለጋ, ምዕራብ ወለጋና ጉጂ) ዞኖች ውስጥ ብቻ “የሃገር መከላከያ ሠራዊት” በሚል የሚታወቁ የኢሕኣዴግ ወታደሮች በሰላማዊ (ትጥቅ-ኣልባ) የኦሮሞ ዜጎች ላይ በፈጸሙት ዘግናኝ ግድያ እስካሁን በተረጋገጠ መረጃ ቢያንስ 36 የሚሆኑ ሰዎች ተገድለው ቁጥራቸው እስከ ኣሁን በውል ያልታወቀ ደግሞ ቆስለዋል። በርካታ የህዝቡ መኖሪያ ቤቶችም በእሳት ጋይተዋል። የኢህኣዴግ ጦር ሃይል ኣባላት እየወሰዱት ባለው በዚህ በእጅጉ ኣስከፊና አረመኔያዊ እርምጃ ከተገደሉት ዜጎች መካከል ሁለት እድሜያቸው 5 ዓመት ያልሞላቸው ህጻናት በጉጂ ዞን ዱግዳ ዳዋ ወረዳ ከቤት ጋር እንዲቃጠሉ ተደርገዋል። በምዕራብ ወለጋ ዞን ጊምቢና ጉሊሶ መካከል በሚገኝ ኩርፌ ብርብር በተባለ ቦታም ኣንድ ህጻን ከወላጅ እናት ጋር ከነቤታቸው ተቃጠሉ። እነዚህን መሰል የግድያ ወንጀሎች የተፈጸሙባቸው ቦታዎች በቄሌም ወለጋ፡ ምዕራብ ወለጋና ጉጂ ዞኖች ውስጥ ጊዳሚ፡ ኮበረ፡ ከታ ኣባ-ኮርማ፡ ሁዋ፡ ዋዪ ኩሊ፡ ኩርፌ ብርብር፡ ዩብዶ፡ ላሎ ቂሌ፡ ፊንጫኣ፡ ኮምቦልቻና ሻላ በተባሉ ቦታዎች ውስጥ ነው። በጉጂ ከተገደሉት 23 ከሚሆኑት መካከል 5 ዓመት ያልሞላቸው ህጻናትና የ70 ዓመት ኣዛውንት ይገኙበታል።
የኦሮሞ ነጻነት ግንባር በሰላማዊ (ትጥቅ-ኣልባ) ሰዎች ላይ በኢህኣዴግ ወታደሮች እየተፈጸመ ያለውን ኣሰቃቂ፡ ግድያ ኣጥብቆ ያወግዛል። ይህን መሰሉ የኣውሬነት ኣረመኔያዊ እርምጃም በዝምታ መታየት የሌለበትና በሁሉም ሰላም-ወዳዶች መወገዝ ያለበት ነው ብለንም እናምናለን። የጭቆናና ኣምባገነናዊ ስርዓት (በጠብመንጃ ኣፈሙዝ ህዝብን የሚገዛ) ካሁን በኋላ እንደማይቻል ለኢህኣዴግ ፓርቲ ለማሳየት ለመገመት የሚያዳግት የህይወትና የንብረት መስዋእትነት ተከፍሎበታል። የኢህኣዴግ ፓርቲም ከ27 ዓመታት በኋላ (ተገዶም ቢሆን) ይህንን እውነታ ኣምኖ እንደተቀበለና በውስጡ ለውጥ/ተሃድሶ እንዳደረገ ገልጾ፡ ወደ ዲሞክራሲ ለሚደረግ ሽግግር ከሁሉም የሃገሪቷ የፖለቲካ ሃይሎች ጋር በሰላማዊ መንገድ ለመስራት ቃል ከገባ ውሎ ኣድሯል። ይሁን እንጂ በተግባር መሬት ላይ እየታየ ያለው ኢህኣዴግ የስልጣን ዘመኑን ለማራዘም ባለፉት 27 ዓመታት ሲከተለው በነበረው የኣምባገነንነት ጎዳና የሙጢኝ ማለቱን ነው።
ኢህኣዴግ በጦር ሃይል መዋቅሩ ውስጥ ተሃድሶ ኣካሂጃለሁ ብሎ በኣፉ ይለፍፋል። ይሁን እንጂ “የሃገር መከላከያ ሠራዊት” በሚል ስም የተደራጀው የኢህኣዴግ ጦር ዛሬም የኢህኣዴግን የፖለቲካ ዓላማ ለመጠበቅ የቆመ መሆኑን እንጂ ህዝባዊ ወገንተኝነት ያለው ስለመሆኑ የምያሳይ ኣንዳችም ምልክት የለም። ይህ ጦር ዛሬም ከኢህኣዴግ የተለየ የፖለቲካ ኣመለካከት ያላቸውን ሰዎች እንደጠላት ማየቱን ቀጥሏል። ለዚህ ማስረጃ የሚሆነው በኦሮሚያ ውስጥ በደረሰበት ቦታ ሁሉ የኦነግ/የኦሮሞን ባንዲራ ጨምሮ የተለያዩ ኦነግን የሚገልጹ ምልክቶችን ማውደምና እንዲህ ያሉ ነገሮችን በእጃቸው ያገኘ ሰዎችን ለጉዳት በመዳረግና በማሸበር ላይ መሆኑ ነው።
ይህ የኢህኣዴግ አደገኛ ኣካሄድ የፖለቲካ ምሕዳሩን ለማስፋትና የሁሉንም የሃገሪቷ ዜጎች የዲሞክራሲ መብቶችን ለማክበር ኢህኣዴግ እራሱ የገባውን ቃል የሚጻረር ነው። ይህ ደግሞ ኣሁን የታየውን የለውጥ ተስፋ ጭላንጭል መልሶ የሚያጠፋና በኦሮሚያ፡ በኢትዮጵያና በኣካባቢዋ ከፍተኛና ኣዉዳሚ የጦርነት አደጋ የሚያስከትል ስለሆነ ኢህኣዴግ በኣስቸኳይ ከዚህ ድርጊቱ እንዲታቀብ ኦነግ ኣጥብቆ ይጠይቃል። ኢህኣዴግ በእምቢታዉ ጸንቶ ኣሁን በያዘዉ የጦረኝነት ኣካሄድ የሚቀጥል ከሆነ ግን ከዚህ ጋር ተያይዞ ለሚከሰቱ ኣደጋዎች ሁሉ ተጠያቂው እራሱ/ኢህኣዴግ መሆኑን ኦነግ ያስገነዝባል።
የኦሮሞ ነጻነት ግንባር
ታህሳስ 29 ቀን 2018ዓ.ም.
Filed in: Amharic