>

ሕወሃት ስንል ገዳይ! ሕወሃት ሲሉ ትግራይ! (ሀይለገብርኤል አያሌው)

ሕወሃት ስንል ገዳይ! ሕወሃት ሲሉ ትግራይ!
ሀይለገብርኤል አያሌው
ለህዝብ ጥቅም ተቆጣጠርነው ባሉት ሚድያ የቀረበው ዶክመንተሩ የብዙዎችን ልብ ሰብሯል:: እንባ አራጭቶ ቁጭት እልህና የበቀል ስሜትን ቀስቅሷል:: ሃገሩ ኢትዮጵያ ሕዝቡም አማኝና ታጋሽ ሆኖ እንጂ ይህን ያህል የሚከብድ የሰቆቃ አይነትና መጠን ሰምቶና አይቶ አልቅሶ የሚያድር ሕዝብ በሌላ ሃገር የሚኖር አይመስለኝም:: በእኛይቱ ኢትዮጵያ ግን ሁሉ ሆነ::
ሕወሃቶች  ሲዘርፉና ሲገሉ በቡድን ሲካፈሉ ለየግል ቢሆንም : ተቃውሞና ትግሉ ሲበረታ በትግራይ ሕዝብ ላይ እንደተናሳ በማድረግ እኩይ ሴራ ሲቀምሩ ኖረዋል:: እነሳሞራ የትግራይ ሕዝብ ማለት ሕወሃት ሕወሃት ማለት ትግራይ ነው በሚል በአደባባይ ተናገዋል:: ሕወሃትን መንካትም የትግራይ ሕዝብን በመጥላት ሲወነጅሉና ሲያሸማቅቁ ከርመዋል::
ይህ ሁሉ ሆኖ ግን በአብዛኛው  ፓለቲከኛውም ሆነ አክቲቪስቱ ሕወሃትንና የትግራይ ሕዝብን ነጥሎ ከመመልከት ውጪ እንደሃገር ለደረሰብን መከራና ስቃይ የትግራይ ሕዝብን ተጠያቂ ሲያደርግ ታይቶ አይታወቅም::
እርግጥ ነው ሊካድ የማይችል የሃገርና የሕዝብ ንብረት በጠራራ ጸሃይ እየተዘረፈ ወደ ትግራይ ተጭኗል:: የኢትዮጵያ ሕዝብ በሚከፍለው እዳ ትግራይን ልትሽከመው የከበዳት የኢንዱስትሪ ማዕከል አድርገዋታል::
  ሕዝቡ የዕለት  ጉርሱን መቻል አቅቶት ልጆቹ በጠኔ በሚወድቁባት ሃገር የሕወሃት አባላትና ደጋፊ የትግራይ ተወላጆች በሻፓኝ ሲታጠቡ በድህነት ተራራ ላይ ቆመው በቅንጦት የሚያደርጉትን ሲያጡ ሕዝባችን አንጀቱ እያረረ ተመልክቷል:: ነጋዴው ወታደሩ ፖሊሱ ከዜጎች በላይ ዜጋ እነማ እንደነበሩ ሕዝቡ በደንብ ያውቃል:: ይህ ሁሉ ሆኖ ግን ሕወሃትንና የትግራይን ሕዝብ አልደባለቀም::
ሕዝባዊው መዐበል ነቅንቆ ከመንበሩ የፈነቀለው የሕወሃት ፈላጭ ቆራጭ አገዛዝ አክትሞ አዲስ የለውጥ ሁኔታ ሲሰፍን በግልጽ እንደታየው በየትም አካባቢ የትግራይ ተወላጆችን የለየ ትንኮሳ አልተደረገም:: አሁን አሁን ግን የሕዝባችን ትግስት እያለቀ ሕወሃትና የትግራይ ሕዝብ የሚለየው ድንበር እየጠፋው እየተቸገረ ይገኛል:: በዘረፉና በዜጎች ላይ አሰቃቂ ወንጀል የፈጸሙ ተጠርጣሪዎችን መንካት ትግራይን መንካት ተደርጎ የታየበት ተደጋጋሚ ሰልፎች በትግራይ አይተናል::
አካላቸውን ያጡ ወንድሞቻችን የቁስላቸው  ጠባሳ ለደረሰባቸው አይደለም ላየነውና ለሰማነው የሚሰጠው ስሜት ከባድ ነው:: ይህ ሁሉ ግፍ የተፈጸመው በትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪ የትግራይ ተወላጆች ለመሆኑ ሰቆቃውን ካስተናገዱት ወገኖች  በላይ ማስረጃ አይገኝም:: ያን ሁሉ መከራ የቻሉት ወንድሞች ስቃይና እንግልት ስድብና መንጏጠጥ ያደረሱባቸው ትግሬዎች ቢሆኑም የትግራይ ሕዝብን የማይወክሉ የጥቂት አውሬዎች ድርጊት መሆኑን በጨዋነት ገልጸዋል::
ለዚህም ነው አብዛኞቻችን ትግራይ ስንል መልካም ኢትዮጵያዊ ወገናችን ስንል የኖርነው:: ሕወሃት ስንል ገዳይ ቀማኛና የጥላቻ ምንጭ ብለን የታገልነው:: ከእንግዲህ ወደ ሗላ የሚመለስ ማንም የለም:: ግፍ የፈጸሙ የሕወሃት አባላት አይደሉም ሕወሃት በሚል ስም የሚቆም የፖለቲካ ቡድን አይኖርም:: ይህ ትውልድ ባየውና በሰማው ሰቆቃ አምርሯል:: ፍትሕ ይፈልጋል ወንጀለኞች ለፍርድ እንዲቀርቡ ይታገላል::
ከዚህ ባለፈ እንዳለፉት አመታት የፖለቲካ ቧልት ሕወሃትን መንካት ትግራይን መንካት አድርጎ የሚወስድ ወገን ካለ የሚመጣውን ለመቀበል ሊዘጋጅ ይገባል:: በተለይ የትግራይ ልሂቃን የሃይማኖት አባቶች የሃገር ሽማግሌዎችና በዲያስፖራ ያለው የትግራይ ማህበረሰብ በግልጽ ወጥቶ በሕወሃትና በትግራይ ሕዝብ መካከል ያለውን አንድነትና ልዩነት በግልጽ ካላስቀመጠ ጥቂቶች በፈጸሙት ነውር መላ ተወላጁ ተጠያቂ እንዳይሆን በ11ኛው ሰዐትም ቢሆን ደፍረው ሊያስረዱ ይገባል::
አለያ በርባንን አስፈትተው እየሱስን ለማሰቀል ከግፈኞች ጋር ያበሩ አይሁዳውያን ጺላጦስ ከዚህ ሰው ደም ንጹህ ነኝ ሲል ደሙ በኛና በልጅ ልጆቻችን ላይ ይሁን ብለው መርገምን ለትውልዳቸው እዳወረሱት እንዳይሆን:: የትግራይ ወገናችን ዲያቢሎስ ሕወሃት ከውድቀት ላይድን ሃገርና ወገን እንዳያሳጣችሁ ተግታችሁ ልትመክሩ ይገባል:: መከራ ያበቀለው በቀል መጨረሻው አያምርም:: ጥቂት ጭራቆች ላፈሰሱት ደም ብዙሃኑ በሃጢያት እንዳይደመር ሊታሰብበት ይገባል::
ፈራጁም ፍርድ አስፈጻሚውም እነርሱም ሆነው በህዝብ ላይ ሲያደርሱት የኖሩትን ሰቆቃ ለአብነት ያህል:-
*** ቀን ቀን ዳኛ፣ ማታ ማታ ገራፊ ***
አቶ ዘርዓይ ወልደሰንበት ማታ ማታ የሚገርፋቸውንና የሚያስገርፋቸውን እስረኞች ቀን ላይ ዳኛ ሆኖ ይፈርድባቸዋል። የገረፋቸውና ያስገረፋቸው የቀድሞ እስረኞች ምስክር ሆነው ሊቀርቡበት ይችላሉ። የዚህ ሰው ስም በህግ ከሚጠየቁ ወንጀለኞች ሊስት ውስጥ መግባት አለበት።
”ጨው ለራስ ስትል ጣፍጥ አለያ ……..”
ማስተዋሉን ያድለን!
Filed in: Amharic