>

“ኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ዕንቅፋቶቿን ሁሉ ማጥፋት አለባት” (ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ)

“ኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ዕንቅፋቶቿን ሁሉ ማጥፋት አለባት” 
ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ
ጎልጉል 
* አማራና ትግራይ ክልሎች ከቃላት ጦርነት ወደ መሣሪያ መማዘዝ? 
 
*የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ዑመር ሀሰን አልበሽር ወደ አስመራ  ሊያቀኑ ነው!
 
“ቀለበት ውስጥ ገብተናል” ህወሀት
ሰሞኑን በአማራና በትግራይ ክልል መካከል የተፈጠረው የመግለጫ እሰጥ አገባ ከቃላት ጦርነት ወደ መሣሪያ መማዘዝ እንዳይቀየር ፍርሃቻ አለ። የኤርትራው መሪ ኢሳያስ አፈወርቂ ወደ አማራ ክልል ለጉብኝት መምጣታቸው በህወሓት አቀንቃኞች ዘንድ በፍርሃቻ እየታየ ነው፤ ሌሎች የዘር ፖለቲካ አራማጆች ደግሞ ጉብኝቱን ስህተት ነው ብለውታል።
የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቅና የሱማሌው ፕሬዚዳንት ሙሐመድ አብዱላሂ ፎርማጆ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ግብዣ ዛሬ በአማራ ክልል ጉብኝት ለማድረግ ጎንደር ገብተዋል። ይህ በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነው ጉብኝት የጎንደርና አካባቢውን ታሪካዊ ቦታዎች ለመመልከትና በባህር ዳር ውበት ለለመሰጥ እንዳልሆነ ግልጽ ነው። በተለይ ኢሳያስ በተደጋጋሚ በትግራይ አመራር ላይ ካሉት የህወሓት ሰዎች የቀረበላቸውን የወዳጅነት ጥያቄ ችላ በማለት ከህወሓት ጋር በበርካታ የማንነትና የወሰን ጥያቄ እየተናቆረ ወደሚገኘው የአማራ ክልል መምጣታቸው የህወሓትን ደም ግፊት ከፍ የሚያደርግ እንደሆነ እየተነገረ ነው።
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በአማራ ክልል በተለያዩ ቦታዎች የተነሳውን ግጭት አስመልክቶ የትግራይ ክልል የከረረ መግለጫ ሲያወጣ ቆይቷል። በአማራ መስተዳድር መተማ ከተማ በሚኖሩ በአማራ እና በትግራይ ተወላጆች መካከል ሰሞኑን በተቀሰቀ ግጭት በርካታ ሕዝብ ከቤት ንብረቱ ተፈናቅሏል። የትግራይ መስተዳድር ግጭቱን አስመልክቶ ባወጣዉ መግለጫ “አንዳንድ” እና “ከፍተኛ” ያላቸውን የአማራ መስተዳድር ባለሥልጣናትን ተጠያቂ አድርጓል፤ ለፍርድ እንዲቀርቡም አሳስቧል።
ሁለቱ ፕሬዚዳንቶች ወደ ጎንደር ከመምጣታቸው በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሁለት የተለያዩ ውይይቶች ከወልቃይት ጠገዴና ከቅማንት የአገር ሽማግሌዎች ጋር በየአካባቢው ስለተቀሰቀሱ ግጭቶችን እና እንዴት በሰላም በመፈታት እንዳለባቸው ተወያይተዋል።
ሰሞኑን ከቅማንት ሕዝብ ጋር በተያያዘ በአካባቢው የተነሳውን ግጭት አስመልክቶ የአማራ ክልል ሰላም እና ደኅንነት ቢሮ ሃላፊ ብርጋዴር ጄኔራል አሳምነው ጽጌ የቅማንት ሕዝብ ወኪሎች ነን የሚሉ ጽንፈኛ ኃይሎች ከሌሎች አካላት ጋር በቅንጅት ሆነው ጥፋት እያደረሱ እንደሆነ ለቢቢሲ አማርኛ ተናግረዋል። ጄኔራሉ ቡድኖቹ በትክክል ከእነማን እንደሆኑና ከማን ጋር እንደሚሠሩ በስም ጠቅሰው ባይናገሩም የክልሉን ሰላም ለመበጥበጥ ከጎረቤት ሀገር ወይም ከሀገር ውስጥ ከአጎራባች ክልል (ትግራይ) ጋር ስትራቴጂ ተነድፎ እየተሠራ ነው ብለዋል። ለዚህም እንደ ማስረጃ ይሆን ዘንድ በምዕራብ ጎንደር እና መተማ አካባቢ ሰሞኑን በተፈጠረው ግጭት በገበሬ እጅ ሊገኙ የማይችሉ ጦር መሣሪያዎች መገኘታቸውንም አክለው ገልጸዋል። ወደፊት የሚጣራ ቢሆንም ላሁኑ በጥቃቱ የሞቱት የአማራ ብሄር ተወላጆች ይልቃሉ ብለዋል።
በቅማንት ጉዳይ ላይ ለዓመታት በከፍተኛ ሁኔታ ሲሠራ የኖረው ህወሓት በትግራይ ክልል ስም ባወጣው መግለጫ በግጭቱ “አንዳንድ” እና “ከፍተኛ” ያላቸውን የአማራ መስተዳድር ባለሥልጣናትን እጃቸው አለበት ማለቱን ጄኔራል አሳምነው “ሃሰት” በማለት አጣጥለውታል።
ባለፉት ቀናት በተለይ በመተማ አካባቢ ደረሰ የተባለውን ግጭትና በትግራይ ተወላጆች ላይ ተፈጸመባቸው የተባለውን ጥቃት አስመልክቶ ህወሃት የሚመራው የትግራይ ክልል ጥቅምት 27/2011 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ ላይ “ችግር በተፈጠረባቸው ኣከባቢዎች ኣንዳንድ የኣማራ ክልል ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ኣስቀድመው በማንቀሳቀስ የደረሰውን ግፍ እንዲፈፀም ኣመራር” ሰጥተዋል በማለት በግልጽ ኮንኗል። ሲቀጥልም “… በህዝባችን ላይ የሚፈፀሙ የጥፋት ተግባሮች ኣይተን እንዳላየን እንሆናለን ማለት ኣይደለም” በማለት በቀጣይ እርምጃ እንወስዳለን የሚል እንደምታ ያለው መግለጫ አውጥቶ ነበር።
ለዚህ በህወሓት ለተረቀቀው የትግራይ ክልል መግለጫ አዴፓ የሚመራው የአማራ ክልል በሰጠው ምላሽ “… የህዝብን ሠላም ለማስጠበቅ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ሙሉ አቅሙን ተጠቅሞ ርብርብ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን እየገለፅን መላ የክልላችን ህዝቦችም የተገኘውን ሠላም እና ነፃነት በመጠበቅ ከመንግስት ጐን እንዲሰለፍ” ጥሪ አድርጓል።
በማኅበራዊ ሚዲያ በአክቲቪስትነት የሚታወቁ ከአማራም ከትግራይ ያሉ ሰሞኑን በመተማና ሽንፋ አካባቢ የደረሰው አስመልክቶ ብዙ ሊባልበት የሚችል መልዕክቶችን ተለዋውጠዋል። ሙሉቀን ተስፋው በፌስቡክ ገጹ “ሽንፋና መተማ ያሉ አንዳንድ የመከላከያ አባላትን አነጋግሬ ነበር። ከባድ መሣሪያ ታጥቆ መሸገው የሕወሓት ማፍያ ቡድን በሄሊኮፍትር ካልታገዘ በስተቀር በእግረኛ ጦር ብቻ ማስቆም አልቻልንም ብለውኛል። ጦርነቱን እየመሩ ያሉት ትግርኛ ተናጋሪ የቀድሞ ጦር አባላትን ናቸው” በማለት ለጻፈው ህወሓትን በይፋ የሚደግፈው ዳንኤል ብርሃኔ ምላሽ ሰጥቶ ነበር።
“ምን እየቀባጠሩ እንዳሉ ግልጽ ባይሆንም፤ አጼ ቴድሮስን ያፈራው ታላቁ የቅማንት ህዝብ የገዱ አንዳርጋቸውን እና የኣሳምነው ጽጌ ጀሌዎችን እየገረፈ ያለ ይመስላል። የመይሳው ካሳ እና የገብርየ ህዝብ ላይ ጥይት የተኮሰ እድሜውን አሳጠረ! ቅማንትን አገውን አጥፍቼ እቀጥላለሁ የሚል ፋሺሽታዊ ሀይል የኢትዮጲያን ታሪክ ቁጭ ብሎ ቢማር ይበጀዋል” በማለት ዳንኤል ለሙሉቀን ጽሁፍ ቀጥተኛና የማያሻማ መልስ ሰጥቷል።
ሃሳቡን እንደፈለገ በመቀያየር የሚታወቀውና ብዙዎች ሁሉን “አዋቂ ነኝ” ባይነቱን ብቻ ሳይሆን የመርህ ሰው አለመሆኑን የሚመሰክሩበት የዘር ፖለቲካ አቀንቃኙ ጃዋር መሐመድ ደግሞ የኢሳያስ አፈወርቅን ጉብኝት በመቃወም ብልሃት የጎደለውና ያለጊዜው የተደረገ ብሎታል። በሁለቱ ክልሎች (አማራና ትግራይ) መካከል የተፈጠረውን ውጥረት የበለጠ ከማጋጋል በተጨማሪ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል እየቀጠለ ባለው ሰላማዊ ግንኙነት ላይ ጉዳት ሊያደርስ ይችላል ብሏል። (ጃዋር “reproachment” በማለት የጻፈው የተሳሳተ ሲሆን ትክክለኛው “rapprochement” ነው)።
በቅርቡ ከራያ የማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ አላማጣ ላይ አምስት ሰዎች መደገላቸው ታወቃል። ይህንን አስመልክቶ “የማንነት አስመላሽ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አግዜ ህዳሩ” ለቢቢሲ አማርኛ ሲናገሩ “ራያ አዘቦ፣ ራያ አላማጣ እና ኦፍላ የማንነት ጥያቄ የሚነሳባቸው ወረዳዎች ናቸው … የአካባቢው ህዝብ ላለፉት ሦስት እና አራት ወራት የማንነት ጥያቄዎችን በሰላማዊ መንገድ ለማቅረብ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል … የትግራይ ክልል መንግሥት ግን ከፍተኛ ቁጥር ያለውን ልዩ ኃይል ወደ አካባቢው በማስገባት የማንነት ጥያቄውን ለማዳፈን ወጣቶችን በማሸማቀቅ ከፍተኛ የሆነ የሥነ-ልቦና ጫና እያደረገ ነው” ብለዋል።
ይህንን ጉዳይና የተገደሉትን አስመልክቶ የትግራይ ክልላዊ መንግሥት ኮሚኬሽን ጉዳዮች ቢሮ በፌስቡክ ገጹ ላይ “የህዝብን የማንነት ጥያቄ በማስመሰል ሌላ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት እየተደረገ ያለው ሩጫ በማንኛውም መመዘኛ ተቀባይነት የሌለው ተግባር ነው” በማለት በዚህ ተግባር ላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የተሳተፉትን አካላት በቸልታ አላልፋቸውም በማለት ማስጠንቀቂያና ዛቻ የተቀላቀለበት መግለጫ ማውጣቱ አይዘነጋም።
ከዚህ የራያ የማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ ወደ ትግራይ የሚወስዱ መንገዶች ተዘግተው ለቀናት የቆዩ ሲሆን በመከላከያ ሠራዊት ጣልቃ ገብነት እንደገና ሊከፈቱ ችለዋል። ሆኖም ተግባሩ በትግራይ ክልል ላይ ተመሳሳይ ድርጊት ቢፈጸም በመስተዳደሩና በህወሓት ላይ ሊያመጣ ስለሚችለው አሉታዊ ተጽዕኖ የተወሰነ ግምት ሰጥቷል።
ከራያ ጋር በተመሳሳይ የማንነት ጥያቄ በማንሳት በህወሓት የአገዛዝ ዘመንም የትግራይ የውስጥ እግር እሣት ሆኖ የቆየው የወልቃይት ጉዳይ የራሱን መልክ እየያዘ መጥቷል። ጎልጉል ያነጋገራቸው በጎንደር የሚገኙ የወልቃይት ተወላጅ “ከእንግዲህ ወዲህ በድርድር ወይም በውይይት የምንፈታው ነገር የለም፤ እነሱ በራሳችን አገር ምሽግ እየቆፈሩ ሳለ እኛ እንደራደር የምንልበት ምንም አግባብ የለም” ብለዋል። ሌላ እዚያው ጎንደር ከተማ በግል ሥራ ተሰማርተው የሚገኙና የወልቃይት ተወላጅ መሆናቸውን መናገር እንደማፈልጉ የገለጹ “የወልቃይት ሕዝብ ከአገሩ ተፈናቅሏል፤ ስልታዊ የዘር ማጥፋት ተካሂዶበታል፤ አልበገርም ብሎ እስካሁን ቆይቷል፤ አሁን በኃይል የተወሰደበትን በኃይል ከማስመለስ በቀር ምንም አማራጭ የለውም” በማለት ለጎልጉል ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ የለውጥ ንፋስ መንፈስና የህወሓት የበላይነት መክሰም ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በትግራይ የመሸገው ህወሓት በተለይ ከኤርትራ ጋር የተጀመረውን ወዳጅነት የራሱ ለማድረግ በርካታ ጥረቶችን ሲያደርግ ቆይቷል። ከኤርትራ ጋር የሚደረግ ግንኙነት ለህወሓት ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ያለው ከመሆን ባሻገር በሱዳን በኩልም ያለውን ክፍተት እንደፈለገ መጠቀም እንዲችል ምቹ ዕድል የሚፈጥርለት ነው።
ኢሳያስ ከኢትዮጵያ ጋር የቀጥታ ግንኙነት በማድረጋቸው ታላቅ የፖለቲካ ኪሳራ ውስጥ የገባው ህወሓት ለኤርትራ የምንቀርበው እኛ ነን፤ በደምም የተሳሰርነው እኛ ነን ከማለት አልፎ “የኤርትራ ልጆች! አማራ ባህራችሁን ይፈልጋል፤ እኛ ትግራዮች ግን የምንፈልገው ፍቅራችሁን ነው” እስከማለት የደረሰ መሆኑ አይዘነጋም።
በመቀጠልም ኢሳያስን ለማባበል እና ኤርትራውያንን ወገናዊ ለማድረግ የኤርትራ ቲቪ ወደ ትግራይ መጥቶ እንዲዘግብ ህወሓት ላቀረበው ጥያቄ ኢሳያስና መንግሥታቸው ከህወሓት ጋር የጎንዮሽ ግንኙነት እንደያማያደርጉ በመግለጽ ጥሪውን ውድቅ ማድረጋቸው የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው።
ህወሓትን የፈጠሩትና ማንነቱን የሚውቁት ኢሳያስ አሁን ባለንበት ወቅት ህወሓትን አጥብቀው ይጸየፉታል፤ የወንበዴ ቡድኑንም መሪዎች እጅግ ይንቋቸዋል። ከዚህ አንጻር ህወሓት የኢትዮጵያና የኤርትራ የጋራ ጠላት መሆኑን ኢሳያስ በውል ያውቃሉ።
ኢሳያስ አፈወርቂ እኤአ ሰኔ 20 (ሰኔ 13) ባደረጉት ንግግር በኢትዮጵያ እየተከሰተ ያለውን ለውጥ ካደነቁ በኋላ በዋንኛነት የንግግራቸው ትኩረት የነበረው “መርዘኛ፣ በጣም አደገኛ፣ (ተንኮለኛና ምቀኛ) ስለሆነው የህወሓት ሌጋሲ” ነበር። ሲቀጥሉም የህወሓት “ጥምብ አንሣዎች” ሥልጣናቸውን እንዳጡ ሲያውቁ በመደናገጥ “አዎንታዊውን ለውጥ ለማጨናገፍ” ይህም በሁለቱ አገራትና በኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚሠሩ ንግግራቸውን ሊያደምጥ ለተሰበሰበው ሕዝባቸው በግልጽ ተናግረው ነበር።
ከዚህ በተጨማሪ ኢሳያስ ወደ ጎንደር ለጉብኝት ለመምጣት እየተዘጋጁ ባሉበት ወቅት በሁለቱ አገራት መካከል ስለተደረሰው ስምምነት አስመልክተው በሰጡት ቃለምልልስ “ኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ዕንቅፋቶቿን ሁሉ ማጥፋት አለባት” በማለት ስለ ህወሓት በግልጽ ተናግረዋል። (“On TPLF: Ethiopia must eradicate all hurdles to ensure the success of peace.”)
ከዚህ ሌላ ሱዳንና ኤርትራ ግንኙነታቸውን ሊያድሱ እንደሆነ ተነግሯል። ባለፈው አመት ሱዳን በኳታርና ኢትዮጵያ ታግዛ ልትወረኝ ነው ስትል ኤርትራ ክስ አቅርባ የነበረ ሲሆን በዚህም ምክንያት አገሮቹ ወታደሮቻቸውን ወደ ድንበር እስከማስጠጋት ደርሰው ነበር። በአሁን ወቅት የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ዑመር ሀሰን አልበሽር ወደ አስመራ  ለማቅናት እየተሰናዱ ሲሆን በዚህ ሳምንት የሱዳን ልዩ ልዑክ ወደ አስመራ ተጉዞ ሁኔታዎችን እንደሚያመቻች ተነግሯል።
ይህ የሱዳንና የኤርትራ ወዳጅነት ለኢትዮጵያ በተለይም ህወሓት በጉልበት ከጎንደር ወስዶ የትግራይ በማድረግ ከሱዳን ጋር ያካለለውን ድንበር ለማስመለስ በሚደረገው የሚጫወተው የራሱ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ እንዳለው ብዙዎች ያምኑበታል። ከዚህ በተጨማሪ የሶማሊ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፋ ከኢሳያስ ጋር እየመሰረቱ ያሉት የቅርብ ወዳጅነት በእርግጥም ህወሓት በተደጋጋሚ “ቀለበት ውስጥ ገብተናል” የሚለውን ዕውን እያደረገ የመጣ ሐቅ ሆኗል። በኖቬምበር 14 በህወሓት ጎትጓችነት በኤርትራ የተጣለው የተባበሩት መንግሥታት ማዕቀብ እንዲነሳ ቀጠሮ መያዙ የዐቢይ ቀጥተኛ ጣልቃገብነት ያለው ብቻ ሳይሆን ኢሳያስ ለዚህ አጸፋ ብዙ እንዲከፍሉ የሚያደርግ ውለታ ሆኖ ተወስዷል።
በኢሳያስ አነጋገር “መርዘኛ፣ በጣም አደገኛ፣ (ተንኮለኛና ምቀኛ)”፣ “ጥምብ አንሣዎች”፣ “አዎንታዊውን ለውጥ አጨናጋፊዎች” ተብሎ የተጠቀሰው ህወሓት ከአማራ ክልል ጋር ከገባው እሰጥ አገባ የቃላት ጦርነት ባለፈ ወደ መሣሪያ መማዘዝ ለመሄድ ዙሪያው ሁሉ የታጠረበት ይመስላል። አልፎ ተርፎም ሶማሊያና ሱዳን ከኤርትራ ጋር ስምምነት በመፍጠር ለመጓዝ የመረጡት መንገድ የዐቢይና ኢሳያስን ግንኙነት ወደላቀ ምዕራፍ ከማድረስ አልፎ ኢሳያስ “ኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ዕንቅፋቶቿን ሁሉ ማጥፋት አለባት” በማለት ስለ ህወሓት የተናገሩትን ዕውን ወደማድረግ የተቃረቡ አስመስሏቸዋል።
Filed in: Amharic