>

“ህዝብ መንግስትን ይፈጥራል እንጂ መንግስት ህዝብን አይፈጥርም” (ሻምበል ለማ ጉያ - ሰዓሊ)

“ህዝብ መንግስትን ይፈጥራል እንጂ መንግስት ህዝብን አይፈጥርም”
ምበል ለማ ጉያ (ሰዓሊ) አዲስ አድማስ
ኢትዮጵያን አትንኩ ነው! ኢትዮጵያን መንካት ዋጋ ያስከፍላል! ቀድሞ ጊዜ ጥሪ አሳልፈናል፤ አሁን የሚታየው ግን በዚህ እድሜዬ በእጅጉ ያሳስበኛል!!!
እኔ አሁን የ90 ዓመት አዛውንት ነኝ፡፡ የዚህችን ሀገር ብዙ ሂደቶችና ውጣ ውረዶች አይቻለሁ። ከዛሬ 40 እና 50 ዓመት በፊትም ሆነ ዛሬ፣ ከ80 በላይ ብሄሮች በዚህችው በኢትዮጵያ ስር ነው የምንኖረው፡፡ የተለወጠች የተቀየረች ሀገር የለችንም፡፡ የተለወጠው ፖለቲካው ብቻ ነው። ሀገሪቷም ህዝቧም ያው ናቸው፤ አዲስ የመጣ ህዝብ የለም፡፡ ጃንጥላችን ኢትዮጵያችን ነች። ኢትዮጵያ ማለት አንድ ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ አሜሪካ ስንል ሃምሳ ስድስት ግዛት የሚለው ወደ አዕምሯችን ፈጥኖ አይመጣም፡፡ ወደ አዕምሯችን የሚመጣው ጠንካራዋና አንድ የሆነችው አሜሪካ ምስል ነው። በአድዋ ጦርነት ጠላትን አሸንፈን ሃያላንን ያስደነገጥነው በ10 ወይም 11 ግዛቶች ተከፋፍለን አይደለም፤ በአንዲት ኢትዮጵያ ጥላ ስር ሆነን ነው፡፡ ጎሰኝነትና ዘረኝነት፣ ሀያል እንሆናለን ብለው ለተነሱት የጀርመኑ ሂትለርና የጣሊያኑ ሞሶሎኒም አልበጀም፡፡ ሺህ ጦርና ጉልበት ቢኖር አንደበት ፍቅርና አንድነትን ካልሰበከ፣ ተከታዮቹ ሰይጣኖች ስለሚሆኑ የኋላ ኋላ የትም ተጥለው ነው የሚቀሩት። ሂትለርና ሞሶሎኒ መጨረሻቸው ያላማረው አስተሳሰባቸውን የራሳቸው ህዝብ ስለማይወደው ነው፡፡ ስለዚህ አንድነትን መስበክ የፈጣሪ ስራን መስራት ነው፡፡ ያስከብራል እንጂ አያዋርድም፡፡ ዘረኝነት ነው የሚያዋርደው፡፡ የህዝብን አንድነት ለማምጣት የሚደረግ ጥረት ሁሉ ከሰይጣን በስተቀር ሁሉም ይደግፈዋል፡፡
አፄ ቴዎድሮስ ለ66 ዓመታት ኢትዮጵያን የከፋፈሉ መሳፍንቶችን አጥፍቶ አንድነትን የሰበከ ሰው ነው፡፡ ዛሬ በርካቶች በስሙ የሚጠሩት ታሪኩ ኩራት ስለሆናቸው ነው፡፡ ዛሬ ኢትዮጵያ 10 ቦታ ነው የተከፋፈለችው፡፡ ይሄ ጥሩ አይደለም። ይሄን ህዝብና ሃገር አንድ ማድረግ ያስፈልጋል። ይሄን የሚያመጣ ሙሴ ያስፈልገናል፡፡ እዚህ ጋ አንድ ታሪክ ማንሳት እፈልጋለሁ፡፡ ዛሬ የህንድ ውቅያኖስ የሚባለው ጥንተ ስሙ የሶማሌ ውቅያኖስ ነበር፡፡ ሶማሌዎች በጎሳና በዘር በመከፋፈላቸው አንድነታቸውን ማስጠበቅ ተስኗቸው፣ ጥንተ ስማቸውንና ክብራቸውን በንግድ እንቅስቃሴ የዘመኑ ሃያል በነበረችው ህንድ ተነጥቀዋል። ኢትዮጵያም ክብሯ ተጠብቆ የሚኖረው በጎሳ በመከፋፈል ሳይሆን በፅኑ አንድነት ብቻ ነው፡፡
በአድዋ ጦርነት ምኒልክ መሪ ሆኑ እንጂ የተዋጋው ከየአቅጣጫው የተሰባሰበው ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ ይሄ የህዝቡ አንድነት ደግሞ የሚያኮራ ነው፡፡ እነሱ በአንድነት በአኩሪ ገድል ያስረከቡንን ሀገር ለመበታተን በመጣደፋችን አዝናለሁ፡፡ እኛ ሽማግሌዎች ነን፤ ወጣቶቹ ይህቺን ሀገር ሊበትኗት ሲነሱ ያሳዝነናል፡፡
የት ልንሄድ ነው? እኛ በዚህ እድሜያችን እንሰደዳለን እንዴ? ይሄ ሊታሰብበት ይገባል፡፡ እኛ ታግለን ይህቺን ሀገር አስረክበናል፤ ትውልዱ ግን ራሱን ወዳልሆነ አቅጣጫ እየወሰደ ነው፡፡ መልዕክቴ፡- ኢትዮጵያን አትንኩ ነው፡፡ ኢትዮጵያን መንካት ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ቀድሞ ጊዜ ጥሪ አሳልፈናል፤ አሁን የሚታየው ግን በዚህ እድሜዬ በእጅጉ ያሳስበኛል፡፡ ህዝብ ነው መንግስትን የሚፈጥረው እንጂ መንግስት ህዝብን አይፈጥርም፡፡ ይሄ መታወቅ አለበት፡፡
Filed in: Amharic