>
5:13 pm - Monday April 19, 4630

"እኔ ዕድሜ ልኬን፣ ሙሉ ሕይወቴን ለአማራ ሕዝብ ጥቅም ስሠራ ነውየኖርኩት!!" - አቶ ታደሰ ካሳ (ጥንቅሽ)

“እኔ ዕድሜ ልኬን፣ ሙሉ ሕይወቴን ለአማራ ሕዝብ ጥቅም ስሠራ ነውየኖርኩት!!”

 አቶ ታደሰ ካሳ  (ጥንቅሽ)

* ‘እኛ ስለማንፈልግ ውጣ የምትሉኝ ከሆነ እናንተ ልቀቅ ስላላችሁኝ ወይም እናንተ ስላገዳችሁኝ አልወጣም፤ እስከመጨረሻው ድረስ እታገላችኋለሁ። ቆይም ብትሉኝ አልቆይም። በራሴ ውሳኔ ለቅቄ ነው የምወጣው’ 

የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ አቶ ታደሰ ካሳን እና አቶ በረከት ስምኦንን ከማዕከላዊ ኮሚቴ አባልነት ማገዱ ይታወሳል።

አቶ ታደሰ የብአዴንን ውሳኔ በተመለከተ፤ በጥረት ኮርፖሬሽን ውስጥ ስለነበራቸው ተሳትፎ እንዲሁም ቀጣይ የፖለቲካ ህይወታቸው ምን ሊመስል እንደሚችል ለቢቢሲ አካፍለዋል

ጥያቄ፦ ከብአዴን ማእከላዊ ኮሚቴ ለምን የታገዱ ይመስልዎታል?

አቶ ታደሰ፦ የጥረት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ነበርኩ። ለዘጠኝ ዓመት ያህል አገልግለናል። በዛ ቆይታ ጥረት ብዙ ለውጥ አምጥቷል። እኔ አመራር ላይ እያለሁ በጣም አስደናቂ ለውጥ እያመጣ የነበረ ደርጅት ነው። ሂደቱ የማይስማማቸው ሰዎች ይኖራሉ። አንዳንድ የሚነሱ ነገሮች ነበሩ። ችግር አለ ይባል ነበር። እኛም በየጊዜው እየተማርን ነው ሥራውን ስንመራ የነበረው። የቢዝነስ ሥራ ነው። በ20 ሚሊየን ብር ተጀምሮ እኔ በምወጣበት ጊዜ ወደ 11 ቢሊየን ብር ካፒታል ያላቸው 20 ኩባንያዎችን ነው የፈጠርነው። ጉድለት ነበር የሚለውን አስቀድመን ራሳችን ያየነውና እየገመገምን፣ መጨረሻም ሥር ነቀል የሆነ መፍትሄ ለማምጣት የሚችል ሥራ ስንሠራ ነው የነበረው። ከዛ የጤንነትም የዕድሜም ጉዳይ ስላለ ከዚህ በኋላ «ጥረት» ላይ በቃኝ በሚል ሚያዝያ ወር ላይ በራሴ ለቅቄ ወጣሁ።

ጥያቄ፦ በራስዎ ፍቃድ እንጂ ተገድጄ አይደለም የወጣሁት እያሉ ነው?

አቶ ታደሰ፡- ደብዳቤው እኮ በእጄ አለ። በግልጽ ነግሬያቸው ነው…። አሉ የምትሏቸውን ጉድለቶች ራሳችን የገመገምናቸው ናቸው። ከዚ ውጪ ያባከንነው ገንዘብ የለም። በግልም ደግሞ የሠራነው ጥፋት የለም። በዚህ ረገድ ማንም ደፍሮ ይሄን ሀብት ወስደሀል፤ ይሄን አድርገሀል የሚለኝ ካለ ይምጣ። የጀመርኳቸው አምስት ፕሮጀክቶች ስለነበሩኝ ‘የኮርፖሬት ፋይናንሱን ወርልድ ክላስ ለማድረግ’…፣ ነው ትንሽ የቆየሁት እንጂ፤ ለመውጣት ካሰብኩኝ ቆይቷል።

‘እኛ ስለማንፈልግ ውጣ የምትሉኝ ከሆነ እናንተ ልቀቅ ስላላችሁኝ ወይም እናንተ ስላገዳችሁኝ አልወጣም፤ እስከመጨረሻው ድረስ እታገላችኋለሁ። ቆይም ብትሉኝ አልቆይም። በራሴ ውሳኔ ለቅቄ ነው የምወጣው’ የሚል ነገር ተነጋግረን፣ ‘ባንተ ውሳኔ ነው’ ተብሎ ደብዳቤውም በዛ ነው የተሰጠኝ። ሚያዝያ ላይ ከ3000 በላይ የክልሉ ካድሬ በተሰበሰበበት ‘በራሱ ፍቃድ ጠይቆ ነው የወጣው’ ብሎ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩም ተናግሯል። ሰለዚህ ከጥረት በራሴ ነው የወጣሁት።

ጥያቄ፦ ከማእከላዊ ኮሚቴ እባረራለሁ ብለው ይጠብቁ ነበር?

አቶ ታደሰ፦ አንደኛ ያለፈው ሰባተኛው ጉባኤ ላይ እኛ አንመረጥም እያልን አባላት መመረጥ አለባቸው ተብሎ አስገድደውን ነው የተመረጥነው። ከተመረጥን በኋላ ደግሞ በቃ ብትመርጡንም አንቀጥልም ብለን ስናንገራግር ነው የቆየነው።

የዛሬ ሦስት ዓመት በነበረው ጉባኤ ላይ አንመረጥም ያልነው ‘ለውጥ የለውም፣ ይሄ ድርጅት ሊለወጥ ፍቃደኛ አይደለም። ባለፈው ምርጫም ቢሆን ሕዝቡ ማስጠንቀቂያ ነው የሰጠን እንጂ ደግፎን አልመረጠንም። ስለዚህ አሁንም ካልታረምን በስተቀር በ2008 አመጽ አይቀርም በሚል በግልጽ ነበር ስናነሳ የነበረው።

ጥያቄ፦ ግን እንደዚህ ዓይነት ሐሳቦችን የሚያነሱት ስለተባረሩ ነው ወይስ ከዛ በፊትም ለሕዝብ አሳውቀዋል?

አቶ ታደሰ፦ አይደለም! አይደለም። የድርጅታችን ባህል አለ። በድርጅቱ አመራር ውስጥ ትታገላለህ። ከድርጅቱ እስካለቀቅክ ድረስ በአደባባይ አትናገርም። በድርጅታችን ጉባኤ ስንናገር ነበር። በጉባኤ ላይ ስንታገል ነበር። አንመረጥም ስንል ነው የነበረው። አባላት ያውቁታል ይሄን። በድርጅቱ ሰነዶች የተመዘገበ ነው።

ጥያቄ፦ ለምን ይመስልዎታል ታዲያ እርስዎና አቶ በረከት ድጋፍ እያጣችሁ የመጣችሁት?

አቶ ታደሰ፦ ዘረኛ የሆኑ አስተሳሰቦች በድርጅታችን ነበሩ፤ አንቀበልም አልን። ‘የዚህ ብሔር የበላይነት አለ። ይሄኛው ብሔር አማራን ጎዳ፤ ይሄ ተጠቀመ ምናምን’ የሚባል ነገር ስንታገል ቆይተናል። ከዚያ ውጭ ግን ዘረኝነቱ አለ። ከአቶ በረከት ጋር የሚነሳው እናትና አባቱ የኤርትራ ሰው ስለሆኑ የሚል ነው። እኔም ኮረም አካባቢ ስለሆነ የተወለድኩት ከዚህ ጋር ተያይዞ ዘረኝነት አለ።

‘ሰው ለየትኛው ዓላማ ይታገላል?’ የሚለው ሳይሆን እያንዳንዱ ሰው ባደገበት አገር፣ በገነባው ሥነ ልቦና ነው የሚታገለውና የሚኖረው። ቤተሰቡ ከየትም ቦታ ሊመጡ ይችላሉ። ግን ተወልዶ ያደገበት አካባቢ ላይ ደግሞ የሱ ሥነልቦና ይገነባል። በዚያ ሥነ ልቦና ተመርኩዞ በዚያ በዚያ ነው የማንኛውም ሰው እንቅስቃሴ የሚለካው ብለን እናምናለን። ሆኖም እነዚህ የቆዩ የዘረኝነት ቅሪቶች አሉ።

አኔ የተወልዱት ኮረም በሚባል አካባቢ ነው። ኮረም አሁን ትግራይ ክልል ያለበት ቦታ ነው። ስለዚህ ቤተሰቦቼ አማራም፣ አገውም፣ ትግራይም የሦስቱም ቅልቅል ያለባቸው ናቸው። እና ንጹሕ አማራ አይደለም የሚባለው ነገር… አለ። እኔ ብቻ ሳይሆን ሌሎችም የብአዴን አመራሮችም በተለያየ ጊዜ እንዲህ ዓይነት ነገር ይነሳባቸዋል።

ጥያቄ፦ እርስዎ ራስዎን ከየትኛው ብሔር ነኝ ነው የሚሉት?

አቶ ታደሰ፦እኔ ወሎ ወስጥ ነው ያደኩት፤ ወሎዬ ነኝ መታወቂያዬም አማራ የሚል ነው።

ጥያቄ፦ ባለፉት ዓመታት የአንድ ፓርቲ የበላይነት ነበረ ብለው ያምናሉ?

አቶ ታደሰ፡- አልነበረም። ኢህአዴግ የአራት አቻ ፓርቲዎች ድርጅት ነው። እያንዳንዱ ድርጀት በእኩል ይወከላል። እኩል ድምጽ አለው። አንዱ የበላይ ሆኖ ሊያዝበት የሚችል ድርጅታዊ አሠራር አልነበረም።

ጥያቄ፦ ብአዴን በህወሓት ይዘወር ነበር የሚለውን ሐሳብ ይቀበሉታል?

አቶ ታደሰ፦ ይሄንን አልቀበልም። ብአዴን ድርጅታዊ ነጻነቱን ጠብቆ የሚሄድ ድርጅት ነው። ህወሓትም እንደ ድርጅት እኔ ያልኳችሁን ብቻ ፈጽሙ የሚል ድርጅት አልነበረም፣ በባሕሪው። ብአዴን የሕወሓት ተጎታች ሆኖ አያውቅም። የኢትዮጵያ ችግርም የአንዱ የበላይ የመሆን ችግር ነበር ብለን አናስብም።

ጥያቄ፦ ለአማራው ታግያለሁ ብለው ያስባሉ?

አቶ ታደሰ፦ እኔ ዕድሜ ልኬን፣ ሙሉ ሕይወቴን ለአማራ ሕዝብ ጥቅም ነው ስሠራ የኖርኩት። ያንን ሕዝብ ወክዬ ስታገል ኖሪያለሁ። ጥቅሙን ለማስከበር ስታገል ኖሪያለሁ። አልታገልክም የሚለኝ ሰው ካለ ያላደረኩበትን መንገድ መናገር ያለበት እሱ ነው።

ጥያቄ፦ በፓርቲ ደረጃም በሕዝቡም ለምን ተቃውሞ የበረታባችሁ ይመስልዎታል?

አቶ ታደሰ፦ሕዘቡ ኢህአዴግ ላይ ያሳደረው ጥላቻ ‘አንደርስታንደብል’ ነው። ድክመቶች አልተፈጠሩም የሚል አስተሳሰብ የለንም። ሁለተኛ አመራር ላይ በነበርንበት ሁኔታ ላይ እኛ ነባር አመራር ስለሆነ ድክመቶቹን ኋላ የመጡ ሰዎች ናቸው የፈጠሯቸው ብለን አንልም። በጋራ የተሠሩ ስህተቶች አሉ። በጋራ ተጠያቂ ነን። በ17ቱ ቀን ውይይት ሁሉንም ጨርሰነዋል እኮ። ከዚህ በኋላ መሠረታዊ ለውጥ ካላመጣን አደጋው የአገር አደጋ ነው ብለን ተስማምተን ወጥተናል። ማንም ይመረጥ ማንም አብረነው እንጓዛለን ብለናል። ከዚያው ውጭ ግን አንዱ ተጠያቂ፣ አንዱ ነጻ የሚባል ነገር ብዙም የሚያስኬድ አይመስለኝም።

ጥያቄ፦ አሁን ላይ የሚታየውን ለውጥ ዶክተር ዐብይ ያመጡት ነው ብለው ያምናሉ?

አቶ ታደሰ፦ እርሳቸውም እኔ ያመጣሁት ለውጥ ነው ሲሉ ሰምቼ አላውቅም። ኢህአዴግ መለወጥ አለብኝ ብሎ፣ ሰፊ ግምገማ አድርጎ፣ ለሠራው ጥፋትም የኢትዮጵያ ሕዝብን ይቅርታ ጠይቆ የመጣ ለውጥ ነው። እርሳቸውንም የመረጣቸው ኢህአዴግ ነው። ስለዚህ ኢህአዴግ እያካሄደ ያለው ለውጥ አድርጎ ማየት ትክክል ነው የሚመስለኝ።

የርሳቸውን አካሄድ በሚመለከት ኢህአዴግ ውሳኔ ይወስናል፤ የወሰነውን ውሳኔ ለመተግበር አመራሮችን ያደራጃል። ዶክተር ዐብይ ፈጣን የሆኑ እንቅስቃሴዎችን በማድረግ ረገድ ጥሩ እየሄዱ እንደሆነ እገነዘባለሁ። የኢህአዴግ ውሳኔዎች መሆናቸው አንዳለ ሆኖ ማለቴ ነው።

ጥያቄ፦ ጥቃት ይደርስብኛል ብለው ይሰጋሉ?

አቶ ታደሰ፦ እኔ በመጀመሪያ ደረጃ የኢትዮጵያ ሕዝብ አስተዋይ ሕዝብ እንደሆነ አምናለሁ። ሁለተኛ በግሌ ለጥቃት የሚያጋልጠኝ የሠራሁት ጥፋት አለ ብዬ አላምንም። ስለዚህ ጥቃት ይደርስብኛል ብዬ የምጨነቅባቸው ነገሮች የሉም። ይህ እንዳለ ሆኖ ጥቃት ቢመጣ ደግሞ ምንም የምፈራበት ምክንያት የለም። ለኔ አሁን ያለሁበት ሕይወት ትርፍ ሕይወት ነው። ብዙ መስዋእትነት አልፈን ነው እዚህ የደረስነው። የማምነበትን ነገር እናገራለሁ፤ እሠራለሁ። ከዚህ አንጻር በስጋት አገሬ ጥዬ የምሄድበት ሁኔታ የለም። በይፋ እየተንቀሳቀስኩ ነው ያለሁት። አንዳንድ ቦታዎች ላልሄድ እችላለሁ። ከሁሉ በፊት መቅደም ያለበት ግን የአገራችን ሰላም ነው። እኔ፣ የኔ መስዋእትነት ተከፍሎ አገር ሰላም የሚሆን ከሆነ ደስታውን አልችልም።

ጥያቄ፦ ከ”ጥረት” ጋር በተያያዘ በምዝበራ የሚጠየቁ ይመስልዎታል?

አቶ ታደሰ፡-ሁሉም በይፋ ያለ ነገር ነው። በኦዲት እየተረጋገጠ የሄደ ነገር ነው። ሁሉም ነገር መሬት ላይ ነው ያለው። ፋብሪካዎቹ አሉ፤ ሰነዶቹ አሉ። በዚያ ማረጋገጥ ይቻላል። አሁን እኔ በዚህ ጉዳይ ላይ ‘ተጠያቂ እሆናለሁ፤ እርምጃ ይወሰድብኛል’ የሚል ስጋቱም ፍርሃቱም የለኝም። የሚመጣ ነገር ካለም ለመብቴ እታገላለሁ።

ጥያቄ፦ ከኢህአፓ-ኢህዴን፣ ከኢህዴን- ብአዴን…ቀጣይ ሕይወትዎ ወዴት ያመራል?

አቶ ታደሰ፡-ከ40 ዓመት በላይ ፖለቲካ ሕይወት ውስጥ ኖረናል። አሁን መጽሐፍ የምንጽፍበት፤ በማኅበራዊ ጉዳዮች የምንሳተፍበት የማረፊያ ዕድሜ ላይ ነን። ወደ አክቲቭ ፖለቲካ ግን አልመለስም።

Filed in: Amharic