>
5:13 pm - Monday April 20, 4229

የቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ጥፋቱ ምንድን ነው?[ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ-ማርያም]

ሰኔ 2006 ዓ.ም

Tewodros Kasahun Teddy Afroቴዎድሮስ ካሣሁንን በአካል አላውቀውም፤  በዘፈንና በጭፈራ በእውነት ተደሳች መሆን ካቃተኝ ቆይቷል፤ ከ ኅዳር 1967 ጀምሮ ነው የቆረቆረኝ፤ ይህ ሰው እንደሰውና እንደ ኢትዮጲያዊ በየጊዜው የሚደርስበትን ወደ ግፍ የሚጠጋ በደል ስመለከት ያው የለመድነው ምቀኝነት ነው እያልሁ ሳልፈው ቆየሁ፤ ግን በደሉ አላቆም አለ፤ ማንም ሊደርስለት አለመቻሉ ይበልጥ ያሳዝናል፣ በእሱ ላይ ተከታታይ  የደረሰበት በደል የሕግ ያለህ የሚያሰኝ ነው፤ በቴዎድሮስ ካሣሁን ላይ በተቀነባበረ መንገድ የሚፈፀመው ማሰቃየት ማንንም ሰው የሚያሳስብ ነው፤ ምክንያቱ ምንድን ነው? በግልጽ የታወቀ ነገር የለም።

በቴዎድሮስ ላይ ከባድ ተንኮል ሲፈጸምበት የሰማሁት በመጀመሪያ ዛሬ በስደት ላይ ባለው « አዲስ ነገር» የሚባል ጋዜጣ ላይ ነበር፤ ጋዜጣው ቴዎድሮስ በሙያው ያገኘውን መልካም ስም በሰፊው ጥላሸት ቀብቶት ነበር፤ በጣም ሰፊ የሆነ ሀተታ በቴዎድሮስ ዘፈኖች ላይ በማቅረባቸው ምን ያህል አንገብጋቢ የአገር ጉዳይ አግኝተውበት ይሆን ብዬ አነበብሁት፣ ምንም ለአገር  የሚጠቅም ጉዳይ አላገኘሁበትም፤ በዘፈኖቹ ላይ በተደረገው ሂስም ከጋዜጠኞቹ መሀከል የሙዚቃ ሙያ ባለቤት እንዳለ ብጠይቅም ጋዜጣው ባለሙያ እንደሌለውና ስሙ እንዲጠቀስ ያልፈለገ ባለሙያ ማማከራቸውን ነገሩኝ፣  ስሙ  እንዲጠቀስ የማይፈልግ ባለሙያ፣ ባለሙያ አይባልም፣ እንኳን በሙያው በራሱም አይተማመንም ማለት ነው፤ በዚህ በራሱ በማይተማመን ሰው ምስክርነት ላይ በተመሰረተ ረጅም ነቀፌታ ቴዎድሮስን ደበደቡት፤

ሁለተኛው የቴዎድሮስ ጣጣ በመኪና ሰው ገጭቷል ተብሎ መከሰሱ ነው፤ በሌሊት፣ በጨለማ ነው፤ ቴዎድሮስ እንደሚለው  «እኔ ወደአገሬ የገባሁት ሰውዬው ሞተ በተባለበት ቀን ማግስት እንደሆነ ቪዛዬ ያረጋግጣል፣»  (ነጋድራስ መስከረም 30/2001 ዓ.ም. ) በኋላም ከዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የተገኘው መረጃ ይህንኑ የሚያረጋግጥ እንደነበረ ተነግሮአል፤  በዚሁ በነጋድራስ ጋዜጣ ላይ የሚከተሉት መረጃዎች ተጠቅሰዋል ፦

  1. ቴዎድሮስ ከውጭ የተመለሰው በ22/2/1999 ዓ.ም መሆኑ
  2. ሰውዬው በ 22/1/1999 ሞቶ አስከሬኑ በ22/2/1999 ዓ.ም መመርመሩን የጽሑፍ ማስረጃ፣
  3. ዓቃቤ ሕግና ፖሊስ በሆስፒታሉ የተገለጸው የምርመራ ቀን እንዲለወጥ መጠየቃቸው፣
  4. ከአሥራ ሦስት ቀኖች በኋላ በተደረገ ምርመራ መኪናው ላይ ምንም ደም አለመገኘቱን፣

ይህ ሁሉ ሆኖ በቴዎድሮስ ላይ ተፈርዶበት ወህኒ ወርዶ ጊዜውን ጨርሶ ከወጣ ቆይቶአል።

ከዚያ ወዲህ ደግሞ በተቀነባበረ ሁኔታ ቴዎድሮስ ካሣሁን በዘፈኑ ያገኘውን ዝና ለማጉደፍና በሥራውም የሚያገኘውን ጥቅም ለመቀነስ ተግተው የሚሠሩ ሰዎች መኖራቸውን የሚያመለክቱ ነገሮች አሉ፣ በመጀመሪያ ቴዎድሮስ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የፈጸመው በደል ከአለ ግልጽ ሆኖ ቢወጣና ሁላችንም ብናውቀው ጥሩ ነው፤ አለዚያ ግን እየተደራጁ አንድ ግለሰብን ለማጥቃት የሚደረገው እርምጃ የሚወገዝና ልንቃወመው የሚገባ ጉዳይ ነው፣  አንድን ሰው በእምነቱ፣ በአስተያየቱ፣ ወይም ስኬታማነቱን በመመቅኘት ለመጉዳት ዓለም -አቀፋዊ ሴራ ማካሄድ ክፋት ነው፤ ይህንን ክፋት አምጠው የወለዱትና ለማሳደግ የሚሞክሩት ሰዎች፤ የማሰብ ችግር ያለባቸውና ክፋታቸው ተመልሶ እነሱኑ የሚያጠቃ መሆኑን የመገንዘብ ችሎታ  እንኳን የሌላቸው ናቸው።

ሦስተኛው የቴዎድሮስ ስቃይ የበደሌ ቢራ ፋብሪካ በቴዎድሮስ ዘፈን ለመጠቀም ሲፈልግ፣ የጨለማ ሰዎች ተሰብስበው በቴዎድሮስ ዘፈን የታጀበውን የበደሌ ቢራ እንደማይጠጡ በመዛታቸው ኩባንያው ከቴዎድሮስ ጋር የነበረውን ውል መሰረዙ ነው፤  እንደተገነዘብሁት ቴዎድሮስ ትንሽ በቁንጫ ተሰቃየ እንጂ ክፍያው አልቀረበትም፣ ነገር ግን ቴዎድሮስን አንደሰው፣ እንደኢትዮጵያዊ፣ እንደዘፋኝ የሚያውቁት ሰዎች የሉም፤ ወይም በጨለማዎቹ ሰዎች ተሸንፈዋል፤ ወይም በፍርሃት ቆፈን ደንዝዘዋል! የጨለማ ሰዎቹ ቴዎድሮስ ካለበት አንጠጣውም የተባለው ቢራ ለቴዎድሮስ ወዳጆች እንዴት ጣፈጣቸው?

አራተኛው የቴዎድሮስ ስቃይ የመጣው ሦስተኛውን ጥቃት ለመቋቋምና ለማረም ምንም ዓይነት የማረሚያ እርምጃ ስላልተወሰደ ነው፤ የበደሌ ቢራ ኩባንያ እንዳደረገው ሁሉ የኮካኮላ ኩባንያም ቴዎድሮስ ካሣሁንን ለአሻሻጭነት መረጠ፤  የጨለማዎቹም  ሰዎች እንደገና ተነሡ፤  ቴዎድሮስን ካልሻራችሁ ኮካ ኮላ አንጠጣም  ብለው የቴዎድሮስ ውል እንዲፈርስ አደረጉ፤  አሁንም ቁንጫው ትንሽ ምቾቱን ከመቀነሱ በስተቀር ቴዎድሮስ ገንዘቡን አላጣም፤ አሁንም የቴዎድሮስ ወዳጆች ነን የሚሉ ኮካ ኮላ እየጣፈጣቸው ይጠጣሉ፤ ትንሽ ቆራጦች የጨለማ ሰዎች  በአደባባይ ምላሱን እየሳለ እልል ከሚለውና ከሚጨፍረው ነፍሰ-ቢስ ስብስብ ምን ያህል እንደሚበልጡና ውጤታማ እንደሚሆኑ ያሳያል።

የቴዎድሮስ ካሣሁን ጉዳይ የአንድ ግለሰብ የሰብዓዊ መብት ጉዳይ ነው፤ የጨለማ ሰዎቹ ግን ወደግለሰብነት ደረጃ ገና ያልደረሱ ናቸው፤ ስለዚህም ቴዎድሮስን እንደሰው እንዳያዩት እዚያ ገና አልደረሱም፤ እንደኢትዮጲያዊ እንዳያዩት መናፍቃን ናቸው፤ እንደዘፋኝ እንዳያዩት ጆሮአቸው አይሰማም።

በአዲስ ነገር ተጀምሮ እስካሁን አልበርድ ያለው ቴዎድሮስን ነጥሎ የማጥቃት ዘመቻ ምክንያቱ ምንድን ነው? በጥሞና ሊታይና ሊመረመር የሚገባው በአዲስ ነገር ጋዜጣና በጨለማዎቹ ሰዎች መሀከል ያለ የሚመስለው ድርጅታዊ ግንኙነት ነው፤  የአንድ ግለሰብን ሰብዓዊ መብቶች እየደጋገሙ በመርገጥ አጋጣሚ እየፈለጉ ማጥቃት የሚጎዳው ተረጋጩን ብቻ ሳይሆን ረጋጮቹንና የጋን ወንድሞችንም ነው፤ አንድ ቀን ግፍ ወደተነሣበት ይመለሳል።

Filed in: Amharic