>

የቅዳሜው ዝግጅትና ታሪክ አጥፊው ዳንኤል ክብረት!  (ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው) 

የቅዳሜው ዝግጅትና ታሪክ አጥፊው ዳንኤል ክብረት! 
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው 
ዳንኤል ሃይማኖትን የሚጠቀመው ለንግድ ብቻ ሆኖ ባገኘው እኮ ነው እንዲህ ብየ መጠየቄ ወገኖቸ! ምን ዓይነት ዘመን ላይ እንደደረስን አላውቅም ሰዎች በሰፊው ያለአንዳች እፍረት “እግዚአብሔር ማለት ሆድ ነው ሌላ እግዚአብሔር የለም!” የሚል በሚመስል አስተሳሰብና እምነት ኢሃይማኖታዊ ኢሞራላዊ በሆነ መንገድ ሃይማኖትን የሚሸቃቅጡ፣ በሃይማኖት ስም የሚነግዱ ሰዎች የሞሉበት ዘመን ላይ ነው ያለነው፡፡ ከነኝህ ዓይነት ሰዎች አንዱና ዋናውም ዳንኤል ክብረት (ጋኔል ክስረት) ነው፡፡
በእግዚአብሔር የሚያምን ሰው ሌላው ሁሉ ቢቀር ቢያስ “እግዚአብሔር ምን ይለኛል?” የሚል መንተፍረት ይኖረዋል፡፡ ዳንኤል እኮ “እግዚአብሔር ምን ይለኛል?” የሚል ነገር አያውቅም፡፡ እንኳን የማያየውን እግዚአብሔር “እግዚአብሔር ምን ይለኛል?” ሊል ይቅርና የሚያያቸውንና ማንነቱን በደንብ እንደሚያውቁ የሚያውቃቸውን ሰዎች እንኳ ፈጽሞ “ምን ይሉኛል?” የሚባል እፍረት ቅንጣት አይሰማውም፡፡ እኔ ምን ዓይነት የጉድ ፍጥረት እንደሆነ ግራ ይገባኛል፡፡ ለሰው ልጅ ከዚህ የከፋ ምን ውርደትና ኪሳራ አለው???
ስለ ዳንኤል ሳስብ ምን እንደሚታሰበኝ ታውቃላቹህ??? እሱን እንደ አርዓያ የሚቆጥሩት ክርስቲያኖች ክርስቲያናዊ ሕይዎታቸውን በእሱ ተግባርና አስተሳሰብ ተርጉመውና ቃኝተው እንደሱ ሲኖሩ ከክርስቲያናዊ ሕይዎት መስመር መሳታቸውና መክሰራቸው ነው የሚያሳስበኝና የሚያሳዝነኝም ነገር፡፡
በቀደም ቅዳሜ ዕለት በ28,11,2010ዓ.ም. ተሰዶ የነበረውን የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን ወደ ሀገር መግባት አስመልክቶ እነሱ እርቅ ለሚሉት ጉዳይ በሚሊኒየም (በአምዓት) አዳራሽ ዝግጅት አድርገው ነበር፡፡
በዚያ ዝግጅት ላይ የዝግጅቱ መሪ የነበረው ከዚህ ቀደም በድብቅ አሁን ደግሞ በግልጽ የወያኔ/ኢሕአዴግ ቀንደኛ ካድሬ (ወስዋሽ) የሆነው ዳንኤል ይሄ “በአንድ መንበር ሁለት ፓትርያርክ!” ብለው ያስቀመጡትንና በቤተክርስቲያን ላይ የፈጸሙትን ተደጋጋሚ የቀኖና ጥሰት በደል “አያውቅም!” ብለው በንቀት ለሚያዩት ሕዝበ ክርስቲያን ትክክለኛ እርምጃ አድርጎ እንዲያስብ ለማድረግ በማሰብ ዳንኤል ምን አለ መሰላቹህ፦
“በዐፄ ዘርአያዕቆብ ዘመንም በደቂቀ እስጢፋ ምክንያት በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ያሉ አባቶች ከማዕከሉ ጋር ለመቶ ዓመታት ያህል ተለያይተው ቆይተው ነበር!” አለና ይሄንን “በደቂቀ እስጢፋ በሰንበት አከባበርና በሌላም ምክንያት ተፈጠረ!” ያለውንና “ለመቶ ዓመታት ያህል ቆየ!” ያለውን መለያየት ጸብ መልሶ በዛው ጸቡ መለያየቱ ተፈጸመ ባለው ዘመን “በዐፄ ዘርዓያዕቆብ አሸማጋይነት ተፈታ!” ይላል፡፡ የዘመን መሳከሩን ልብ በሉ!
እንዲያ ይልና “ከስድስት መቶ ዓመት በኋላም ተመሳሳይ ችግር በቤተክርስቲያን ተፈጥሮ ነበር ይሄው አሁን በጠ/ሚ ዶ/ር ዐቢይ ተፈታ!” ብሎ በእጅጉ የተሳከረ ነገር በማውራት ይሄ ቤተክርስቲያንን በሁለት ሲኖዶስ፣ በሁለት ፓትርያርክ የመከፋፈል ችግር ከዚህ ቀደሞም በታሪካችን በአማራ ነገሥታትም የነበረና በዘመነ ወያኔ ብቻ የተፈጠረ እንግዳ ነገር እንዳልሆነ ሁለት ጊዜ አንደኛው የዝግጅቱ እንግዶች ከመምጣታቸው በፊት ለተሰበሰበው ሕዝብ እና ለሁለተኛ ጊዜ ደግሞ እንግዶቹ ከመጡ በኋላ በማውራት እንዲህ ዓይነቱን በቤተክርስቲያን ላይ የተፈጸመ ድፍረት የአማራ ነገሥታትም የፈጸሙት ለማስመሰል አሳፋሪ፣ ወራዳና ነውረኛ የባንዳ ጥረት አደረገ፡፡
ይሄ ነውረኛ ሰው ቀጠለና “ከ1600 ዓመት በፊት አብርሃ እና አጽብሐ በአንድ ዙፋን ተቀምጠው ሀገር መርተዋል፡፡ አሁን ደግሞ በዘመናችን ይሄው በአንድ መንበር ሁለት ፓትርያርክ ተቀምጠው ቤተክርስቲያንን ሊመሩ ነው!… ይሄንን ለማየት አበቃን!” በማለት በሥርዓት ጨርሶ የማይገናኝንና የማይመሳሰልን ነገር ሊገናኝና ሊመሳሰልም የማይገባውን ምድራዊን ሥልጣን ከሰማያዊ ሥልጣን በማገናኘት በማመሳሰል ሕዝበ ክርስቲያንን በማምታታትና በማወናበድ አስጨበጨበ እልል አሰኘ፡፡
መቸስ በጣም የሚገርም ነው ሰው እፍረት ከሌለው፣ ሕሊናውን ከሸጠ፣ ለሆዱ ብቻ ካደረ፣ እግዚአብሔርን ካልፈራ “አንተ ውሸታም! አንተ ሌባ! አንተ አጭበርባሪ!” ብሎ ሰው ሊነቅፈው፣ ሊተቸው፣ ሊያሳፍረው፣ ሊያዋርደው እንደሚችል ጨርሶ ባለማሰብና ከቁብ ባለመቁጠር በሕዝብ ፊት እንደዚህ የሌለ እና ያልነበረ ነገርን ለርካሽ ጥቅምና ትርፍ ለመቀላመድ እንዳይችል ምን ሊከለክለው ይችላል??? በዳንኤል ክብረት (በጋሌል ክስረት) ላይ የምናየው የሞራል ውድቀትና ክስረት ይሄው ነው፡፡
አጭበርባሪው አወናባጁ ቀልማዳው ዳንኤን ሆይ! ለመሆኑ ከስድስት መቶ ዓመታት በፊት እስከ ቀዳማዊ ፀፄ ኃይለሥላሴ ዘመን ድረስ ከግብጽ አንድ ጳጳስ እየተላከልን በግብጽ ቤተክርስቲያን ስር እንተዳደር ነበር እንጅ ያኔ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የራሷ ጳጳሳት ፓትርያርክና ሲኖዶስ ነበራት እንዴ ለመሆኑ???
በዚያን ጊዜ የነበረው በሃይማኖታዊ አስተምህሮ መለያየትና መወዛገብ እንጅ በፕትርክና ሥልጣን የይገባኛል ውዝግብና የሲኖዶስ መከፈል ችግር የት ነበረና ነው “ተመሳሳይ ችግር ከስድስት መቶ ዓመታት በፊት ነበረ!” ብለህ የምትቀደው አንተ ባንዳ???
ሃይማኖታዊ አስተምህሮን ምክንያት አድርጎ የሚፈጠር ችግር ደግሞ በዐፄ ዘርዓያዕቆብ ዘመን ብቻ ሳይሆን በዐፄ ሱስኒዮስም ዘመን፣ በዐፄ ፋሲልም ዘመን፣ በዐፄ ዮሐንስ 4ኛም ዘመን በዐፄ ምኒልክም ዘመን የካቶሊክና የፕሬቴስታንት ሚሽነሪዎች (መልእክተኞች) የቅባትንና የጸጋን የክህደት ትምህርት አስገብተው ተዋሕዶ ለማጥፋት በሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ያናቁሩን እንደነበር ይታወቃል፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች እንዲያውም የዚህ ግጭትና አለመግባባት ችግር ዛሬም ድረስ በቤተክርስቲያን በአንዳንድ የሀገራችን ክፍሎች አለ፡፡
እናም እንዲህ ዓይነት በሃይማኖታዊ አስተምህሮ መለያየት ችግር በዐፄ ዘርዓያዕቆብ ዘመን ብቻ ሳይሆን ከዚያም በኋላ በጠቀስኳቸውና ባልጠቀስኳቸው ዘመናት የነበሩ ሆነው እያሉና አሁን ከተፈጠረው የቤተክርስቲያናችን ሲኖዶስ የመከፈል፣ ሁለት ፓትርያርክ የመሾም ኢቀኖናዊ ችግር ጋር ጨርሶ የማይገናኝ ሆኖ እያለ “ሰው ምን ይለኛል?” የሚባል እፍረት ጨርሶ የሌለበት ይሄ የወያኔ ካድሬ ወያኔ በቤተክርስቲያን ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ በፈጠረው ችግር ተወቃሽና ተከሳሽ እንዳይሆን ለማድረግና ያለና የነበረ ቀላል ነገር ለማስመሰል በማሰብ ከዐፄ ዘርዓያዕቆብና ከአብርሃ አጽብሐ ጋር ለማገናኘትና ችግሩም በዚያ ዘመንም የነበረ ለማስመሰል መጣሩ እጅግ አሳፋሪና ነውረኛ ተግባር ነው፡፡ እውነታው ግን ጋሌል ክስረት ዋሽቶ እንዳወራው ሳይሆን የተለያየና የማይገናኝም ነው፡፡
ዳንኤል ብቻ ሳይሆን በእዚያ ዝግጅት ላይ ወረብ ያቀረቡት፣ ትምህርት ያስተማሩት ካህናትም ሁሉ ፈጽሞ ከካህናት በማይጠበቅና እግዚአብሔርን በእጅጉ በሚያሳዝን፣ አድርባይነትን ጎልቶ በታየበት መልኩ ያቀረቡት ነገር ከእውነቱ ጋር የሚጋጭ ዕብለት የተሞላ ነበር፡፡
ለምሳሌ የወረቡን ስንኝ ተመልከቱን፦
ኦ አንትሙ ሊቃነ ጳጳሳት ወመርቆሬዎስ ፓትርያርክ፤
በከመ ተጋባእይክሙ በዛቲ ዕለት እምርሑቅ ብሔር፤
ከማሁ አስተጋብአክሙ ማትያስ ፓትርያርክ፤
በኢትዮጵያ ኢየሩሳሌም ሀገሩ ለንጉሥ ዐቢይ፡፡
ትርጉሙ፦
እናንት ሊቃነ ጳጳሳትና ፓትርያርክ መርቆሬዎስ ሆይ፤
በዚህች ዕለት ከሩቅ ሀገር እንደተሰበሰባቹህ፤
እንደዚሁ ፓትርያርክ ማትያስ ሰበሰባቹህ፤
በንጉሥ ዐቢይ ሀገር ኢየሩሳሌም በሆነች ኢትዮጵያ፡፡
ዐቢይ በጥንቆላ ይሁን በምን አይታወቅም “እናቴ በሰባት ዓመቴ 7ኛው ንጉሥ ትሆናለህ ብላኝ ነበረ!” ያለውን ነው በመዝሙር ያቀረቡት፡፡
የቀረበው ስብከትም እንደ እነ መርጌታ እንደሥራቸው አግማሴን የመሳሰሉ በሽዎች የሚቆጠሩ የሕሊና ወይም የፖለቲካ እስረኞች አሁንም በግፍ ወኅኒ እየማቀቁ እያሉ ዐቢይ የሀገር ውስጥ እስረኞችን ፈትቶ፣ ከውጭ ደግሞ ወደ ሀገር እንዳይገቡ ተከልክለው የነበሩትን አባቶች ፈትቶ እንዲገቡ በማድረግ ኢትዮጵያን እጆቿን ወደ እግዚአብሔር እንድትዘረጋ እንዳደረጋት እውነታን አምታትቶ የተሰበከ የአድር ባይ ስብከት ነበር፡፡
እነኝህ ነገሮች በአውሬው አገልጋይ በወያኔ ጫናና ጭቆና ምክንያት ካህናቶቻችን በእንዴት ዓይነት የሞራል (የቅስም) ዝቅጠት፣ ውድቀትና ስብራት ውስጥ እንዳሉ የሚያሳይ ትዕይንት ነው፡፡ በወያኔ ጨካኝ ፀረ ቤተክርስቲያን ጥፍር ተፈጥርቃ ከተያዘች ቤተክርስቲያን አገልጋዮች እንዲህ ያለው ነገር የሚጠበቅ ነው፡፡ ከዚህም የከፋ ስንት ነገር አለ መሰላቹህ፡፡ ከሽህ አንድ ቢገኝ ነው በወያኔ ያልረከሰና ላለመርከስ ሲል ዋጋ የከፈለ ቆራጥ ካህን ያለው፡፡
በዚህ ዝግጅት ላይ ካህናትና የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች ቤተ ክህነት ያሳተመውን በአንድ ገጹ የወያኔ ኮከብ ያለበትን የአገዛዙ ሰንደቅ ዓላማ የታተመበት በሌላ ገጹ የቅዱስ ፓትርያርኩ የአቡነ መርቆሬዎስና የአቦይ ማትያስ ፎቶ ያለበት ሰንደቅ ዓላማ እንዲይዙ ተደርገዋል፡፡
በዚህ መድረክ ብቻ ሳይሆን በየንግሥ በዓላቱ ቤተክርስቲያን የራሷንና የመጀመሪያውን ንዋዬ ቅዱሷን የቃልኪዳን ምልክት (ትእምርተ ኪዳን) ማለትም ንጹሑን ሰንደቅ ዘፍ. 9፤8-19 አጥፍተው በየቤተክርስቲያኑ የሰይጣን አምላኪዎች ምልክት የሆነው ኮከብ ያለበትን የወያኔን ጨርቅ ካህናቱና ሰንበት ተማሪዎች ይዘውና በቤተክርስቲያን ሰቅለው ማየታችን ወያኔ የቤተክርስቲያኗን እምነትን በነጻ የማራመድ መብት ገፎና ከጣልቃ መግባት ባለፈ ራሱ ተቆጣጥሮ ምን ያህል የራሱን ዓላማና ጥቅም እያራመደባት እንዳለ ማሳያ ነው፡፡
የአውሬው የ666 መልእክተኛና አገልጋይ ወያኔ ይሄንን አርማ ቤተክርስቲያን ላይ ሰቅሎ ሕዝበ ክርስቲያኑን ለአሕዛብ ጣኦት ለሰይጣን አምላኪዎች ምልክት ሲያሰግደው “ለምን? አይሆንም! አይደረግም!” ብሎ ዋጋ የከፈለና የተከላከለ ካህን ታውቃላቹህ??? ይሄንን ያህል ናቸው የእኛ ካህናት!!!
ሰሞኑን እንኳ በጅጅጋ የኪዳነ ምሕረት፣ የቅዱስ ሚካኤል፣ የቅዱስ ገብርኤል፣ የቅዱስ ጊዮርጊስ፣ የቅድስት አርሴማ አምስት ቤተክርስቲያን በወያኔ ሸፍጥ ሲቀጠል፣ አገልጋይ ካህናቱና አብረው የነበሩ ምእመናን በአሰቃቂ ሁኔታ ተገለው አስከሬናቸው እንዲቃጠል ሲደረግ “የእኛ ጉዳይ  ነው!” ብለው ይሄንን አረመኔያዊ ድርጊት ማውገዝና ሐዘናቸውን መግለጽ ያልቻሉ ከሐድያን የወያኔ አገልጋዮች ናቸው፡፡ ዋጋቸውን ያገኛሉ!!!
እስኪ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለአውሬው የሰገዱትንና እያገለገሉት ያሉትን የረከሱ፣ የወደቁ፣ የጠፉ ካህናትን ከቅድስት ቤተክርስቲያን ምንጥር አድርጎ አጥርቶ የራሱ የሆኑና የታመኑ፣ ቆራጥ፣ ጽኑና ትጉ አገልጋይ ካህናትን፣ ጠባቂ እረኞችን ይስጠን!!! አሜን!!!
ድል ለቅድስት ቤተክርስቲያን!!!
Filed in: Amharic