>
5:13 pm - Monday April 19, 3548

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ ከአርበኞች ግንቦት 7 አመራሮች ጋር ተወያዩ

ቢቢሲ አማርኛ

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ ”ግንቡን እናፍርስ፤ ደልድዩንም እንገንባ” በሚል መሪ ቃል በአሜሪካ ጉዟቸውን በማገባደድ ላይ ናቸው። በቆይታቸው በአሜሪካና በኢትዮጵያ ተከፋፍለው የቆዩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሲኖዶሶች ጋር በመገናኘት ሲኖዶሶቹ በመዋሃድ አንድ ሆነው እንዲሰሩ ማስማማት ችለዋል።

ባሳለፍነው አርብ ደግሞ በአሜሪካ ከሚገኙ የተለያዩ የፖለቲካ ፖርቲዎች ጋር ውይይት አድርገው ነበር። በውይይቱ ላይ ተሳታፊ የነበሩ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ጥያቄዎች አቅርበው ጠቅላይ ሚንስትሩ ምላሽ ሰጥተውባቸዋል።

ከዚህም ባለፈ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአርበኞች ግንቦት 7 መሪ ብርሃኑ ነጋ (ዶ/ር) ጋር ተገናኝተው ተነጋግረዋል። ለአንድ ሰዓት ያህል የቆየው ውይይት የትውውቅና አንዳንድ መሠረታዊ በሚባሉ ጉዳዮች ላይ ስምምነት የተደረሰበት እንደነበረ የግንባሩ የዓለም አቀፍ አመራር የዉጭ ግንኙነት ኃላፊና የንቅናቄዉ ምክር ቤት አባል አቶ ነአምን ዘለቀ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

ከዚህ አጭር ውይይት በኋላ ሌላ ሁለተኛ ዙር ንግግር እንደነበረም አቶ ነአምን ተናግረዋል።

ይኸውም ቅዳሜ ማታ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ አርፈውበት ነበር በተባለው ‘ወተር ጌት’ ሆቴል 12ኛ ፎቅ ላይ የተካሄደው ነው። በዚህ ውይይት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ጨምሮ አምስት ከፍተኛ የአርበኞች ግንቦት 7 አመራሮች የተገኙ ሲሆን ከመንግሥት ወገን አቶ ለማ መገርሳ ተገኝተዋል።

ከሁለት ሰዓት በላይ የዘለቀው ይህ ውይይት ወዳጅነትና መግባባት የሰፈነበት ነበር ብለዋል አቶ ነአምን ለቢቢሲ። ሆኖም የውይይቱን ዝርዝር ጉዳዮች ከመናገር ተቆጥበዋል።

አሁን በሃገሪቱ እየታየ ያለውን ለውጥ ግንቦት 7 እንደሚደግፈውና ኢትዮጵያን ወደ ሃቀኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለማሸጋገር በሚደረገው ጥረት ትብበር እንደሚያደርግ ገልጸዋል። በተጨማሪም ሀገር ቤት ሲንቀሳቀሱ የነበሩ አባላቱን ወደ ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል የማምጣትና የማደራጀት ዕቅድ ላይም ሰፋ ያለ ውይይት መደረጉ ተመልክቷል።

ግንባሩ በሰላማዊ መንገድ ወደ ሃገር ቤት የሚገባበት፤ የመሪዎቹን የደህንነት ጉዳይ ዋስትና የሚያገኝበት ሁኔታዎች ላይ ውይይትም ተደርጓል። በተጨማሪም በኤርትራ በረሀ ላይ የሚገኙ የሠራዊቱ አባላት ወደ ሰላማዊ ሕይወታቸው የሚመለሱበትን ሁኔታም በቅድሚያ ማመቻቸት እንደሚያሻ ተናግረዋል። አቶ ነአምን በአጠቃላይ ውይይቱን “በጣም ውጤታማና በጣም ፍሬያማ” ሲሉ ነው የገለጹት።

በቀጣይ በአገሪቱ በሚደረገው ምርጫ ስለመሳተፍ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ተነጋግረው እንደሆነ የተጠየቁት አቶ ነአምን “እሱ ቅድሚያ የምንሰጠው ጉዳይ አይደለም” ካሉ በኋላ “ለኛ ዋናው ነገር አሁን የተጀመረውን ለውጥ መደገፍና ዴሞክራሲያዊ ተቋማት እንዲገነቡ ማገዝ ነው” በማለት እንደ ፖለቲካ ፓርቲ ለሥልጣን መፎካከር አሁን አጀንዳቸው እንዳልሆነ ተናግረዋል።

የድርጅቱ ሊቀመንበር ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ወደ አገር ቤት የሚመለሱበት የጊዜ ሰሌዳ ተቀምጦ እንደሆነ ከቢቢሲ የተጠየቁት አቶ ነአምን ጊዜውን በትክክል ማስቀመጥ ቢቸገሩም ምናልባት በሳምንታት ሊሆን እንደሚችል ጥቆማ ሰጥተዋል።

አርበኞች ግንቦት 7 ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በተደረጉ ጉዳዮች ዙርያና በመጪው የድርጅቱ እቅድ ላይ ዛሬ ማምሻውን ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል

Filed in: Amharic