>

ኦነግ ከመንግስት ጋር የተጀመረውን የሰላም ውይይት ለማሳካት ጊዜያዊ የተኩስ አቁም አወጀ

ኦነግ ከመንግስት ጋር የተጀመረውን የሰላም ውይይት ለማሳካት ጊዜያዊ የተኩስ አቁም አወጀ
F.B.C
አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 5፣ 2010 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የተጀመረውን የሰላም ውይይት ለማሳካት ግዜያዊ የተኩስ አቁም ማወጁን አስታወቀ።
ግንባሩ ዛሬ ባወጣው መግለጫ፥ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለውን የፖለቲካ ችግር በሰላማዊ መንገድ መፍትሄ እንዲበጅለት እንደሚፈልግ ገልጿል።
በቅርቡ በግንባሩ ሊቀ መንበር በሚመራ የኦነግ የልዑካን ቡድንና በኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ መካከል በተደረገ ውይይት ያለውን ችግር በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ሲደረግ የነበረው ጥረት የሚያበረታታ ነው ብሏል።
በመንግስት እና በግንባሩ መካከል የተጀመረውን የሰላም ንግግር መንግስታት፣ ህዝቦችና ሰላም ወዳዶች የሚሹት መሆኑን እንደሚገነዘብም ግንባሩ ገልጿል።
የተጀመረውን የሰላም ንግግር ወደፊት ለማራመድና ለማሳካት ይረዳል በሚል እምነት በጊዜያዊነት ተኩስ ማቆሙን በመግለጫው አስታውቋል።
ለጊዜው ይህ የተኩስ ማቆም አዋጅም የተጀመረው ንግግር የሚጠበቀውን ፍሬ ያገኛል ብሎ እንደሚያምንም ገልጿል።
Filed in: Amharic