>

አስቴር በዳኔ ከቤተ-መንግስት ስልጠና ለምን ተባረረች? (ክንፉ አሰፋ)

አስቴር በዳኔ ከቤተ-መንግስት ስልጠና ለምን ተባረረች?

ክንፉ አሰፋ

ወዲ ብርሃነ “ኮሽ ባለ ቁጥር (በህወሃት) ማሳበብ አስቂኝ ነው” ብሎናል። ልክ እንደ ቦስተን ማራቶን፤  ንጹሃን ዜጎች ላይ ቦንብ ሲወረወር፤ ሌላው ይጨነቃል፤ ኮካ ደግሞ ይስቃል። የቦንብ ፍንዳታ በተሰማ ቁጥር ሕዝብ የነሱን የፈስ ቡክ ገጽ ለመዳሰስ የሚሯሯጠው የተለመደ ፍንጭ ስለሚሰጠው ብቻ መሆኑን እንኳ ገና አልባነነም። የመረጃ ፍንጭ መስጠታቸው ባልከፋ፤ ግና ጉዳዩን ማን መመርመር እንዳለበት ኮካዎች የሚወስኑበት ዘመን፤  እንደ ፈርኦን አሽከሮች የባህር ውሃ ከበላው ወራት አለፉ።

ዘንግተነው ካልሆነ በስተቀር፤  በሟቹ ግዜም፤ “ነገ መርካቶ አካባቢ በአስር ሰዓት ቦንብ ይፈነዳል” እያሉ በብሄራዊ ቴሌቪዥን ይነግሩን ነበር። የአበሻ ዘር በወቅቱ ያስጨንቀው የነበረው ታዲያ የቦንቡ መፈንዳት ሳይሆን፤ ሊታሰሩ እቅድ የተያዘላቸው “አሸባሪዎች” ጉዳይ ነበር። ፍቅር እንደ ወንጌል እየተሰበከ ባለበት በዛሬ ዘመን ደግሞ የጅቦቹን የልብ ትርታ የሚለካልን ቴርሞ ሜትር የኮካዎቹ ገጽ ሆኗል።   

“የቀን ጅቦች” የተሰኘው ነጠላ ስም እንደ ሰደድ እሳት ተለቆ፤ ጅቦቹም ያሻቸውን ሲያደርጉ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁንም ፍቅርን ነው የሚሰብከው። እሳት ጫሪን ከመቅጣት ይልቅ፤  እነሱ የሚጭሩትን እሳት እየዞረ ማጥፋት የለት ስራው ስላደረገ። ይህንን በማድረግ ትእግስቱን ጫፍ ቢያመላክታቸውም እነሱ ግን በንቀት ያዩት ይመስላል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ከኪነጥበብ ባለሙያዎች ጋር ውይይት አደረጉ የሚለውን መልካም ዜና ገና ሰምተን ሳንጨርስ የማግለል ፖለቲካ ጉዳይ ተከተለ። ተስፋ አስቆራጭ ዜና!

የአስቴር በዳኔን ከቤተ-መንግስት መባረር ስንሰማ፤ የዚያ ቫይረስ ተሸካሚዎች በኪነጥበብ ስም መስረጋቸውን ያመላክተናል። ክስተቱ ያሳዝናል። ድርጊቱ በየትኛውም መስፈርት ቢለካ፤… የተፈለገው ምክንያት ቢደረደር፤  ስህተት ያለመሆኑን አያስረግጥም።

ማቹ ጠቅላይ ሚንስትር ኪነ ጥበብ ባለሞያዎችን ባናገሩበት ግዜ  “ማን ይጠራ፧ ማን ይቅር፧ ማን ምን ይጠይቅ?” ሸፍጥ ሰዓሊ ስዩም አያሌው “ሰራዊትና ሰራዊቶቹ” በሚል ርዕስ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ አስነብቦን ነበር። አቶ መለስ ከሰራዊት ፍቅሬ የወርቅ ብዕር ተሸልመው ነበር። ጋዜጠኞችን በማሰራቸው እና በፕሬስ አፈናቸው። አሁንም እነዚሁ ሰዎች ቆባቸውን ቀይረው አዛዥ ሆነውልናል።  

“ግዜው የመደመር ነው፣ ግዜው የምህረት ነው፣ ግዘው የይቅርታ ነው፣ ፍቅር ያሸንፋል።”.. ካልን አንዱን የበኩር ሌላውን ደግሞ የእንጀራ ልጅ የምናደርግበት ምክንያት አይኖርም።  “አስቴር በዳኔ ለብቻዋ እውነትን የደፈረች ልጅ ተመርጣ ለምን ከአዳራሹ እንድትወጣ ተደረገ?” የሚለው ጥያቄ ለብዙዎቻችን እንቆቅልሽ ሆኖብናል። ከጅቦቹ ጋር እየተሞዳሞዱ የማስታወቂያ ስራውን ጭምር ጠቅልለው የያዙት ግልገል ጅቦች እያሉ፤ ይህች ልጅ ለምን? “ኢትዮጵያዊ አይደለሁም” ይል የነበረው፤  ኦነግን ሳይቀር በሁለት እጃቸው ተቀብለው ያስተናገዱ መሪ፤ ሃስዝብን በነጸ የገለጸ ዜጋ ላይ የማግለል ፖለቲካ ይሰራሉ ብለን ለመገመት ይከብደናል። የቀን ጅቦቹ ያሉት ሁሉም ስፍራ ነው።

ዛሬ ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያዊነት የሚቆረቆር መብዛቱ በጎ ነው። ከነፈሰው የሚነፍሱ ግብዞች፤ ተቆርቋሪዎች እኛ ብቻ ነን ሲሉ ማየት ግን ያምማል።

አንዳንድ ቀላጆች እንደሚሉት አስቴር በዳኔ የጠቅላዩ ስልጠና አያስፈልጋትም፤ እስዋ አስቀድማ ተደምራለች እያሉ የሚነግሩን ቁም ነገር እንደተተበቀ ሆኖ፤ ጉዳዩን ከማድበስበስ ይልቅ ጸሃይ ላይ አውጥቶ ማስጣቱ ትምህርት ይሆን ይሆናል።

የድብቅ ፖለቲካ አይኖርም ተብለናል። ሃገር የምትተዳደረው ገንዘብ እና ጥላቻ ባሰከራቸው ካድሬዎች ሳይሆን በፍቅር እና በህግ እንደሆነም ተነግሮናል። በጠቅላይ ሚንስትሩ የመደመር ራዕይ ላይ ጥርጣሬ እንዲፈጠር፤ ሌሎችን ተስፋ የሚያስቆርጥ፤  ጥላሸት የሚቀቡ ወያላዎች የሚሰሩት ተንኮል እንዳለ ይሸታል።

አርቲስትዋ በቤተ-መንግስት ደብተር እንጂ ድማሚት ይዛ እንዳልገባች እርግጥ ነው። አስቴር ከሌሎች አርቲስቶች የተለየ ሃሳብ እንዳለትም ይታወቃል። የተለየ ሃሳብ ያለው ዜጋ ደግሞ አይደመርም የሚል ደንብ አልወጣም። የአርቲስትዋ ሃሳብ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ራዕይ  ጋር የሚጻረርም አይደለም።

ከዚህ ቀደም፤ ህወሃት አርባኛ አመቱን ሲያከብር፤ በደደቢት በረሃ ውስጥ ተገኝታ እንደሌሎቹ አላጎበደደችም። ይልቁንም በህወሃት አናት ላይ የሃሳብ ቦንብ አፈንድታ እንደነበር እናስታውሳለን። በዚያ በአስፈሪ ድባብ ውስጥ ማይክ ጨብጣ፤  “እውነትን መናገር እወዳለሁ። … በእርግጥ የፖለቲካ ሰው አይደለሁም። … እናንተስ በምርጫ ትወርዱ ይሆን?” ብላ ጠየቀች።

“ህዝብ ‘አጎብዳጆች’ ይለናል።” አለች አስቴር በዳኔ። የፖለቲካ አየሩ እንደዛሬው ጸዳ ያለ አልነበረም። የኪነ-ትበብ ሰዎቻችንን መፈተኛ ግዜ ነበር። ከአስቴር ውጭ ጥርስ የሚያስነክስ አይደለም ተራ ጥያቄ እንኳን የጠየቀ አርቲስት አልነበረም። ሁሉም አሞጋሽ ነበር።

አስቴር በአለቆቻቸው ላይ እንደዚያ አይነት የድፍረት ቃል በመናገርዋ አርቲስቶቹ እንዳኮረፏት ሰምተን ተደንቀን ነበር። እነዚያ አሽቃባጮች ዛሬ የፊት ተሰላፊ ሆነው እስዋን ሲገፏት ሰምተን ዝም ልንል እና ልናዝን አይገባም። የደደቢቱ ድፍረትዋ እስካሁን ብዙ አስከፍሏታል። የአሁኑ ድርጊታቸው ደግሞ፤  የቀን ጅቦቹ ሆን ብለው ሞራልዋን ለመጉዳት ስራ እንደጀመሩ ቢያመላክትም፤ ኢትዮጵያ ሕዝብ በሚያከብራት እና በሚመሰክርላት ስለሆነች ልትኮራ ይገባታል። ምክንያቱም የሃቅን መንገድ መረተች እንጂ፤ ያላግባብ ባለሃብት እንደሆኑ አርቲስቶች አጎብድዳ መኖርን አያቅታትም። ለቀን ጅቦች ዘንድሮ የሙስና በር የተዘጋ ይመስላል።

አስቴር ከአዳራሹ እንድትወጣ ተደረገ። ስልጠናው ቀጠለ። ኪነ ጥበብ በኢትዮጵያ ውስጥ በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝና የንፅፅር ትምህርት ሰጥተዋል ተብሏል። ስልጠናውን የወሰዱት አርቲስቶች በቴሌቭዥን የሰጡዋቸውን ቃላትም ሰምተናል። ራያና ቆቦ!

የዶክተር አብይ ሰዎችን ለስልጠና ሲጠሩ የሰልጣኞችን እውቀት፤ የግንዛቤ እና የትምህርት ደረጃ መጥነው ቢያቀርቡ ይመረጣል።  ትምህርቱ እንዲዋሃዳቸው ምንም የእንግሊዝኛ ቃልባይጠቀሙ ደግሞ መልካም ነው። ለምሳሌ እነ ሳሞራን ሲያሰለጥኑ ትምህርቱን ያዘጋጁት በእንግሊዝኛ ቋንቋ ስለነበር ሰዎቹ ገለጸውን ለመረዳት  እንደተቸገሩት በግልጽ ይታያል።

የአርቲስት ሰርጸ ፍሬ ሰንበት እና የተዋንያን ሰለሞን ቦጋለን ከስልጠናው በኋላ ተጠይቀው የሰጡትን መልስ ብቻ ሰምቶ አርቲስቶቹ ስልጠናውን እንዳልተከታተሉት መገመት ይቻላል።  ሰለሞን ቦጋለ እንዴት መስራት እንደሚገባን አቅጣጫ ጠቋሚ ትምህርት ነበር ሲል። ሰርጸ ግን ከኮሚኒስት ተኮር ጥበብ ነጻ ሆነን መስራት እንደሚገባን … ለምሳሌ ግድብ ሲሰራ ስለ ግድብ ዝፈኑ ከሚል ዕዛ ይልቅ አርቲስቱ በራስ ፈጠራ እንዲመራ የሚል አስተምሮት እንደሆነ ነግሮናል።

ከመጣው ጋር ማሸርገድን አቁሙ ሲሉ ምክር እንደሰጡም ምንጮች ገልሰዋል። በተለይ ድምጻዊ ጌትሽ ማሞ እና ቴዎድሮስ ተሾመን በስም ጠርተው “አብረን አድገናል። ጓደኛ ነን።  አሁን ቤተሰብ ነን.. ምናምንም ማለታችሁን አቁሙ ማለታቸውን ቃሊቲ ፕረስ ዘግቧል። እንደ ዶ/ር አብይ ገለጸ ሁሉም የኪነጥበብ ሰው እኩል ነው መታየት ያለበት።

እርግጥ ነው ኢትዮጵያ ውስጥ ስሙን የተሸከመ ሁሉ አርቲስት አይደለም። ከጥበብ ይልቅ ንዋይ ያስቀደመውን ሁሉ አርቲስት አይባልም። “ገንዘብን ሳይሆን ጥበብ አስቀድሙ” ይላሉ ጠቅላይ ሚንስትሩ።  እንደዚህ አይነቱ አስተምሮት እንደ አስቴር በዳኔ ላሉ አርቲስቶች አያስፈልጋቸውም።

Filed in: Amharic