>
5:14 pm - Thursday April 20, 5843

የስብሃት ምርኩዝ (በፍቃዱ ሞረዳ)

ተወርቶ ያላለቀ ስንት የሀገርና የሕዝብ ጉዳይ እያለ ስለግለሰዎች ለማዉሳት ጊዜ ማጥፋት አግባብ አለመሆኑን ብናምንም የአንዳንድ ግለሰዎች ነገረሥራ ግን ሳንወድ በግድ እናሽኮረምመዉ ዘንድ ይነካካናል፡፡
   ይህ ሰዉ የማዉቀዉ ወያኔ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ 41 መምህራንን (ዶክተሮችና ፕሮፌሰሮች) ‹‹ በብቃት ማነስ›› ካባረረችበት ጊዜ ጀምሮ ነዉ፡፡ እኒህ ሰዉም ከተባረሩት መምህራን መሀከል አንዱ ነበር፡፡
 ነፍሱን ይማረዉና አቶ አብርሃም አበበ ‹‹ አቡጊዳ›› በሚል ስም ባቋቋመዉ ሲቪክ ድርጅት ዉስጥ የአድቮከሲ መኮንን ሆኖ ከተቀጠረ በኋላ በሥራ አጋጣሚ መቀራረብ ፈጠርን፡፡ መተዋወቅም ጀመርን፡፡ኦሎምፒያ አካባቢ እህል ዉኃ ሳንባባል ቀረን?
       NDI (ናሽናል ዲሞክራቲክ ኢንስቲቱት) የተሰኘዉ የአሜሪካ ድርጅት (በኋላ መለስ ከኢትዮጵያ ያባረረዉ) በሰጠዉ ዕድል መሰረት ለሥልጠና አሜሪካ ሄደ፡፡ በኢሕአፓዎች ድጋፍ ጥገኝነት አግኝቶ አሜሪካ ቀረ፡፡ ያኔ የአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ ጋዜጠኛ የነበረችዉን ሚሚ ስብሃቱን ጠበሰ፡፡ ተጋቡም፡፡
     የመለስና የስዬ ቡድን ግብግብ ሰሞን ከመለስ ደጋፊዎች ሰልፍ ዉስጥ ራሱን አገኘ፡፡ ከዲያስፖራዉ ጋርም ተደባበሩ፡፡ ከእነገነነ አሰፋ ጋር በመሆን ‹‹ back to the Nation›› የሚል መፈክር ይዘዉ ወደሀገር ተመለሱ፡፡ ባለቤቱም ገባች፡፡ ደርግ የወረሰዉን የአባቷን መናፈሻም በጥሬ ገንዘብ አስመለሰች፡፡ (በአንድ ሹክሹክታ ምክንያት ቢሯችን ድረስ መጥተዉ ‹‹ካልተደባደብን›› ያሉበትን ጉዳይ ተዉኩት፡፡ እሱና ገነነ፡፡)
  የጅጅጋዉ አራዳ በምርጫ 97 ወቅት ‹‹ኢፍቲን›› የሚባል የግል ጋዜጣ መስርቶ ተቃዋሚዎችን ጭቃ ሲቀባ ቆየ፡፡ በኋላም የራዲዮ አየር ሰዓት ተሰጣቸዉና ‹‹ ዘሚ›› (ዘርይሁንና ሚሚ) ተብለዉ ተከሰቱ፡፡
    ከዚያ የስብሃት ነጋ በጎ ፈቃደኛ ረዳት ሆኖ ሲያገለግል እንደነበር ወሬ እንሰማ ነበር፡፡ አገልግሎቱ ዘርፈብዙ ነዉ አሉ፡፡ አንዳንዱ ባለጌ ነገር ስለሚያናግረን ትተነዋል፡፡
 የእነአብይ አብዮት ከመጣ ወዲህ ሆድ ቁርጠት ከያዛቸዉ ጥቂት የማይባሉ ሰዎች መሐከል አንዱ ነዉ፡፡ (ባለቤቱ ለጤና ምርመራ ዲሲ ነበሩ ወይም አሉ)
     አሁን በቀደም ዕለት የግንቦት ሃያ በዓል መኸለ ላይ ሲከበር የኢሕአዴግ ነባር ታጋዮች ተሰብስበዉ ነበር፡፡ ትዝታ ሊያወጉ፡፡ ጥቂትም ሊዶልቱ፡፡ ይህ ሰዉ ከነባር ታጋዮችም በተለየ ሁኔታ ስብሃት ነጋ ጎን በክብር ተሰይሞ ሳየዉ ሊገርመኝ ሞከረ፡፡ ሽማግሌዉ ስብሃት ‹‹ዘሪሁን›› የሚባል ምርኩዝ ተገዝቶላቸዉ ካልሆነ በቀር እዚያ ሽማግሌዎቹ ሽፍቶች መሐል ምን ሊሰራ እንደገባ እንጃለቱ፡፡ ብቻ ይሁን፤ በሰዉ እንጀራ ምን ጥልቅ አደረገን? እንዲያዉ ለነገሩ እንጂ…
   የያኔዉ ወዳጄ ዘሪሁን ተሾመ የሰጠኝን ምክር ተቀብዬ ከስደት ቀርቼ ብሆን ኖሮ ከአቃጣሪነትና ከደላላነት አልፌ የአንዱ ሽማግሌ ሽፍታ ምርኩዝ ሆኜ ዓለሜን እቀጭ አልነበር? ወይ ጮሌ አለመሆን፡፡
Filed in: Amharic