>

ስንት አከሰሩን? (ጌታቸው ሽፈራው)

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በአቶ አንዳርጋቸው እስር ብቻ 11 ቢሊዮን ዶላር እንደቀረ ተናግረዋል። 11 ቢሊዮን በጊዜው   ዶላር ተመን ወደ 308 ቢሊዮን ብር ይደርሳል!
አንድ ፋብሪካ ውስጥ የሚሰራ ወዳጄ  እንዳጫወተኝ፣ አንድ  እስከ 6 ሺህ ሰራተኛ የሚቀጥር  ፋብሪካ ለመገንባት እስከ 2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ይጨርሳል። 308 ቢሊዮን ብር ደግሞ 123 ፋብሪካዎችን ይገነባል። እነዚህ ፋብሪካዎች ደግሞ 739, 200 ያህል ሰራተኞችን ይቀጥራሉ። እነዚህ ሰራተኞች በአማካይ 3 ቤተሰብ ቢያስተዳድሩ 2,196,600 ህዝብ ኑሮ ተሻሻለ ማለት ነው።  123 ፋብሪካዎች ሲያመርቱ ለህዝብ የሚያበተክቱትን አቅርቦት፣ የውጭ ምንዛሬ በቀላሉ ማሰብ ይቻላል። ለሀገር ጥቅም ቢውል ኖሮ ከሚል መነሻ
ይህ በአንዳርጋቸው  እስር ብቻ የቀረ ነው። ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በዓለም ደረጃ 6 ጊዜ ተሸልሟል። እኛ የሰማነው እስክንድር መሸለሙን እንጅ መንግስት የተቀጣውን አይደለም። ርዕዮት ስትሸለም፣ ውብሸት ሲሸለም መንግስት የተከለከለውን ብድርና እርዳታ አልሰማንም።
ፕሮፌሰር አስራት፣ ዶ/ር መረራ፣ የቅንጅት አመራሮች፣ ብርቱካን ሚዲቅሳ፣አንዱዓለም አራጌ፣ በቀለ ገርባ፣ ጋዜጠኛ ተመስገን፣  አቡበክር አህመድ፣
ዶ/ፍቅሩ ማሩ፣ ማሙሸት አማረ፣ ኦኬሎ አኳይ፣ ስንት ፖለቲከኞች ጋዜጠኞች፣ባለፉት ሁለት አስርት አመታት  ኦነግ፣ ግንቦት 7 እየተባሉ የታሰሩትን ፍቱ ሲባሉ አሻፈረኝ ብለው አይሰሩበትም እንጅ ስንትና ስንት ፋብሪካ የሚያሰራ  ገንዘብ ኦና ቀርቷል።
አንዳርጋቸው የብሪታኒያ ዜጋ እንደሆነ ሁሉ ኦኮሌ ኖርወይ ነው፣ የስዊድን ጋዜጠኞች ታስረው ነበር፣ ዶክተር ፍቅሩ ማሩና ሌሎች የውጭ ሀገር ዜግነት ያላቸው ታስረው ነበር። በዚህ ሁሉ እስር ዲፕሎማሲ ተበላሽቷል፣ ሰብአዊ መብት ተቋማት ብድርና እርዳታ እንዲታገድ አመልክተው ተሳክቶላቸዋል።
በአንዳርጋቸው እስር ምክንያት የታጣውን ዶ/ር አብይ ስለሆኑ ገለፁት። መለስ ዜናዊና ጓደኞቹ አልገለፁትም እንጅ ባሰሯቸው ንፁሃን ምክንያት ከዚህ ሁለት፣ ሶስት፣ አራት እጥፍ  ብድርና እርዳታ ታግዷል።
በጣም ቀለል አድርገን፣ ለአንድ አንድርጋቸው የታጣውን መሰረት አድርገን፣ ያ ሁሉ ንፁሃን ሲታሰሩ ከአንዳርጋቸው አራት እጥፍ ቢታገድ ብለን ብናስብ እንኳ ወደ 500 ግዙፍ ፋብሪካዎች  ከስረዋል። 3 ሚሊዮን የስራ እድል ኦና ቀርቷል ማለት ነው። 9 ሚሊዮን ሕዝብን ማኖር የሚችል አማራጭ ወና ቀርቷል ማለት ነው።
ከዚህ ላይ መለስ ስዊዝ ያስቀመጠው 55 ቢሊዮን፣ አባይ ያጠፋው 77 ቢሊዮን፣ አዜብና ሰምሃል ተገኘባቸው የተባለውን ስንጨምር ደግሞ ይህን ሀገር ነቀዝ ሲበላው እንደኖረ ለመረዳት አያዳግተንም!
 ነቀዝ!
(ይህን ሁሉ የለውጥ ሀይል አስረው ያስቀሩት ዲሞክራሲ፣ ዲሞክራሲ ሲከስር፣ ሰብአዊነት ሲገሰስ የቀረውን እድገት ማሰብ እጅጉን ከባድ ነው! ባይገመት ይሻላል)
Filed in: Amharic