>
5:13 pm - Tuesday April 20, 4280

" ፖሊሶቹ የኢትዮጵያ ወታደሮች ናቸው"?  ወይስ "የኢየሱስ ወታደሮች?"  (ዘመድኩን በቀለ)

~ ሕገ መንግሥቱ ሳይነገረን ተቀይሮ ይሆን እንዴ ?
~ እነእስክንድርን ያሳሰር ኮከብ አልባ ሰንደቅ ዓላማ ፖስተሩንና ሕግ አስከባሪ ተብዬዎችን የማያስጠይቅበት የህግ አግባብ ይኖር ይሆን?
በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 11 ላይ ” የመንግሥትና የሃይማኖት መለያየት” በሚለው አንቀጽ ሥር ንዑስ አንቀጽ 1-3 የተቀመጠውን ሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌ ስንመለከት እንዲህ የሚል ቃል እናገኛለን “መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው፡፡ መንግሥታዊ ሃይማኖት አይኖርም፡፡ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፡፡ ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፡፡” የሚልና በመንግሥትና በሃይማኖት መካከል የፈንጂ ወረዳ የገነባ ሕግ ተደንግጎ እናገኛለን። ታዲያ ይኼ ሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌ በህውሓት መራሹ አገዛዝ መሬት ላይ ወርዶ በተግባር ላይ ሲውል አይታይም።
አሁን በመሬት ላይ የሚታየው የመንግሥት ፖሊሲ የሚያሳየን ግን ሌላ ነገር ነው። በተለይ የደቡብ ክልል ህዝብ “በአነስተኛና ጥቃቅን የተዳራጁ” ወጣቶች “ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ መጋቢና፣ የእግዚአብሔር ሰው የሚል ስያሜን በመላበስ በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ስም የተጠመቁ ማፍያዎችን አደራጅተው የደቡብን ምስኪን ህዝብ በየአዳራሹ እየሰበሰቡ የድኻውን ህዝብ በህልሙ ቅቤ እያጠጡ ሚልየን ብርም እያስቆጥሩት ጢባ ጢቤ እንዲጫወቱበት ህገመንግሥታዊ ፈቃድ ተሰጥቷቸው ያለተቆጪ ተንቀባረው እንዲኖሩ ተደርገው ይታያሉ።
በደቡብ ክልል የሚኖሩ ዜጎች በጅምላ ሁሉም ባለ ራዕይ ሆነዋል። ሁሉም ሰይጣን አባራሪ ሆነዋል። ሁሉም ፈዋሽ ከመሆኑ የተነሳ የሚፈወሱ ሰዎች እጥረት እየገጠማቸው መምጣቱ እየተነገረ ነው። በደቡብ የመላእክትን ዝማሬ በሞባይል ስልካቸው ለየዋሑና ” ማሞ ቂሎ ” ህዝብ የሚያሰሙ ነብያት ተፈጥረዋል። እግር የሚያስረዝሙ ፣ ቦርጭ የሚያጠፉ፣ እጅ የሚያስረዝሙ ፣ የስልክ ቁጥር በቃላቸው የሚናገሩ “ቴሌ ነብያቶችም ” እንደጉድ እንደ አሸንም ነው የፈሉት።
በጫማጥፊና በቴስታ አጋንንት የሚያባርሩ። የባንክ ብድር በጸሎት የሚሰርዙ ፣ ለባርሴሎናና ለአርሰናል ተጫዋች በጸሎታቸው የሚሸጡ። አሜሪካ መግቢያ ቪዛ፣ የአሜሪካ መኖሪያ ፈቃድና የአሜሪካ ዜግነት ስማቸውን ለጠሩ አማኞች ያለ ምንም አንጃ ግራንጃ እንደሚያሳኩ፣ 1 ሊትር ውኃ የባረክነው ነው ብለው 100 ብር፣ የጉሎ ዘይት 500 ብር የሚሸጡ ነጋዴዎች ተከስተዋል። በገስት ሃውስ ለሴቶች ብቻ ሌሊት ሌሊት ብቻ ለብቻ የሚጸልዩ፣ የሞተ ለሰው የሚያስነሱ ብቻ እንደባለዛር በእሳት እንደሚገረፍ ሰው የሚንቀጠቀጡ እሳት የበሉ እሳቶች እሳት ሆነው ህዝቡን እሳት ለቀውበት እያነደዱት ይገኛሉ።
ይኼ እዳው ገብስ ነው። የሆነ ጊዜ ሲባነንበት ይቆማል። እኔ የሚያስፈራኝ ሌላው ነገር ነው ። እሱ ነው የከፋው።
በቪዲዮው ላይ የምታይዋቸው የደቡብ ክልል ፖሊሶችና የትራፊክ ፖሊሶች ናቸው። የካራቲስቱ የነቢይ ኢዩ ጩፋ ደቀመዛሙርት ናቸው። የደንብ ልብሳቸውን እንደለበሱ ” የኢየሱስ ወታደር ነኝ ” በሚል ዝማሬ ወታደራዊ ትርኢት ሲያሳዩ ነው የሚታዩት። በእልህ ፣ በወኔ ፣ እሳት ለብሰው እሳት ጉርሰው ነው የሚደንሱት።
እንጠይቃለን ። እንዲያው ለመሆኑ በሕገ መንግሥቱ ላይ በሠፈረው ደንብ መሠረት ወታደሩ ተገዢነቱ ለፓስተር ኢዩ ጩፋ ነው ወይስ ለሕገ መንግሥቱ?  እንዲህ ነርቨስ ሆኖ በፓስተሩ መድረክ ላይ ብንን ብሎ የሚውረገረግ ፖሊስ የእምነቱ ተቃራኒ የሆኑ ዜጎችን ሲያገኝ እንዴት እንደሚያስተናግድ ታይቷችኋል? በወላይታና በአዋሳ ዩኒቨርሲቲ የመብት ጥያቄን ባነሱ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ላይ ” ጭካኔ የተመላበት ዘግናኝ ጭፍጨፋ” በመፈጸም ” ኢየሱስ ጌታ ነው ” እያሉ የተማሪዎችን ጭንቅላት በመፈንከት እጅና እግራቸውን በመስበር ጌታቸውን ያስደሰቱት ፖሊሶች እኮ እነዚህ ” የኢየሱስ ወታደር ነን” ብለው በአደባባይ መፈክር የሚያሰሙት ወታደሮች እኮ ናቸው።
ወዳጄ ራሳቸው ያወጡት ሕገመንግሥት ራሳቸው ሲጥሱት እያየህ ለምን ብለህ ስትጠይቅም መልሱ የታወቀ ነው “
ለማንኛውም 30 ሺህ የዐማራ ነገድ ከጉራ ፈርዳ የተፈናቀለውና የተገደለው በእነዚህ ” የኢየሱስ ወታደሮች ” ነው። ” ዐማራና ኦርቶዶክስ አከርካሪው የሚሰበረውም በእነዚህ ” የኢየሱስ ወታደሮች” ነው። #መክት_ዐማራ !
 ውድ ኦርቶዶክሳውያን ሆይ ! ነገ ለሚመጣው የከፋ ቀን ከወዲሁ መዘጋጀቱ አማራጭ የሌለው አማራጭ ነው። ከላይም ከታችም ” በኢየሱስ ወታደሮች ” የገና ዳቦ ትሆን ዘንድ ተዶልቶብሃልና በጸሎትም ፣ በትምህርትም መዘጋጀቱ አይከፋም።
ሻሎም !  ሰላም ! 
ዘመድኩን በቀለ ነኝ
ግንቦት 17/2010 ዓም
ከራየን ወንዝ ማዶ ።
Filed in: Amharic