>
5:13 pm - Sunday April 19, 5220

ጄኔራል ሰዓረና ጋዜጠኛ እስክንድር – ከኢየሩሳሌም አርአያ

ሰኔ 1 ቀን 1997ዓ.ም፤ በአዲስ ከተማ ት/ቤት የተጀመረው ተማሪዎችንና ንጹሃን ዜጐችን በግፍ የመግደል እርምጃ ተከትሎ አብዛኛው ባለስልጣናት ልጆቻቸውን ከየት/ቤቱ በአጃቢ ያስወጡ ነበር። ወደ ካቴድራል ት/ቤት በሁለት ኮብራ ተጭነው የተላኩ 20 ልዩ የፌዴራል ፖሊሶች የጄ/ል ሰአረና የጄ/ል ብርሃነ (ወዲ መድህን) ሴት ልጆችን አጅበው ሄዱ። ሁለቱ ሴት ልጆች በማግስቱ አሜሪካ ኤምባሲ ቪዛ ተመቶላቸው ዓርብ ሰኔ 3 ቀን በረሩ። የብዙ ባለስልጣናት ልጆች በተመሳሳይ እንዲወጡ ተደረገ።

..29ሺህ የአሜሪካ ዶላር በተርም እየተከፈለላቸው መማር ቀጠሉ። የአዜብ ልጅና የእህቷ ልጅ፣ (በነገራችን ላይ አርአያ መኮንን ይባላል፤ በ1995ዓ.ም ቦሌ ከሩዋንዳ ፊት ለፊት ጥቂት ገባ ብሎ አዜብ ለዚህ ወጣት በ7 ሚሊዮን ብር ቪላ ቤት ገዝታ በስጦታ አበርክታለች። የቪላው ኪራይ ሂሳብ በስሙ ባንክ ይገባለታል) ..የአርከበና ስብሃት ልጆች በቨርጂኒያ፣ የሽፈራው ጃርሶ ልጆች በካሊፎርኒያ፣ የፖሊስ ኮሚሽነር የነበረው ወንጀለኛውና 5ሚሊዮን ዶላር ሰርቆ የወጣው ተስፋዬ መረሳ ልጆች በኒዮዎርክ….ወዘተ በተቀማጠለ ኑሮና በውድ ክፍያ መማር ያዙ።

ባለፈው አመት በነርስ የተመረቀችው የጄ/ል ሰአረ ልጅ ሐመልማል ሰዓረ የምርቃት ፕሮግራም ላይ ጄኔራሉ ተገኝተው ነበር።…ወደ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እንለፍ። እስክንድር በላባቸው ሰርተው ሃብት ካፈሩ ጥሩ ቤተሰቦች የተገኘ ልጅ ሲሆን የተማረው በሳንፎርድ ት/ቤት ነው። ከዚያም አሜሪካ መጥቶ ትምህርትና ህይወቱን ቀጠለ። “አገር አማን” ብሎ በዘመነ ኢህአዴግ አገር ቤት ገባ። ተደጋጋሚ እስርና ድብደባዎችን አሳለፈ። እነሆ “አሸባሪ” ተብሎ ከሌሎች ንፁሃን ጋር በእስር እየማቀቀ ይገኛል። እነ ጄ/ል ሰአረና መሰሎቻቸው በመቶ ሺህ በሚቆጠር ዶላር ልጆቻቸውን በአሜሪካና አውሮፓ ሲያስተምሩና ሲያንደላቅቁ፣ እንዲሁም ልጆቻቸውን ለማስመረቅ ሲገኙና ሲደሰቱ በአንፃሩ በመፃፉና ሃሳቡን በመግለፁ ብቻ እስር ቤት የተወረወረውና ናፍቆት ልጁን እንዳያሳድግ የተደረገው እስክንድር ነጋ ጭራሽ ቤተሰቡ ያወረሱትን ቤት በግፍ እንዲነጠቅ ተደረገ። በጄኔራሎቹና ባለስልጣናቱ ሰፈር ግን በሚሊዮን ብር የተገነባ ቪላ፣ ልጆቻቸው የሚንደላቀቁበት በመቶ ሺህ የሚቆጠር ዶላር…ወዘተ አለ። ይህ ከህዝብ የተዘረፈ የአገር ሃብት ነው!!

የጄ/ል ሰዓረ ባለቤት ኰ/ል ፅጌ በስማቸው በገርጂ የተገነባውና ሰባት ሚሊዮን ብር የፈጀው ቪላ ሲገኝ የሚገርመው የቅጥር ግቢው ወለል በእምነበረድ መሸፈኑ ነው። ሌላው በሙስና የታሰሩት የደህንነት ሹሞቹ ወ/ስላሴና ገ/ዋህድ..መኖሪያ ቤት ውስጥ በርካታ የጦር መሳሪያዎችና ቦንቦች እንዲሁም በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብና የቤት ካርታ ወዘተ መገኘቱን ገዢው ፓርቲ ይፋ አድርጓል። ዛሬ ጠያቂ ባይኖርም ቅሉ ነገር ግን ጄኔራሎቹና ባለስልጣናቱ እንደነ ወ/ስላሴ ዘርፈው ያካበቱት ለመሆኑ አያጠያይቅም። የሚገርመው መፅሐፍትና ጋዜጣ የተገኘበት የእስክንድር ቤት ሲወረስ በአንፃሩ ህገ ወጥ የጦር መሳሪያና ሚሊዮኖች ተገኘበት ያሉትን የዘራፊዎቹን የሙስና ቤት አልነኩም።… እንደ እስክንድር ሁሉ አቶ አንዱአለም፣ አቶ በቀለ፣ ውብሸት፣ የሙስሊሙ ህብረተሰብ ተወካዮች እነ አቡበከር.. በሙሉ ልጆቻቸውን እንዳያሳድጉ የተደረጉ የህሊና እስረኞች ናቸው!! እንዲሁም ጄ/ል ሰአረ በምሳሌነት ተጠቀሱ እንጂ የአብዛኛው ባለስልጣን ከዘረፋ የተገኘ ህይወት ተመሳሳይ ነው። የአንዳንዶቹ ባለስልጣናትና ልጆች የአሜሪካ ውሎና ኑሮ የሚያሳይ በፎቶ የተደገፈ ማስረጃ እንዳለ ሳልጠቁም አላልፍም።…

(በፎቶው ጄ/ል ሰዓረ ሴት ልጃቸውን አቅፈው ሲያስመርቁና ሲደሰቱ- በአንፃሩ እስር ቤት ከጋዜጠኛ ሰርካለም የተወለደው ሕፃን ናፍቆት እስክንድር በጨቅላነቱ በስደት ያለ አባት እንዲያድግ ተፈርዶበት ይታያል..)

General Seare & Nafkote

Filed in: Amharic