>

በኢትዮጵያ ምድር የግፍ እስር ይብቃ!!! (ኤልያስ ገብሩ)

እውነት ነው! እስረኛን ለመፍታት ጊዜ አያሻም!  ታዮ ደንደአ እና ስዩም ተሾመ እንኳን ተፈታችሁ! 
…ከዚህ በኋላም በረባ ባልረባ ማንኛውንም ዜጋ በግፍ ማሰር ፈጽሞ ማክተም አለበት! ለዚህ የአገዛዙ እኩይ ድርጊትም ጨክኖ መታገል ያሻል።
አገዛዙ ለድብቅና ለአድርባይ ዓላማው ሲል፣ ንጽሃን ዜጎችን ያስራል፣ ይፈታል። ድጋሚ ያስራል፣ ይፈታል። አዙሪቱን ይወደዋል – ለጥቅሙ ሲል።
 የግፍ እስር፡- ለሀገር፣ ለህዝብ ታላቅ ተግባራት ማከናወን የሚችሉ ዜጎች ተረጋግተው ስራቸውን እንዳይከውኑ ለዓመታት ከባድ ደንቃራ መሆኑን አምናለሁ። እስሩም እስረኛውን፣ ቤተሰቡን፣ የእስረኛውን የህይወት መስመሩን፣ የሞያና የፖለቲካ ትግሉን ክፋኛ ጎድቷል። የዴሞክራሲ ተቋማት መመስረት፣ ማደግ፣ መጠንከር፣ ፍሬ ማፍራት የሚችሉት ዜጎች ተረጋግተው መኖርና መስራት ሲችሉ ነው።
 አገዛዝ ደግሞ ይሄንን ጠንቅቆ ስለሚያውቅ፣ ጠንካራ ዜጎች ተረጋግተው እንዳይኖሩና በመረጡት መስመር ሰርተው ውጤታማ እንዳይሆኑ፣ ራሳቸውን፣ ቤተሰቦቻቸውን፣ ተቋሞቻቸውን፣ እንዲሁም ሀገራቸውን፣ አህጉራቸውንና ዓለምን መጥቀም እንዳይችሉ አንድም የሚያሰናክለው በግፍ እሳቤ ሴራ ዜጎችን በሰበብ አስባቡ በማሰር ነው። የግፍ እስር በቃ! ልንል ይገባል። እስር ከፖለቲካ ጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ እጅግ ያይላል። …መለስ ብሎ እንደሃገር የመጣንበትን አስቀያሚ መንገድ ማየት በቂ ይመስለኛል።
…ሌሎች የግፍ  እስረኞች ፍቱ! የግፍ እስርም በቃን! በቃን! በቃን!

በተያያዘ ዜና – የግብዣ ጥሪ ከሆላንድ ለጋዜጠኛ እና አክቲቪስት እስክንድር ነጋ

አምንስቲ ኢንተርናሽናል የተመሰረተበትን 50ኛ አመት ለማክበር በክብር እንግድነት ታላቁ እስክንድር ነጋን በሆላንድ አምስተርዳም ከተማ እንዲገኝ ጋብዞታል:: ጋዜጠኛና የሰብአዊ መብት ተከራካሪው እስክንድር ነጋ የፊታችን አርብ ሆላንድ አምስተርዳም ከተማ በአውሮፓውያን ሰአት አቆጣጠር 14:30 ላይ ይገባል። ታላቁ እስክንድር ነጋን (እስኬውን) በደማቅ ሁኔታ ለመቀበል የምትፈልጉ በተባለው ሰአት አምስተርዳም እስኪፓል ኤርፖርት ተገኙ:: እዛው እንገናኝ!
ከዚሁ የጋዜጠኞችን የፓለቲከኞች ዜና ሳንወጣ አርቲስቶቹ ለነጻነት ታጋዮቻችንን ፍቅራቸውን እና ክብራቸውን ገለጹ!!! ታሪኩ ደሳለኝ
አርቲስት ሽመልስ አበራ እና አርቲስት ማንገሻ ተሰማ ዛሬ ሚያዛያ 8/2010 ዓም ለጋዜጠኛ ተመሰገን ደሳለኝ፣ ለጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ ለፖለቲከኛ በቀለ ገርባ እና ለፖለቲከኛ አንዱዓለም አራጌ በአንድ ታዋቂ ሪስቶራት የምስጋናና የምሳ ግብዣ አድርገዋል። ምሳው ላይም እኛም ተገኝተን ነበር።
ሁለቱንም አርቲስቶች እናመሰግናለን።
ሚያዛያ 8/2010 ዓ.ም
#ድል_ለዲሞክራሲ
Filed in: Amharic