>

ባለቤት አልባ እስረኞች፤ ለሰው ልጅ የማይመጥንም  የማይገባም  ቦታ ታጉረዋል ይገኛሉ (ታሪኩ ደሳለኝ)

እነዚህን ሰዎች አረንጓዲ ቢጫ ቀይ ሰንደቅ ዓለማ ምንም ምልክት የሌለው ሰቅለው እና  ከበው በፈገግታ እና  በለበ ሙሉነት እያወሩ ሻይ ቡና እያሉ በገዛ ቤታቸው ስላገኘዋቸው ፖሊስ አስሬቸዋለሁ ካለ ዛሬ አራተኛ ምሽታቸውን  ይዘዋል። 
 እነ እስክንደር ጀሞ ከሚገኘው ከጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ቤት መጋቢት 16/2010 ዓም ይዞ  ሙዚቃ ሰፈር የሚገኘው ፖሊስ ጣቢያ እስከ ውድቅት ለሊት እንዲቀመጡ ከተደረጉ በኃላ ወደ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ወስዷቸዋል። 
በፖሊሲ መምሪያ ቀን 1
እዚህ መምሪያ ውስጥ ባደሩ በማግስቱ ጠዋት ሄጄ ሳያቸው ፊታቸው ላይ ግርማቸው ያልጎደለ ቢሆነም እንቅልፍ ባይናቸው እንዳልዞረ መላ ሁኔታቸው ይስታውቃል።
 አንድ ሜትር በአንድ ሜትር ከግማሽ  ሆኖ ስምንት ቦታ በፌሮ ብረት በተከፈፈለ መስኮት ወጥተው ከሌሎች አስረኞች ጋር በመሆን የፊታቸውን ግማሽ ብቅ አድርገው ትከሻቸውን አጉብጠው አንገታቸውን አስግገው ተመስገንን እስክንድርን አንዷለምን ሳያቸው የማወራው ጠፍቶኝ ዝም አልኩኝ። በሰዐቱ ሌሎች እስረኞች እየተጮጮኽሁ ከጠያቄዎቻቸው ጋር እየወሩ ቢሆንም አልተሰማኝም እን አንዷለም ያሉበት ሁኔታ አፍዝዞኛል። ከሰከንዶች በኃላ የግዴን አናገርኳቸው “እንዴት አደራችሁ?” አልኩኝ ሦስቱም ፈገግ አሉ “እግዜር ይመስገን፣ በጣም ደና ነን” አሉኝ የመጣውን ቁርስ ለማቀበል እየሞከርኩ “ተኛችሁ” አልኩ እስክንደር  እና አንዷለም ፈገግ አሉ። ተመስገን “አልተኙም ቁጭ በለው ነው ያደሩት” አለኝ እስክንደር ፈገግታው ሳይጠፋ “ለአስራ አምስት ሰው የማይሆን ቦታ ከኛ ጋር ዘጠና ሆነን ነው ያደርነው” አለኝ አንዷለም ወደ ተመስገን አየት አድርጓ “ወገብህን ታማሚ ነህ ተኛ ሲባል ጥሎን ላለመተኛት አስቸገረን” አለኝ።  መተሳሰባቸው መከባበራቸው አንተ ትብስ መባባላቸው ቢያስቀናኝም ሀኔታቸው ግን አሳዘነኝ።
እነሱን ካዋራው በኃላ ሌሎች አናገርኩኝ “እግር ለመዘርጋት ይቅርና አጥፎ ለመቀመጥ የማይመች ቦታ ማደራቸውን ለሰው ልጅ በፍፁም የማይገባ ቦታ ማደራቸውን ለጎናቸው ማረፊያ ይቅርና ጀርባቸውን ማስደገፊያ ቦታ ሳያገሩኙ ማደራቸውን አይናቸው ሳይከደን እንዳደሩ ነገሩኝ ባናቱም ክፍሉ ከሽንት ቤቱ ጋር ተያይዞ በመሰራቱ ሽታውና  ሞቀቱ ለጉድ መሆኑን ነገሩኝ። ይህን ስሰማ ከማዘን ውጪ ምንም ማድረግ ባለመቻሌ አዘንኩኝ።  በሀዘንም ወደ ሴቶቹ ክፍል ሄድኩኝ። ማህሌትና ወይንሸት በአንፃራዊ ሲታይ ከወንዶቹ ሻል ባለ ቦታ ውስጥ መሆናቸው ትንሽ ደስታ ተሰማኝ። እነሱንም አዋርቼ ወጣሁኝ።
 ቀን 6:15 ላይ 
በዚህ ሰዓት ላይ ምሳ ይዘን ብንመጣም እስከ ዚህ ሰአት ድረስ እዛው ነበርን ድንገት ከለቀቋቸው ብለን። ምሳ ሰዐት ላይ ወንዶቹን እስረኞቹን ፖሊሶቹ ቤሮቸውን ለቀው ለብቻቸው አስረዋቸው አገኘናቸው። ቦታው እጅጉን ከነበሩበት ጋር የማይገናኝ የተሻለ ነው። በሰአቱ የተወሰኑት ሰዎች ሸላብ አድርጓቸው ነበር። ይህን ስይ ትንሽ  ተረጋጋው። “ምን አሏችሁ?” አልኩኝ ተመስገንና እስክንደር መለሱልኝ። “እስካሁን ምን ነገር የለም ቃለም አልሰጠንም ኮኮብ የሌለው ባንዲራ ስቅላቹሀል ማንው ይህን ያደረገው አሉን አንድ ላይ ነው ያደረገው መሪም የለም ተመሪም የለም ብለናል” አሉኝ “ቦታው ትላንት ካደርነበት በጣም የተሻለ ነው” አሉኝ። ጥሩ ስሜት ተሰምቶኝ ወጣሁ። በሴቶቹ በኩል የነበረው ነገር የተለወጣ አይደለም።
በፖሊስ መምሪያ ቀን 2
በሁለተኛው ቀን  በወንዶቹ በሴቶችም በኩል ምንም አዲስ ነገር የለም።  ባሉበት እንዳሉ ናቸው። ክስም አልቀረበባቸው።
በፖሊስ መምሪያ ቀን 3
 ሦሰተኛ ቀናቸው ነው። በዚህ ቀን ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ብለን ሙሉ ቀን ጠብቀን ነበር ግን አልቀረቡም። ፖሊስም ጉዳያቸውን ለኮመንድ ፖስቱ አቅርቤለሁ አለ። ማን እንዳሰራቸው ሳናውቅ ወደ ቤታችን ሄድን። ምሽት ላይም ለሚዲያዎች የአስቸኳይ ግዜ አዎጅ መምሪያም  እነ ተመስገን እንደታሰሩ አላውቅም አለ። እኛም ነገን ተስፋ አድርገን ሳንተኛ አነጋን።
በፖሊስ መምሪያ ቀን 4
 
ዛሬ መጋቢት 19/2010 ዓ.ም  ጠዋት ለቁርስ ሲኬድ ኮማንድ ፖስቱም መታሰራቸውን አላቅም ስላለ ፖሊስ መምሪያውም ስላልከሰሰቸው መደበኛ ፍርድ ቤትም ሳይቀርቡ 48 ሰዓት ስላለፋቸው ይፈታሉ የሚል እምነት ነበረን። የሆነው ግን ሌላ ነው።
ከነበሩበት ቦታ አንስተው መጀመሪያ ያሳደሯቸው ለማንም የማይገባም የማይመጥም ክፍል አዘዋውረዋቸው ደረስን።
ይህ ክፍል የመጀመሪያ ቀን 90 ሆነው ያደሩበት ነው። ክፍሉ ለተመስገን አይነቱ የወገብ በሽታ ላለበት ይቅርና ለማንም ጤነኛ ሰው የሚሆን አይደለም።
 እንግዲህ እዚህ ክፍል ውስጥ ነው ዛሬ ተመስገን ደሳለኝን፣ እስክንደር ነጋን፣ አንዷለም አራጌን፣ ዘላለም ወርቃገኘሁን፣ በፍቃዱ ሀይሉን፣ ስንታየሁ ቸኮልን፣ ይድነቃቸው አዲሱን፣ ተፈራ ተስፋዬን፣ አዲሱ ጌትነትን ነው እዚህ ክፍል ውስጥ ያጎሯቸው።
ማህሌትና ወይንሸት ያሉበት ከፍልም ዛሬ ወደ ስድስት ሰው ተጨምሮበታል።
 የዛሬምው ሁኔታዎቻው ከመውጣት ይልቅ እስር ቤት እንደሚቆዩ የሚያሳይ ስለሆነ እኛም ለታሳሪዎቹ በእስር ቤት የሚያስፈልጋቸውን ነገር ማሟላት ጀምረናል።
 እንግዲህ እስካሁን ከሳሻቸውም ክሳቸውም አልታወቀም። ፖሊስ መምሪያው ጉዳዩን ለኮማንድ ፖስቱ አሳውቄ እየጠበኩ ነው ይላል ኮማንድ ፖስቱ እንደታሰሩ አላውቅም እያለ አንዱ አንዱላይ እያሳበበ እስካሁን በአጎል ቦታ በሆነ እስር ቤት ውስጥ ባለቤት አልባ እስረኞች ሆነው ለተቀመጡት ለነ ተመስገን ደሳለኝ ለነ እስክንድር ነጋ ለነ አንዷለም አራጌ፣ ለነ ዘላለም ወርቃገኘሁ፣ ለነ በፍቃዱ ሀይሉ፣ ለነ ማህሌት ፋንታሁን፣ ለነ ወይንሸት ሞላ፣ ለነ ስንታየሁ ቸኮል፣ ለነ ይድነቃቸው አዲሱ፣ ለነ ተፈራ ተስፋዬ እና ለነ አዲሱ ጌትነት እስር ሀላፊነቱን እኔ ነኝ የምወስደው  የሚለውን አካል እንፈለጋለን ብቻ ሳይሆን የለ ቅድመ ሁኔታ ታሳሪዎቹ እንዲፈቱ አጥብቀን እንጠይቃለን።
ታሪኩ ደሳለኝ (ሚኪ)
መጋቢት 19/2010 ዓ.ም
Filed in: Amharic