>

እስክንድር ነጋና አንዱዓለም አራጌን ጨምሮ 746 ግለሰቦች በይቅርታና ክሳቸው ተቋርጦ እንዲለቀቁ ተወሰነ (ጌታቸው ሽፈራው)

በተለያዩ ወንጀሎች ፍርደኛ የነበሩ 417 ታራሚዎች ይቅርታ እንዲደረግላቸው በይቅርታ ቦርድ ተወሰነኗል።
የፌዴራል ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ዛሬ እንዳስታወቀው ጉዳያቸው በፍርድ ሂደት ላይ የሚገኝ 329 ተጠርጣሪዎች ደግሞ ክሳቸው እንዲቋረጥ ተደረጓል።

እርምጃው የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የይቅርታና የክስ ማቋረጥ እንደሚያደርግ በወሰነው መሰረት የተከናወነ ነው ብሏል ጠቅላይ አቃቤ ሕግ።

ይቅርታ እንዲደረግላቸው በቦርዱ ከተወሰነላቸው 417 ፍርደኞች መካከል የኦነግ፣ ግንቦት ሰባት፣ አልሸባብ፣ ጋህነን፣ሲአን፣ በሀይማኖት አክራሪነትና በሁከትና ብጥብጥ የተፈረደባቸውና ሌሎችም እንደሚገኙበት ጠቅላይ አቃቤ ሕግ አስታውቋል።

ይቅርታ ከተደረገላቸው መካከል እስክንድር ነጋ እና አንዷለም አራጌ እንደሚገኙበትም ታውቋል።

ይቅርታ ከተደረገላቸው ፍርደኞች መካከል 298ቱ በፌዴራል ደረጃ የነበሩ ሲሆን 119ኙ ደግሞ ከአማራ ክልል ናቸው።

ይቅርታ ተጠቃሚ እንዲሆኑ በይቅርታ ቦርድ የተወሰነላቸው ፍርደኞች ለአገሪቱ ርእሰ ብሔር ቀርቦ ሲጸድቅ የተሀድሶ ስልጠና ወስደው ወደ ሕብረተሰቡ ይቀላቀላሉ ተብሏል።

ክሳቸው እንዲቋረጥ የተወሰነላቸው ደግሞ በፌዴራል 278 በአማራ ክልል 18 እንዲሁም በትግራይ ክልል 33 በድምሩ 329 ናቸው።

ክሳቸው እንዲቋረጥ የተወሰነላቸው ተከሳሾችም የተሀድሶ ስልጠና ወስደው ወደ ሕብረተሰቡ እንደሚቀላቀሉ የፌዴራል ጠቅላይ አቃቤ ሕግ አስታውቋል።

Filed in: Amharic