>

"ጃ ያስተሰርያል!" አራት አመታት ተከልክሎ በነበረ መድረክ? (ክንፉ አስፋ)

 ቴዲ ወደ ባህርዳር ሲያቀና “እንዘምራለን”  ማለቱን ያስተውሏል!።  የጉዞውን አላማ እንዲያ ሲል ነበር ረቂቅ በሆነ መንገድ የገልጸው።  በመዘመር እና በመዝፈን መሃልያለውን ጥልቅ ልዩነት የማይረዳ ብቻ ነው ለሰሞኑ “አሲዮ ቤሌማ” እጅ የሚሰጠው።  ከኮንሰርቱ ጀርባ ያለው “የፍቅር ጉዞ” የሚለው መሪ ቃል ውስጥም ከውቅያኖስ የጠለቀመልዕክት አለ። ይህንን ቃል የተረዳ ብቻ ነው የተልእኮውን ስኬት ሊያበስር የሚችለው። ዝግጅቱ ኮንሰርት እንጂ ዳንኪራ አይደለም። ሁለት ወይንም ሶስት ሰዓት ብቻ የፈጀኮንሰርት። ጥላቻ ሳይሆን ፍቅር የነገሰበት ኮንሰርት።  ትንሳዔን አብሳሪ ኮንሰርት። መዝሙር ውስጥ መልዕክት አለ። የሚያንጽ፣ የሚያነቃቃ መልዕክት።

መላው በጠፋበት በዚህ ወቅት፤  ኢትዮጵያ የምትሻው የተስፋ ቃል ብቻ የሚደሰኩርላትን ሳይሆን ድልድይ የሚዘርጋላትን ሰው ነው።  ጥላቻ ነግሷል። በሃገራችን ስርሰድዶ፤ ቤተ እምነትን ሳይቀር አምሶታል፤  ጥላቻ – ጥላቻን ይወልዳል እንጂ ችግርን አይፈታም።  እሱን ለማንገስ ላለፉት 27 ዓመታት ብዙ ድንጋይ ተፈንቅሏል። አዎ ጥላቻ በሽታመሆኑን አይተናል።

ይህን ክፉ በሽታ ለማርከስ  የፍቅርን ዳገት መውጣት ግድ ይላል። ጉዞውን ቴዲ ጀመረው። ጥላቻን የሚያከስሙ ዜማዎቹን የሰሙ …  እነ ለማ መገርሳ እነ … ዶክተርአብይ ተከተሉት።  ለማ መገርሳ “ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው” ማለቱ  የቴዲ “ሲንድረም” ስለመሆኑ የሚጠራጠር ይኖር ይሆን?

            ጎበዝ፣  ዘመኑንም እንቃኘው እንጂ!   ሰው ለታቦት ንግስ ወጥቶ በዚያው የሚቀርበት ዘመን እኮ ነው ያለነው። ወገን የእሬቻን በዓል ለማክበር ሄዶ እስከዘላለሙየማይመለስበት ወቅት ላይ ነን።  ልቅሶና ሃዘንን ሰብሰብ ብሎ በጋራ የማይካፈሉባት ምድር፣  ምእመናን ለጸሎት ወጥተው የሚታፈኑበት ሃገር ላይ እንደተቀመጥን ለአፍታምአንዘንጋው።  ኮንስርት ማድረግ  ብርቅ የሆነበት ሃገር። ዳር ድንበር እንዲያስከብር የተላከ ወታደር  መሃል  ከተማ ገብቶ የወገን ደም የሚያፈስስበት ምድር!  በዚህች ያልታደለችሃገር፣ በዚህ አስከፊ ዘመን፣   “ጃ ያስተሰርያል”ን  አጥንት ይዘን ስንጓተት አጃኢብ አይሆንም?

            ይህ እሰጥ እገባ  ልብ ላለው ሁሉ ቅንጦት ይሆናል።  ነገሩን በደንብ የተረዳው ወገን፣  ከ 50 ሺህ ሕዝብ  በላይ በታደመበት ዝግጅት ላይ  “ምን ይፈጠር ይሆን?”  እያለየልቡ ትርታ ከፍ እና ዝቅ ይል ይሆናል እንጂ፣  ቀሪ ሂሳብ አያወራርድም።  ጥሩ ዜና በሚናፈቅበት በዚህ ቀውጢ ሰዓት፣  ሰማይ ላይ የወጣን የሕዝብ እምቅ ስሜት ተቆጣጥሮበሰላም ማጠናቀቅ መቻል እጅግ የሚደነቅ ነገር  ነው። ስለዚህም ጉዳዩ የገባቸው ዝግጅቱ  “እንኳን በሰላም አለቀ!”  ይላሉ።  ሻንጣ በጀርባ ሸክፎ ማራቶንን መሮጥ ምን ያህልአስቸጋሪ እንደሆነ የሚያውቀው ሯጩ ብቻ ነው።

           እርግጥ ነው ሕዝብ ፍላጎቱን ገልጿል። የሕዝብ ጥያቄ ተገቢ ምላሽ ማግኘት ነበረበት።  የሕዝቡ ጫና ቀላል አልነበረም።  ይህንን በተመለከተ ከቴዲ አካባቢ የሚሰማውነገር የህዝብ ስሜትን ያለመረዳት ጉዳይ አይደለም።   ስሜትን መረዳት እና ስሜትን መንዳት ሁለት የተለያዩ ነገሮች ናቸው።   26ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የነበሩት ቴዎዶርሩዝቬልት በአንድ ወቅት ሲናገሩ “በመሪዎች እና በአለቃ መካከል ያለውን ልዩነት ሰዎች ይጠይቃሉ።  መሪ ይመራል። አለቃ ደግሞ ይነዳል” ብለዋል።  መንዳት እጅግ ቀላል ነው።ውል ለማስያዝ መምራቱ ነው ከባድ።

        አራት አመታት ሙሉ ተከልክሎ የነበረ መድረክ፣  በሰላም እንዳያልቅ፣   እንከን የሚያሸትቱ ተንኳሾች  አሰፍስፈው የሚጠብቁት ነገር ነበር። የጌታቸው ማንጉዳይ ጣልቃመግባት ነገሮችን አስቀድሞ የመረዳት፣ አርቆ የማሰብ እና የመብሰል ውጤት ነው።  በዚህ ፍቅር ጉዞ እቅድ ላይ  “ጃ ያስተሰርያል” አልነበረም።  ጉዞው ለመዝፈን ሳይሆንመልዕክት ለማስተላለፍ ነው።  የሰላም እና የፍቅር መልዕክት።  በዚያ ውስጥ ሃዘን አለ። በዚያ ውስጥ ብሶት አለ። በዚያ ውስጥ ቁጭትም አለ።   በነገራችን ላይ በኮንሰርቱ ላይባለስልጣኖቹ በይገኙም ልጆቻቸው እና ሚስቶቻቸው በሙሉ ስቴዲየም ገብተው ከሕዝቡ ጋር ሲደሰቱ ነበር።

ሕዝብ በአንዲት ቃል ብቻ ማነሳሳት እጅግ ቀላል ነው።  በረጅሙ የሚያይ ሳይሆን አጭሩን አላማ የመረጠ ይህንን ማድረግ ይቀልለዋል። ከዚህ ግፊት የሚገኘውውጤት፣  ኪሳራ እንጂ ትርፉ ሚዛን ሊደፋ አይችልም።  ጥይቱንም፣ ቀለሃውንም የያዙ ሃይሎች ሰፍ ብለው ይህችን ወቅት እንደሚጠብቁ አንዘንጋ።

እያወራን ያለነው ስለ ሞብ  ስነ-ልቦና ነው። ሞብ  የማህበረሰብ ስነ-ልቦና አካል ነው። የስነልቦና ምሁራን የሆኑት ጉስታቭ ሌቦን እና ሲግሞንድ ፍሬድ “ሰዎች አንድ አላማይዘው በሲሰባሰቡ በሚጋሩት የጋራ የሆነ አመለካከት፣  ግላዊ ሃላፊነትን ከአናታቸው አርደው ስለሚጥሉ፣  ምንም ነገር ከማድረግ አይቆጠቡም ” ይሉናል።

            ይህን ያህል ግዙፍ ኮንሰርት ይቅርና ሰዎቹ የራሳቸው የመቀሌው ስብሰባም “በሰላም አለቀ” ይሉን የለ? በረጅሙ እየተነፈሱ “የአዲስ አበባው ጥምቀት በዓል በሰላምተጠናቀቀ” ብለውናል። በተዘዋዋሪ ሰላም የምትለው ቃል  እንደ ዳይኖሰርስ  ከምድሪቱ ጠፍታለች እያሉን እኮ ነው። ሰዎቹ እኮ አስከሬን አጅቦ የሚሄድን ለቀስተኛ እንኳን ማመንየተሳናቸው፣ በራስ ገመድ ተጠልፈው፣  የራሳቸውን ጥላ እንኳን የሚፈሩ፣….  ምጥ ውስጥ ያሉ ናቸው።  የፈሪ ዶላ ረጅም ነው እንዲሉ በጋራ ሆኖ ያዜመ ላይ ሳይቀር የሚተኩሱት ለዚህም ነው።

            ትልቁን ጥበብ እና ማስተዋል የሚጠይቀው ሕዝብ በተሰበሰበበት ስፍራ ሊመጣ የሚችለውን ችግር ማስወገድ መቻል ነው።  ይህ አርቆ ማሰብን ይጠይቃል። ቅዝምዝምሲወረወር ጎንበስ ብሎ የሚያልፍ  አስተዋይ ብቻ ነው። የሕዝብን ስሜት ማረጋጋት መቻል ራሱን የቻለ ጥበብ ይጠይቃል። ብሶት ያጋለው ሕዝብ ነው። እልህ የተናነቀው ሕዝብ።በቋፍ ላይ ያለ ሕዝብ።   አንድ ነገር ለማድረግ ጥቂት ቃላት ብቻ ይበቃሉ።

ደግሞ ጨዋ ነው። መሪውን የሚሰማ – ለሚወድደው የሚታዘዝ ሕዝብ።

            ሁሉም ነገር ግዜውን ጠብቆ ይከሰታል። ከዚህ ቀደም ቴዲ “ጃ ያስተሰርያል”ን ለምን አልዘፈነም ብለን ጮኸናል። ለጩኸታችን ምክንያቱ አጥጋቢ ይሁንም-አይሁን፣ ወቅቱ ይህንን ለማለት ይፈቅድ ነበር። ከአመታት በፊት “ጃ ያስተሰርያል”  ሲዘፈን የነበረው ሁነታ አሁን የለም። አሁን  ስለ ለውጥ እና ስለ አዲስ ንጉስ መምጣት አይደለም የምንጨነቀው። የመኖር እና የአለመኖር፣ የለህልውና ጥያቄ ላይ ደርሰናል።  የንጹሃን ደም በየቀኑ ይፈስሳል።  ሃገር እንደጉድ ይዘረፋል። እየተካሄደ ያለውን ግፍ ቃላትአይገልፀዉም።  ነገሩን ከስሜት መነጽር ወጣ አድርገን እንመልከተው።  ፈጥኖ መፍረድ እና ፈጥኖ መናደድ ከአመክንዮ ሳይሆን ይልቁንም ከፍርሃት እና ከድንቁርና ጋር እጅ ለእጅ የሚሄድ ነገር ነው።

            አሁን ነገሮች ተለዋውጠዋል።  ወደድንም ጠላን፣   አገዛዙ ዳግማዊ “ዘመነ መሳፍንት”  ውስጥ አስምጦን፣  እልቂት አፉን ከፍቶ እየጠበቀን ይገኛል።  ሃገሪቱ አጼ«ቴዎድሮስ»ን  ትሻለች። የአይሻልን ጦርነት በድል ተወጥቶ ዳግማዊው ዘመነ መሳፍንትን  ማብቂያ ያሚያውጅ ጀግና የማውጣቱን  ነገር  ግድ ይላል።

በቴዲ እና በአቡጊዳ ኢትዮጵያ የተጀመረው የፍቅር ጉዞ ይቀጥላል።  ቀጣይዋ  ከተማ ውቢቷ ናዝሬት / አዳማ ናት። በከተማዋ ቀደም ሲል የተዘራው የጥላቻ በሽታ በፍቅር ይታከማል። እነ ለማ መገርሳም በአዳማው ኮንሰርት ላይ ይገኙ ይሆናል።

ፍቅር ያሸንፋል!

Filed in: Amharic